Tuesday, April 15, 2014

ጥቂት የበድር አመራሮች በሰሜን አሜሪካ የሚገኘዉን የሙስሊሙን ማህበረስብ ስም በመጠቀም ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ለመነጋገር ወደ ኢትዮጵያ ያደረጉትን ጉዞ አስመልክቶ የወጣ መግለጫ

April 15, 2014
The First Hijrah Foundation
Washington, DC
ፈርስት ሒጅራህ ፋዉንዴሽን ኢትዮጵያዉያን ሙስሊሞች የሚያደርጉትን ሰላማዊ የመብት ትግል መዳረሻዉ ድል እስኪሆን ድረስ በማንኛውም ጉዳይ በጽናት ይደግፋል። በህዝብ የተመረጡት የሙስሊም የመፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴዎች በኢትዮጵያ ፍርድ ቤት ያሳዩት ቁርጠኝነትንና ጽናትን ፈርስት ሒጅራህ በእጅጉ የሚያደንቅም ብቻ ሳይሆን በነዚህ የሰላም አምባሳደሮች ላይ የኢትዮጵያ መንግስት እየፈጸመ ያለዉን ግፍ በማንኛዉም መልኩ የሚፋረደዉ ዘግናኝ እዉነታ ነዉ። እነዚህ ምርጥ የኢትዮጵያ ልጆች የሆኑት ኮሚቴዎች ዛሬም በእስር ቤት ውስጥ ያሳዩት የአመራር ብቃትና ጥንካሬ በአለማችን የታሪክ መዝገብ ላይ የሚሰፍር አኩሪ ታሪክ በመሆኑ ፈርስት ሒጅራህ ኮሚቴዎቹን ከመደገፍም ባሻገር የሚከተል መሆኑን ሲገልጽ በታላቅ በደስታ ነዉ።
የኢትዮጵያ መንግስት በኢትዮጵያዉያን ሙስሊሞች ላይ እያደረሰ ያለዉን ቀጣይ በደል ለመታደግ የታሰሩትን አሚሮችን (መሪዎችን) በመከተልና ድምጻችን ይሰማ የሚያወጣዉን ትእዛዝ ለመተግበር ፈርስት ሒጅራህ ወደ ሗላ የማይል መሆኑን እያስገነዘበ፤ ኢትዮጵያዉያን ሙስሊሞች የሚያደርጉትን ሰላማዊ ትግል ለማኮላሽት የሚደረግ ማንኛዉንም እንቅስቃሴ ለማጋለጥ ፈርስት ሒጅራህ እምርታዊ በሆነ ትጋት የሚሰራ መሆኑንም ለመግለጽ ይወዳል። እንደ አገር መሪ ሳይሆን እንደ አሸባሪ የሚንቀሳቀሰዉ የኢትዮጵያ መንግስት የፈርስት ሒጅራህ ፋዉንዴሽንን እስትራቴጂያዊ ጠቀሜታ ከግምት ዉስጥ በማስገባት ድርጅቱ የሚያደርገዉን ጠንካራ የመብት ትግል ለማርገብ ያደረጋቸዉ ጥረቶች ሁሉ የመከኑበትን እዉነታ ለመላዉ የኢትዮጵያ ህዝብ ይፋ ማድረጉም ግድ ይላል።
ፈርስት ሒጅራን ጨምሮ ሌሎች በሰሜን አሜሪካ የሚገኙ ኢትዮጵያዉያን ማህበራት የመሰረቱት በድር አለምአቀፍ የኢትዮጵያዉያን ሙስሊሞች ድርጅት የተመሰረተለት አላማን በማፋለስ፤ በድርጅቱ ምስረታ እና አወቃቀር ብሎም አመራር ላይ ወሳኝ ሚና ያለዉንና ለወደፊቱም በድርጅቱ ህልዉና ላይ አይቀሬ ተሳትፎና ድርሻ ያለዉን ፈርስት ሒጅራን በማግለል፤ የኢትዮጵያን መንግስትና የሙስሊሙን ማህበረሰብ እናደራድራለን በማለት አብዛኛዉ ያልወከላቸው ጥቂት የበድር አመራሮች በቅርቡ ስኬት አልባ የሆነን ጉዞ ወደ ኢትዮጵያ ማድረጋቸዉ ይታወቃል። ይህንን ሙሉ ህዝባዊ ይሁንታ ያላገኘዉን ጉዞ ፈርስት ሒጅራህ ፋዉንዴሽን ከዚህ ቀደም እንደተቃወምነዉ አሁንም ሙሉ በሙሉ የሚቃወም መሆኑን እየገልጸ ያለዉንም አቋም ለመላዉ የኢትዮጵያ ህዝብ ይፋ ማድረግ ይፈልጋል።
ቀደም ሲል በመንግስትና በሙስሊሙ ጉዳይ ላይ ገለልተኛ(ኒውትራል) የሆነ አቋም ነዉ ያለን በማለት በይፋ ይናገሩ የነበሩ ግለሰቦች፤ ዛሬ የኢትዮጵያ መንግስት አትኩሮት ሰጥቶ በልዩ አቀባበል(VIP)አስተናግዶናል፤ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር በከፈትነዉ መስመር መስራቱን እንቀጥላለን፤ ሙስሊሙ ህብረተሠብ አንቅሮ የተፋውን የመንግስት መጅሊስን የሙስሊሙ ጉዳይ ያገባዋል (stakeholder) ነው በማለት እዉቅና በመስጠት አነግረናል፣ኢትዮጵያ ዉስጥ ቢሮ ከፍተናል በማለት ያለ ምንም እፍረት ሙስሊሙን ማህበረሰብ እያወናበዱ ይገኛሉ። እነዚህ ግለሰቦች ባስቸኳይ የያዙትን የህዝብ አደራ አስረክበዉ የድርጅቱ መመሪያ ተተግብሮ ህዝብ ያመነበት ምርጫ እንዲደረግ ፈርስት ሒጅራህ በአጽኖ ይጠይቃል።
የኢትዮጵያ መንግስት በሙስሊሙ ማህበረስብ ላይ የሚያደርሰዉን ጭቆና ለማዉገዝ ፍላጎት ብቻ ሳይሆን ወኔ የሌላቸዉ የመንግስትን ጥቅም አስከባሪና መንግሥት በሙስሊሙ ህብረተሰብ መካከል የተፈጠረውን አስጊ አለመግባባትን መፍትሄ ለማስገኘት ነዉ በማላት የተሳሳተ አመለካከታቸዉን ሲያራምዱ የነበሩ ግለሰቦች ዛሬ አስታራቂ መስለዉ ኢትዮጵያ መሔዳቸዉ የሙስሊሙን ማህበረሰብ ንቃተ ህሊና እንደናቁ የሚቆጠር እጅግ አሳፋሪ ስራ በመሆኑ ባስቸኳይ ከበድር ድርጅታዊ አሰራር ገለል እንዲሉ ፈርስት ሒጅራህ የጠይቃል።

ፈርስት ሒጅራህ ከጅማሮዉ አንስቶ ከሌሎች አጋር ድርጅቶች ጋር በመተባበር በአያሌ መስዋእትነት የገነባዉ በድር፤ ከመስመር በወጡ ጥቂት መሪዎች ግላዊ ፍላጎት የሚፈርስ አይደለም። በመሆኑም ፈርስት ሒጅራህ በመላዉ አለም ከሚገኙ ኢትዮጵያዉያን ሙስሊሞች ጋር በመጻጻፍና በመዘዋወር ግንዛቤን የማስጨበጥ ስራ ይሰራል።
ለፊትና (መከፋፈል)የሚለዉን ቃል ብዙ የግል ጥቅም አስጠባቂ አካላት የሚጫወቱበት ካርድ በመሆኑ፤ ፈርስትሒጅራህ በወሰደዉ አቋም ፊትና ፈጣሪዎችን መንቅሮ ለማዉጣት የሚያደርገው ጥረት መላዉ የኢትዮጵያ ሙስሊም ምንም አይነት ግራ መጋባት ሳይስተዋልበት ጥረታችን ከስኬት ይደርስ ዘንድም በዱዓ (በጸሎት) ይበረታ ዘንድም ፈርስት ሒጅራህ ይጣራል። ቀድም ሲል በኢትዮጵያ የሚገኙ ታዋቂ ዳኢዎች እና ተጽእኖ ፈጣሪ ግለሰቦች ሰላማዊ ትግሉን ለመቀልበስ ያደረጉት ሙከራ በተባበረዉ የሙስሊሙ ማህበርሰብ ክንድ እንደከሸፈዉ ሁሉ ተመሳሳይ ሴራን ለማክሸፍ ፈርስት ሒጅራህ የሚያደርገዉን ጥረት ሙስሊሙ ማህበረሰብ እንዲረዳዉ ያሳስባል።
ኮሚቴዎቻችንና ሌሎች በሺዎች የሚቆጠሩ ንጹሃን ዜጎች የታሰሩበት፣ የተገረፉበት፣ የተሰቃዩበት፣የሞቱበትና ብዙዎች የተሰደዱበትን ትግልን ከንቱ ለማድረግ ለሚነሳ ማንኛዉም ሐይል ታጋሾች አንሆንም። በየአደባባዩና በተለያዩ የዲፕሎማሲ መድረኮች በግልጽ ወጥተን ህዝብ ከወከላቸዉ አሚሮቻችን ጎን ቆመን ለመብት ለነጻነት በመታገላችን አንገት ደፊና ይቅርታ ጠያቂዎች አንሆንም። በድር ድርጅታችን ነዉ፦ በድርን ለማዳን ቆርጠን በመነሳታችን መላዉ ኢትዮጵያዊ ሙስሊም በዱዓ (በጸሎት) እንዳይረስን እንማጸናለን።
የሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ በአስቸኯይ ከእስር ይለቀቁ፦
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ
አላሁ አክበር

No comments: