Tuesday, April 8, 2014

እነ አብርሃ ደስታ ታስረው ተፈቱ (አፈናው ትግራይ ውስጥ ተባብሷል)

April7/2014


 በትግራይ ውስጥ በግልጽ ህወሃትን በመቃወም ከሚንቀሳቀሱት ተቃዋሚ ፓርቲዎች መካከል አረና አንደኛው እና ዋነኛው ነው። ትላንት እሁድ መጋቢት 28 ቀን፣ 2006 ዓ.ም. በአፅቢ ወንበርታ ወረዳ ሓይቂመስ ሓል ከተማ ስብሰባ ለማድረግ እቅድ አድርገው ነበር። ከስብሰባው በፊት ግን ቅስቀሳ ሲያደርጉ በነበሩ ሰዎች ላይ ህጻናት ድንጋይ እንዲወረውሩባቸው ነው የተደረገው። ቀላል ድብደባም ተፈጽሞባቸዋል። ከያዙት ሆቴል እንዲወጡ አልጋ ያከራየውን ሰው ሲያስፈራሩት ነበር። ይህ አልበቃ ብሎ የተደበደቡት ሰዎች ሶስቱ በፖሊስ ተይዘው ታስረዋል።
ከስፍራው ሁኔታውን ሲዘግብ የነበረው አብርሃ ደስታ ከመታሰሩ በፊት እንዲህ ብሎ ነበር። “በአስተዳዳሪዎች ትእዛዝ የእንዳስላሴ ቤተክርስትያን ሐላፊዎች የቤተክርስቲያኒቱ ማይክሮፎን በመጠቀም የአፅቢ ህዝብ እሁድ (ዓረና ስብሰባ በጠራበት ሰዓት) በእንዳስላሴ ቤተክርስትያን እንዲገኝ እያወጁ ይገኛሉ። እሁድ በእንዳስላሴ ቤተክርስትያን ያልተገኘ “ክርስትያን አይደለም!” እያሉ ህዝብን እያስፈራሩ ነው። …ህወሓት ኢህአዴግ በሁሉም ሀይማኖቶች ጣልቃ መግባት የሚፈልገው እንደዚህ የሀይማኖት መሪዎች የህወሓት የፖለቲካ መሳርያ እንዲሆኑ ስለሚፈልግ ነው። ከወራት በፊት ቄሳውስት ህዝብ ህወሓትን እንዲደግፍ በመስቀል እንዲያስምሉት ታዘው ህዝቡ ፍቃደኛ እንዳልሆነ ይታወሳል።
የህወሓት ስጋት ይህን ያህል ነው። ምንም የህዝብ መሰረት እንደሌለው ስለሚያውቅ ህዝብ በስብሰባ እንዳይገኝ ማድረግ፣ ቅስቀሳ የሚያደርጉም መረበሽ፣ መደብደብ ነው ስራው።” ይህን ያለው አብርሃ ደስታ ስብሰባውን ካደረገ በኋላ ከሌሎች ጋር  ታሰረ። ከዚህ በመቀጠል የምናቀርብላቹህ፤ የአረና አመራሮችና ደጋፊዎች ታስረው በነበረበት ወቅት፤ የፓርቲው ፕሬዘዳንት የሆኑት አቶ ብርሃኑ በርኼ የጻፉትን ነው። እንዲህ ይላል የአቶ ብርሃኑ መልዕክት።
እሁድ መጋቢት 28 ቀን 2006 ዓ/ም ዓረና ትግራይ ህዝባዊ ፖለቲካዊ ስብሰባ በምስራቃዊ ዞን አፅቢ ወንበርታ ወረዳ ጠርቶ ያካሄደ ሲሆን ከትናትና ጀምሮ ህዝቡን ወደ ስብሰባው እንዲመጣ የሚቀሰቅሱ አባሎችና አመራሮች ከድንጋይ ውርወራ ና የቡድን ረብሻ ባለፈ ከተከራዩት አልጋ አስወጥቶ ለሊት የትም ተጥለው እንዲወድቁ ለማድረግ እጅግ ኢ-ሰብአዊ ተግባር መፈፀሙን ተገልፆ ነበር ፡፡ የአፅቢ ፖሊስ አባላቶቻችን ከተከራየትና ገንዘቡን ከፍለው የክፍሉ ቁልፍ ተረክበው በእጃቸው ከሚገኝ ቤት ካለወጣቹህ በማለት ቅዳሜ መጋቢት 27 ቀን 2006 ዓ/ም አቶ አምዶም ገ/ሰላሴ ፣ አቶ ስልጣኑ ሕሸ ፣ መም/የማነ ንጉሰ እስከምሽቱ 2፡30 በአፅቢ ፖሊስ በእስር ነበሩ ፡፡ በዚሁ ቀን የወረዳ አስተዳዳዎች የሚመሩት ለህዝብ የሚታደል በራሪ ፅሑፍ መቅደድና በአረና አባላት ላይ ድንጋይ በመወርበር ሲያውኩ ዛሬ ጥዋት ደግሞ ህፃናትና ምልምል ካድሬዎች ገብረ ማርያም የተባለው የታጠቁ ሚልሻ ጭምር በዓረና አባላት ላይ መጠነ ሰፊ የማወክ ተግባር እንደጀመሩና ስብሰባው እንዳይካሄድ ከፍተኛ ጥረት እንዳደረጉ ተገልፆ ነበር ፡፡
እሁድ ከሰኣት በሁዋላ የህዝብ ስብሰባው እንደተጠናቀቀ ደግሞ የአረና ከፍተኛ አመራሮችና አባሎች እንዲሁም በስብሰባው የተገኙ ወደ 61 የሚሆኑ ገበሬዎች በአፅቢ ከተማ ፖሊስ ጣብያ ታስረዋል ፡፡ የእስሩ መነሻ ምክንያት ተደባዳቢ የወንጀለኞች ቡድን የአረና አባላትን ሲደበድቡና ስብሳባው እንዳይጀመር ሲያውኩ የሚያሳይ መረጃ በሞባይል ቀርፃችኋል የሚል ሆኖ ተቀረፀ የተባለው ፊልም ከተገኘበት የሞባይል ስልክ አውጥቶ ለመንጠቅና ለማጥፋት ያለመ ነው፡፡
የአቶ አብርሃ ደስታ ሞባይል ተወስዶ እየተፈተሸ ሲሆን የሌሎቹ የአረና ከፍተኛ የአመራር አባላትና አባላት ሞባይል ስልኮችም እንዲሁም በስብሰባው የነበሩ ገበሬዎች ሞባይል በፖሊስ ተነጥቆ በአፅቢ ፖሊስ ጣብያ እስር ቤት እየተፈተሸ እንደሆነ ቦታው ያሉ የአረና አባላት ሪፖርት አድርገውልኛል ፡፡
ሁኔታው ለትግራይ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘአማኑኤል ለገሠ በሞባይል ስልካቸው 0914 300868 ልክ ዛሬ እሁድ ከሰአቱ 9፡30 ደውየላቸው ስልኩን እንዳነሱ የምደውልላቸው ያለሁኝ ብርሃኑ በርሀ መሆኔን ገልጨ ልክ በኩሓ አፀያፊ እስርና መንግላታት በዓረና አባለት እየተፈፀመ እንዳለ ሪፖርት ሳደርግላቸው እኔን መሆኔን እንዳወቁ ወዲያው ስልካቸውን የዘጉብኝ እንዳይሆን ብየ ስልኩን እንዳይዘጉብይ በፍጥነት በአፅቢ ስብሰባ የሚያካሂዱ አባላቶቻችን መታሰራቸው ስነግራቸው ንግግሬን ሳልጨርስ ስልኩን ዘጉት ፡፡
ፖሊስ ወንጀል ስለመሰራቱ ማስረጃ የያዘለት ይሸልማል እንጂ ወንጀል መሰራቱን የሚያረጋግጥ መረጃ ለማጥፋት ፖሊስ የሚሰራ ከሆነ ይህ ዓይነቱ ፖሊስ የሰላም አባት ወይስ የወንጀል አባት እንበለው ?
አሁን በፖሊስ ምርመራ በአፅቢ ፖሊስ ጣብያ የሚገኙት 1- አቶ ስልጣኑ ሕሸ የዓረና የድርጅት ጉዳይ ሃላፊና የፅሕፈት ቤት ሃላፊ 2- አቶ ዓምዶም ገብረ ስላሴ የዓረና የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ 3- አቶ አብርሃ ደሰታ የዓረና የህዝብ ግንኙነት ኮሚቴ አባልና ስራ አስፈፃሚ አባል 4- መም/ ታደሰ ቢተውልኝ የዓረና ማእከላዊ ኮሚቴ አባል 5- አቶ አስገደ ገብረ ስላሴ 6 – መም/የማነ ንጉሴ 7 አቶ ሃይለ ኪሮስ ታፈረ 8- መም/ ሃይለ 9 አቶ ቴወድሮስ 10 – መምህር ክፍሎም እና ሌሎች የአረና አባላትና 61 የስብሰባው ተሳታፊ የአከባቢው ገበሬዎች ናቸው፡፡
ዓረና ትገራይ ፓርቲ ይህንኑ ዘግናኝ የገዢው ፓርቲ የዓፈና ተግባር እንዲቃወምና እንዲያጋልጥ ለሁሉም ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ፣ ለሰብአዊ መብት መከበር የሚሰሩ ተnማት ፣ በኢትዮጵያ ለሚሰሩ የውጭ መንግስታት ኢንባሲዎች እንዲሁም ድምፃቸው ለታፈኑ ድምፅ ለመሆን ለሚሰሩ የሃገር ውስጥና የውጭ ሚድያዎች ጥሪውን ያቀርባል ፡፡ በተጨማሪም እነዚህ የጠራራ ፀሃይ ወንጀለኛች በሕግ ፊት ለመፋለም ይረዳ ዘንድ የቻለ ሁሉ ኢትዮጵያዊ ለዓረና ትገራይ ፓርቲ የገንዘብና የሙያ ድጋፍ እንዲያደርጉ ለሁሉም ወንጀል የሚፀየፉ ወገኖች ጥሪውን ያቀርባል ፡፡
ይህ ዓይነቱ ዓይን ያወጣ ወንጀል የትግራይ ህዝብ ከደርግ አፈና ለመታደግ በ 17 የትጥቅ ትግል ዓመታት ሂወታቸውና ንብረታቸው ለከፈሉ በሂወት ያሉ ለውጥ ፈላጊዎቹ የህወሓት አባለትና ደጋፊዎች እንዲሁም መላ የትግራይ ህዝብ በአማራጭ ሰላማዊ ትግል ለሚያካሂድ ፓርቲ የሚፈፀም ጭፍጨፋ በእራሱ መብት የተቃጣ ወንጀል መሆኑን አውቆ በምሬት እንዲቃወመው ጥሪውን ያቀርባል፡፡
ጭፍን ዓፈና የነፃት ባለ ራአዮችን በማጠናከር የነፃነት ራእይ ገዳዮችን የሚያዳክም ግብዝ ውሳኔ መሆኑን የትግራይ ህዝብ አኩሪ ፀረ ባእዳዊ ገዥዎችና ፀረ ፋሽት ደርግ ተጋድሎ በሚገባ ያስተማረን በመሆኑ በዚሁ እኩይ የደርግን አሻራ የወረሱ የአምባገነኖች ተግባር ዓረና ፓርቲና አባላቱ እንደማይንበረከኩ ሁሉም ሊያቀው ይገባል ፡፡ የዓረና ሃገራዊ ራዕይ የሃገር አጀንዳ ሆኖ በሃገረዊ ለውጥ ይደምቅ ዘንድ ዓረና ጠንክሮ እንደሚሰራም ደግሞ ያረጋግጣል ፡፡
ዓረና ትግራይ ለዴሞክራሲና ለሉእላዊነት ፓርቲ
መጋቢት 28 ቀን 2006 ዓ/ም ከቀኑ 10፡20
መቐለ
ዛሬ አብርሃ ደስታ ከ እስር ተፈቷል። ስለነበረው ሁኔታ እሱ ራሱ ያስተላለፈውን መልእክት ለአንባቢዎቻችን በማስተላለፍ ዘገባችንን እናበቃለን። እንዲህ ይላል የአብርሃ ደስታ የመጨረሻ ዘገባ።
ጓዶች ህወሓት ምንም የህዝብ (በተለይ የትግራይ) እንደሌለው በማረጋገጡ በምርጫ ሙሉ በሙሉ ቢሸነፍ እንኳ ስልጣን በሰለማዊ መንገድ ለማስረከብ ፍቃደኛ እንደማይሆን ከወዲሁ እያረጋገጠልን ነው። በትግራይ ምርጫ ስለመፈቀዱም እርግጠኛ አይደለሁም። ባለፈው ቅዳሜና እሁድ የዓረና አባላት በአፅቢ ከተማ ምግብና አልጋ እንዳያገኙ ተደርጓል። በህፅናትና የህወሓት መሪዎች ተደብድበዋል። እሁድ በዓረና ስብሰባ ለመሳተፍ የመጡ የአፅቢ ኗሪዎች በአዳራሹ በር አከባቢ በድንጋይ ተወግረዋል። እሁድ ማምሻውን የዓረና አባላት በፖሊስ ጣብያ ለሁለት ሰዓት ያህል ታስረዋል (ስለተደበድቡ ታስረዋል)። ተሳታፊዎችና የዓረና አባላት ድብደባ ሲፈፀምባቸው የተቀረፀ ቪድዮ ከዞን (ዓዲግራት) በመጡ ባለስልጣናት በሃይል ተፈትሿል። ሞባይሌ ያለ ፍቃዴ በፖሊስ ሃይል ተነጥቄ የቀረፅኩት የድብደባ ማስረጃ ተፈትሾ ተሰርዟል። የሞባይል ቆፎዬ ተበላሽቷል። አሁን ቅስቀሳችንና ስብሰባችን እንቀጥላለን። ምክንያቱም ህዝብ የራሱን ድምፅ በራሱ የሚያስከብርበት ዓቅም እስኪገነባ ድረስ ማስተማራችን እንቀጥላለን። ህዝብ ራሱ የራሱን ድምፅ ካላከበረ ህወሓት እንዲያከብርለት አይጠበቅምና።

No comments: