Wednesday, April 30, 2014

ሰማያዊ ፓርቲ የአርበኞችን ቀን ሊያከብር ነው – በተጨማሪም የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ቅጣት ተጣለባቸው

April 30/2014

ሰማያዊ ፓርቲ ሚያዝያ 27/2006 ዓ.ም የአርበኞችን ቀን በጽ/ቤቱ ታዋቂ የታሪክ ተመራማሪዎችንና ሌሎች ምሁራንን ጋብዞ እንደሚያወያይ ምክትል የህዝብ ግንኙነቱ አቶ እምላዕሉ ፍስሃ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡

ምክትል የህዝብ ግንኙነቱ እንዳስታወቁት ስነ ስርዓቱ ሰኞ ሚያዝያ 27 ከጠዋቱ 3 ሰዓት የሚጀምር ሲሆን ማንኛውምኢትዮጵያዊ በፕሮግራሙ መሳተፍ ይችላል ብለዋል፡፡ ‹‹የስነ ጽሁፍ ተሰጥዖ ያላቸውና በበዓሉ ስራቸውን ማቅረብ የሚፈልጉ ኢትዮጵያውያንንም እንዲሳተፉ እንፈልጋለን ያሉት ኃላፊው›› ፕሮግራሙን ወጣቶች ስለ አባቶቻቸው ታሪክ እንዲያውቁ ከማድረግም ባሻገር ስራቸውን በማስታወስ ታካቸውን ለመዘከር እንደሚፈልጉ አክለው ገልጸዋል፡፡

 የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ህግን ለማስከበር በመጣራቸው ተጨማሪ ቅጣት ተጣለባቸው 

ሚያዝያ 19/2006 ዓ.ም ለተካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ በቅስቀሳ ላይ የታሰሩት የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት በ1000 (አንድ ሺህ ብር) ዋስ እንዲወጡ መወሰኑን ተከትሎ ‹‹እኛ ነጻ ነን፡፡ ገንዘብ አስይዘን እንወጣም፡፡ ስራችን ህግ ማስከበር እስከሆነ ድረስ እየታሰርንም ቢሆን ህግ
እናስከብራለን፡፡ በመሆኑም ነጻ እስካልተለቀቅን ድረስ እሰሩን፡፡›› በማለታቸው ተጨማሪ ክሶችና ቅጣቶች እየተጣለባቸው ነው፡፡ በትናትናው ዕለት ሜሮን አለማየሁና ትግስት ወንዲፍራው ‹‹ግቢ በመረበሸ›› ተጨማሪ ክስ መከሰሳቸው ይታወቃል፡፡ በአሁኑ ወቅት በቤላፖሊስ ጣቢያ የሚገኙ 14 ያህል የሰማያዊ ፓር አመራሮችና አባላትም ተመሳሳይ ክስየተመሰረተባቸው ሲሆን ባለፈው ከፍላችሁ ውጡ ከተባሉት 1000 (አንድ ሺህ ብር) በተጨማ 600 (ስድስት መቶ ብር) ጨምረው ከፍለው እንዲወጡ ተፈርዶባቸዋል፡፡

እነዚህ አመራሮችና አባላት መጀመሪያ የካ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው የነበሩ ቢሆንም እስረኛውን በማሳመጽና በመረበሽ
ከመከሰሳቸውም በተጨማሪ ወደ ቤላ ፖሊስ ጣቢያ ተዛውረዋል፡፡ በወቅቱ ድብደባና ማዋከብ እንደደረሰባቸው የሚናገሩት
ታሳሪዎቹ ‹‹ህግን ለማስከበር የምናደርገውን ጥረት እንደ ህገ ወጥነት ተቆጥሮ ተጨማሪ ክስና በደል ቢፈጸምብንም እኛ ህግ
ማስከበራችንን እንቅጥላለን›› ብለዋል፡፡

በተመሳሳይ በጉለሌ ፖሊስ ጣቢያ የሚገኙትና ዛሬ ስምንት ሰዓት ላይ ፍርድ ቤት የቀረቡት የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት
እያንዳንዳቸው 5500 ብር አስይዘው እንዲወጡ ተፈርዶባቸዋል፡፡ ታሳሪዎቹ ይህንን ውሳኔ በመቃወም ‹‹ነጻ ካልተለቀቅን
አንወጣም!›› ያሉ ሲሆን ከዳኛው የተሰጣቸው መልስ እንዳሳዘናቸው ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ ‹‹ዳኛውና አቃቤ ህጉ
ተመካክለው ነው የገቡት፡፡ በእያንዳንዳችን 5500 ብር እንድንከፍል ሲፈርዱ፤ ‹እኛ ተማሪዎችና የመንግስት ሰራተኞች ነን
ከየትም አምጥተን መክፈል አንችልም!› አልናቸው፡፡ እነሱ ልክ አንድ ሰው እቃ ሲገዛ እንደሚከራከረው ‹በቃ! 2000 ብር
ይሁንላችሁ› አሉን፡፡›› ያሉት ታሳሪዎቹ በህግ ሳይሆን በዘፈቀደ እየተሰራ መሆኑ አሳዝኗቸዋል፡፡ በሌላ በኩል ‹‹ህገ ወጥ
ቢሆንም በሌላ አካባቢ የታሰሩት የእኛ ጓደኞች 1000 ብር ነው እንዲከፍሉ የተወሰነባቸው፡፡ የእኛውን ለምንድን ነው 5500
ያደረጋችሁት?›› ብለው ሲጠይቁ ዳኛው ‹‹ቅጣቱ ከጣቢያ ጣቢያ ይለያያል፡፡›› የሚል አስገራሚ መልስ እንደሰጧቸው
ገልጸውልናል፡፡

No comments: