Saturday, August 30, 2014

ይድረስ ለወዳጄ… (6ኛው ተከሳሽ ዘላለም ክብረት – ከቂልንጦ እስር ቤት – ክፍል ሁለት)

August30,2014
የኔ ፅጌረዳ ሰላም ላንች ይሁን! እንዴት ነሽልኝ? ባለፈው የፃፍኩልሽን ቧልታይ የበዛበት ደብዳቤ አነበብሽው ይሆን? ዛሬ ደግሞ ስለክሴ፣ ስለከሳሼና ስለአጠቃላይ ሁኔታዎች ልጽፍልሽ አሰብኩ፡፡ እንግዲህ በዚህ ደብዳቤ ትንሽ ኮስተር ሳልል አልቀርምና ከወዲሁ ይቅርታን እለምናለሁ፡፡
ዘላለም ክብረት
ዘላለም ክብረት
ግርምቴ
ከታሰርኩበት ሚያዝያ 17/2006 ጀምሮ በጣም ሲገርመኝ የነበረው ነገር የፖሊስ/የመንግስትና የሕግ ታላቅ እኩያ ነው፡፡ መንግስት ሁሌም ሕግን ለማሸነፍ በሙሉ ድል ‹ተጠርጣሪዎ› ለመክሰስ ችሏል፡፡ ከተያዝኩበት ደቂቃ ጀምሮ አውቆ በሚመስል መልኩ የተለያዩ የፍትሕ አካላት እያንዳንዱን የሕግ አንቀፆች በተግባር ሊጥሏቸው ማየቴ ነበር የመገረሜ ምክንያት፡፡
ለሕጎቹና ለሕግ አካላቱ ቅርብ በመሆኔ ምክንያት የመንግስት አካላቱ ይወስዷቸው የነበሩትን የተለያዩ ርምጃዎች በሕጉ አይን በማየቴ ሊሆን ይችላል የሕግ ጥሰቱ እጅግ ጎልቶ የታየኝ፡፡
የፍተሸ ፈቃድ (Search Warrant) ከእሰር ማዘዣ (Arrest Warrant) ጋር በአንድ ወረቀት ላይ ተደባልቆ በመምጣቱ ገና ከመታሰሬ ነው የሕጉ ነገር ያሳሰበኝ የጀመረው፡፡ ሕግ ስንማር የፍተሻ ፈቃድ ከእስር ማዘዣ ተለይቶ እንደሚመጣ፣ በፍተሻ ፈቃዱ ላይ ሊፈተሸ የተፈለገው ነገር በግልፅ ሊቀመጥ እንደሚገባ፣ ፍተሻ ከጠዋቱ 12 ሰዓት እስከ ምሽቱ 12 ሰዓት መከናወን እንዳለበት …ብንማርም ‹ፖሊስ› በታሰርኩበት ወቅት አንዱንም የሕግ አንቀፅ ላለማክበር ያሰበ በሚመስል መልኩ የፍተሻ ፈቃድን ከእስር ፈቃድ ሳይለይ፣ ፍተሻውን ከምሽቱ 12 ሰዓት በኋላ በመጀመር፣ በፍተሻው ምን ማግኘት እንደሚፈልግ የማይገልፅ የፍተሸ ፈቃድ በማሳየትና እኔ ስጠይቅም ለመናገር ፍቃደኛ ባለመሆን… ሕጉን‹ንዶ ንዶ› የኔን የግለሰቡን መብቶች በዜሮ በማባዛት ‹ወንጀልን የመከላከል ርምጃውን› ጀመረው፡፡ በፍተሻ ወቅት የሚፈለገው ነገር ምንነት አለመገለፁም ፖሊስ ‹ለጠረጠረኝ› ሕገ-መንግሥቱንና ሕገ-መንግሥታዊ ስርዓቱን በኃይል፣ በዛቻና በአድማ የመናድ ወንጀል እንደ ኤግዚቢት የያዛቸው ‹ማስረጃዎች› ምንነት ይገልጣቸዋል፡፡
በፍተሻ ወቅት ፖሊስ ከቤቴ በኤግዚቢትነት ከያዛቸው ‹እቃዎች› መካከል 90 በመቶው ገበያ ላይ ያሉ መጽሐፍት ሲሆኑ ከነዚሀም መካከል የPaulo Coelho “By the river paedra I set down and wept’ PV.I.Lenin ‘what is to be done’ የአፄ ሱስንዮስ ዜና መዋዕል፣ የፍቅረስላሴ ወግደረስ ‹እኛና አብዮቱ›… ጨምሮ ሌሎች መፅሀፍት የሚገኝበት ሲሆን፤ የተለያዩ የሙዚቃ ሲዲዎችም በኤግዚቢትነት ተይዘዋል፡፡
(የሚገርመው ፍተሻው ሕገወጥ መሆኑን ‹ለፖሊስ› በተደጋጋሚ ብናገርም ‹ብርበራ ከጀመርን በኋላ ልናቋርጥ አንችልም›፣ የሚያስፈልገንን ነገር አንተ ልትነግረን አትችልም… የሚሉ መልሶች በመስጠት ‹አዲዮስ ሕግ› የሚል አሰራር ከመከተላቸውም በላይ በቤቴ የተገኘ እንደ ‹አዲስ ራእይ› አይነት መፅሄቶችን የብርበራው መሪ የሆኑ ግለሰብ ለበታች መርማሪዎች ‹ተዉት እሱ የኛ ነው› የሚል አመራር እየሰጡ ግርምቴን አብዝተውት ነበር፡፡ ጉዳዩን አስቂኝ የሚያደርገው ደግሞ በፍተሸው ወቅት ቤቴ ውስጥ ከተያዙት ‹ኤግዚቢቶች› መካከል አንዱም እንኳን ለክስ ማስረጃ ሁነው አለመቅረባቸው ነው፡፡ ይህ ነው እንግዲህ ለህግ ት/ቤት ‹search is not a fishing expedition in which the police grabs every thing › ተብለን የተማርነው፡፡)
የእስርና የምርመራ ጊዜ ደግሞ ፖሊስ ሕጉን ለመጣስ ሆን ብሎ የተጋ በሚያስመስለው መልኩ ሕጉ ግድ ሳየሰጠው የፈለገውን ሲያደርግ የከረመበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ወቅት ነው ‹እኛ የሚያሳስበን የአንተ የአንድ ግለሰብ መብት ሳይሆን፣የሰማኒያ ሚሊዮን ሕዝብ ደህንነት ነው› የተባልኩት(ውዴ! Ayn Rand እንኳንም ይሔን ሳትሰማ ሞተች አላልሽም?)፡፡ በዚህ ወቅት ነው ‹የሽብር ሕጉን ጥርስ አውልቃችሁ አምጡ የሚለን ከሆነ ጥርስ ከማውለቅ ወደኋላ አንልም› ብሎ ፖሊስ ሕገ-መንግስቱንና የዜጎች መብትን በአንድ ላይ ሲቀብራቸው የተመለከትኩት፡፡ (‹ሕገ -መንግስቱ የሀገሩ ህጎች በሙሉ የበላይ ሕግ ነው› የሚለው የህገ መንግስቱ አንቀፅ በምድረ በጋ የተደነገገ እንደሆነ ግንዛቤ ለመጨበጥ ችያለሁ)፡፡ በዚህ ወቅት ነው፡ የፍርድ ቤቱ ትእዛዝ እንዲፈፀምልኝ ለጠየኩት ጥያቄ ‹ሂድ ከዚህ!የማነው?! ፍርድ ቤት ማነው እኛን የሚያዘው? ከፈለገች ዳኛዋ ራሷ ትፈፅምልህ…› የሚል መልስ ‹ከህግ አስከባሪ ፖሊስ› የተሰጠኝ፡፡
‹‹ምን አይነት ዘመን ነው ፣ የተገላቢጦሽ፤
አህያ ወደ ቤት፣ ውሻ ወደግጦሽ፡፡
ይሏል እንዲህ ነው፡፡ በዚህ ወቅት ነው፤ ምንም አይነት ሕጋዊ መብቶቼ ሳይነገሩኝ ‹ለምርመራ የተቀመጥኩበትና ብሎግ ላይ የተፃፉ ፅሁፎች የእኔ ‹የእምነት ክህደት ›ቃል እንደሆኑ ተደርገው መፃፍ እንዳለባቸው ትእዛዝ የተሰዘጠኝና በእምነት ክህደት ቃሌ ውስጥ ወይ ‹ጥፋተኛ ነኝ› ማለት አለያም ባዶውን መተው እንጂ ‹ጥፋተኛ አይደለሁም› የሚል ነገር መስፈር እንደማይችል የተረዳሁትና ‹ለምን?› ብዬ ስጠይቅም ‹ከበላይ አካል የመጣ ትዕዛዝ› እንደሆነ የተነገረኝ፡፡ (ማሬ፣ ዕድለኛ ባልሆን ኖሮ እንደ ‹አንድ› አባሪዬ ‹ህገ መንግስቱ ተከብሮ እያለ፣ ሕገ-መንግስቱ ይከበር ‹በማለቴ ጥፋተኛ ነኝ› ብለህ ፈርም ተብዬ መከራዬን አይ ነበር፡፡)በዚህ ወቅት ነው፤ መንግስቴ በመጀመሪያ ‹በሽብር ወንጀል› ባይጠረጥረኝም የፀረ-ሽብር ሕጉ አንቀፅ 14 በሚያዘው መሰረት ስልኬን ከግንቦት 2005 ዓ.ም ጀምሮ በመጥለፍ ንግግሬን ሁሉ ሊያደምጥ እንደነበር የተረዳሁትና ‹‹እንዴ ‹የሽብር ተግባራትን ለመፈፀም የማሴር ወንጀል› የተጠረጠርኩት ከታሰርኩ ከ23 ቀናት በኋላ ነው፤ ይሄም ፖሊስ እስከታሰርኩበት 23ኛ ቀን ድረስ በሽብር ጉዳይ ምንም አይነት ጥርጣሬ ያልነበረው ሲሆን ታዲያ ስልኬን አንድ አመት ለሚሆን ጊዜ እንዴት የፀረ ሽብር-ሕጉን ጠቅሶ ሊጠልፍ ቻለ?›› ብዬ ለጠየኩት ጥያቄ መልሱ ዝምታ እንደሆነ የተረዳሁት፡፡ (በነገራችን ላይ ስልኬ ለረጅም ጊዜ ቢጠለፍም ለማስረጃነት የቀረበብኝ ከአባሪዎቼ ጋር ‹ሻይ-ቡና እንበል እስኪ ብለን ያወራናቸው ወሬዎች ሲሆኑ፤ካንቺ ጋር ያውራናቸው ወሬዎች በማስረጃነት ባለመምጣታቸው ቅር መሰኘቴን በዚህ አጋጣሚ እገልፃለሁ፡፡)
ግርምቴ ብዙ ቢሆንም እንዳይሰለችሽ በማሰብ አንድ የመጨረሻ ግርምቴን ልንገርሽና ሌላ ጉዳይ ላይ እናልፋለን፡፡ የእስር፣ የምርመራ፣ የብርበራ … ሁሉ ዓላማ ተጠርጥረው የተጠረጠረበትን ወንጀል የሚያረጋግጥ መረጃ ለማግኘት ቢሆንም ከሁለት ወራት ለሚበልጥ ጊዜ፣ እጅግ የተራዘመ ምርመራ ተደርጎብኝ የቀረበብኝን ክስ ስመለከት ብዙ ነገሮች አስገረሙኝ፡፡ ቀዳሚው ጉዳይ የተከሰስኩበትን ‹የሽብር ተግባር ለመፈፀም የማሴር ወንጀል› በሚመለከት በምርመራ ወቅት አንድም ጥያቄ ያልቀረበልኝ ሲሆን፤ ይሄም ነገር ታዲያ የምርመራው አላማ ምን ነበር? እንድል አድርጎኛል፡፡ ሌላው ገራሚው ጉዳይ የሀገሪቱ ከፍተኛ የምርመራ ሂደት እንዲህ ቧልትና እያንዳንዱን እንቅስቃሴውን ከሕጉ ጋር በመላተም እንደሚያከናውን መገንዘቤ ነው፡፡ ታዲያ ‹ፖሊስ› ህግን ለመጣስ ካለው ትጋት የበለጠ ምን አስገራሚ ነገር አለ ውዴ?!
The Fridgegate Scandal እና ሌሎችም …
እኔ አሁን ደግሞ ወደ ክሴ ልውሰድሽ እስኪ ክሴን ባጭሩ ለማስረዳት ያክል (ምንም እንኳን ክሱ ግልፅ ባይሆንም፣ እኔ እንደመሰለኝ)፤ ‹የሽብር ቡድን በማቋቋም (ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ለማድረግ የሚልም ‹ይመስላል›)በሀገር ውስጥ የተለያዩ የሽብር ድርጅቶችን (ሰውን ለመግደል የሕብረተሰቡን ጤና ለከፍተኛ አደጋ ለማጋለጥ፣ እገታ ወይም ጠለፋ ለመፈፀም፣ ንብረት ለማውደም፣ በተፈጥሮ፣ በታሪካዊና በባሕላዊ ቅርሶች ላይ ጉዳት ለማድረስ፣ የህዝብ አገልግሎቶችን ለአደጋ ለማጋለጥ ወይም በቁጥጥር ስር ለማዋልና ለማበላሸት) በመዘጋጀት፣ በማሴር፣ በማነሳሳትና በመሞከር የሚለው የመጀመሪያውና ዋነኛው ክሴ ሲሆን፤ሁለተኛው ክሴ ደግሞ ያች የፈረደባት ‹ሕገ-መንግስትንና ሕገ-መንግስታዊ ስርዓቱን የመናድ ወንጀል ነው፡፡
ሁለቱም ክሶቼ የቅጣት ጣሪያቸው እስከ ሞት ድረስ መሆኑን መግለፄም አያስከፋሽም ብዬ አስባለሁ፡፡ (ዘጠኝ ሞት መጥቶ ከደጅ ቁሟል ቢለው፣ ስምንቱን ተውና አንዱን ግባ በለው› አለ የሞት ዳኛ፡፡ እንደዳኛው ‹አንዱን ሞት ግባ› ብዬ ከመጋበዜ በፊት ብዙ የማጫውትሽ ጉዳይ አለኝና አስኪ ተከተይኝ ውቤ)
ከሳሼ ‹የሽብር ተግባራትን› ልፈፅም እንደተዘጋሁና እንዳሴርኩ እንዲሁም ‹ሕገ-መንግስቱንና ሕገ-መንግስታዊ ስርዓቱን በሀይል ለመናድ› እንደሞከርኩ ለማስረዳት ያቀረቡልኝ የማስረጃ ዝርዝርን ስመለከት ግን የአሳሪዎችን ፍላጎት ‹ወዲህ› መሆኑን የተረዳሁት፡፡
በምርመራ ወቅት አንድም ጥያቄ ያልቀረበልኝ ‹የሽብር ድርጊት› ዋና ‹ወንጀሌ› ሁኖ ሲመጣ አሳሪዬ ጋር ያለው ፍላጎት ሙሉ ለሙሉ የወንጀል እንዳልሆነ ያስረዳኝ ሲሆን፤ በሰነድ ማስረጃነት ከቀረቡብን ብዙ ገራሚና አስቂኝ ‹ማስረጃዎች› መካከል ‹የሽብር ተግባራትን ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር በመሆን ለመፈፀም እንዳሴርን› ያስረዳል ተብሎ የቀረበው ዋነኛና ብቸኛ ማስረጃም ከጓደኛዬና አባሪዬ አንደኛ ተከሳሽ፣ ሶልያና ሽመልስ (ክሷ In Abesntia) እየታየ ያለችና በአንድ ቀጠሯችን ፖሊስ ከ Interpol ጋር በመሆን ለመያዝ ጥረት እያደረገ እንደሆነ የገለፁት በጥብቅ የምትፈለግ ‹አሸባሪ› ቤት በሌለችበት ፖሊስ ላደረገው ብርበራ ማቀዝቀዣ Fridge ዙሪያ ‹አገኘሁት› ያለው ግንቦት ሰባት የተባለ ፓርቲ በታህሳስ 2005 የወጣ የአባላት የውስጥ Newsletterና ቀኑ በሰነዱ ላይ ያልተመለከተ ሌላ የዚሁ ፓርቲ ሰነድ ነው፡፡
ውዴ ለመረጃ አንች ከእኔ ትቀርቢያለሽና ከላይ ስለጠቀስኩት ‹ሰነድ› ጉዳይ ብዙ ሰምተሻል የሚል ግምት አለኝ፡፡ እኔ ያለኝን መረጃ እና የዚህ ሰነድ ስለክስ ሒደቱ ሊኖረው ስለሚችለው አመላካችነት አንዳንድ ወሬዎችን እያመጣን እንተክዝ እስኪ፡፡
መቼም አሜሪካ ግሩም ሀገር ነው፡፡ ብዙ ነገሮች እንደቅሌት (Scandal) እየሆኑ ሲወጡ የምናይበት የቅሌቶች ሁሉ ቅሌት ድሞ የRichard Nixon ነው ‘The Watergatge scandal’ ይሉታል፤ ኒክሰን በ1972 ለተደረገው ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ መረጃ ለማግኘት በማሰብ በ Washington DC የሚገኘውን የዲሞክራቲክ ፓርቲ ICT ዋና መሥሪያ ቤት Watergate የተባለው ሕንፃ ውስጥ) እንዲበዘበዝ በማስደረጋቸውና ይሄም ድርጊታቸው በፕሬሱ ይፋ በመሆኑ ኒክሰን ከስልጠናቸው ተዋርደው እንዲለቁ ሆነ፡፡
የWatergate ብዝበዛን ተከትሎ ብዙ ሐረጎች ለብዙ ሁነቶች መግለጫ በመሆን ይቀርቡም ጀመር ለምሳሌ ‘The Watergate Burglars’ ‘The Saturday Night Massacre:- ‘United States Vs Nixon’…. (የእያንዳንዷን ዝርዝር Google እያደረግሽ እንደምታይው ተስፋ አለኝ አበባዬ)፡፡ ከዛም በኋላ የተለያዩ ቅሌቶችን ከWatergate ጋር እያያያዙ መጥራት የተለመደ ነው፡፡ አሁንም ሌላ ምሳሌ ‘The Monicagate’ የፕሬዚዳንት ክሊንተንን የወሲብ ቅሌት ለመግለጽ)፣( ‘The Nipplegate’ (በ2003 ዓ.ም ጃኒት ጃክሰን በLive የቴሌቪዥን የሙዚቃ ዝግጅት ላይ ባልታሰበ ሁኔታ ያጋጠማትን የጡት ጫፍ (Nipple) መራቆትና በቴሌቪዥን የቀጥታ ስርጭት ታሪክን የቀየረ ሁነት ለመግለፅ)፤
ይሔን ሁሉ ማለቴ ወዴት ለመሔድ አስቤ እንደሆነ ሳትረጂው አትቀሪም ፍቅር፡፡ ከላይ ወደጠቀስኩልሽ ግንቦት 7 የተባለ ፓርቲ ሰነድ ጓደኛችን ቤት ተገኝ ስለመባሉ ጉዳይ ላስረዳሽ አስቤ ነው፡፡ ተገኘ የተባለው ሰነድ ላይ ጓደኛችን ወክለው ቤቷን ሲያስፈትሹ የነበሩት እናቷ ‹ይህ ሰነድ ፖሊስ ከፋይሉ ጋር ይዞት የመጣው ሰነድ ነው፡፡ እዚህ ቤት የተገኘ አይደለምና እዚህ ቤት ተገኘ ብዬ ልፈርም አልችልም› ማለታቸው በሰነዱ ላይ በግልጽ የተመለከተ ሲሆን፤ ሰነዱ ተገኘ የተባለበት ቦታ ደግሞ የጉዳዩን አስገራሚነት ያንረዋል- ማቀዝቀዣ (Fridge)! (በነገራችን ላይ ፖሊስ የወንጀል ‹ማስረጃ› ከውጪ ይዞ ቤት ውስጥ በመጣል ‘Eureka’ ‹ማስረጃ› አገኘሁ የሚልበት ልማድ አዲስ አይደለም፤ በኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ጉዳይ የተከሰሱ ብዙ ሰዎች የዚህ ዓይነት ‹ፖሊስ አመጣሽ› ማስረጃዎች ሰለባ መሆናቸውን እያነበብን/እየሰማን ነው የጎለመስነው፡፡ ፖሊስን ወደቤታቸው ፈትሸው ከማስገባት ጀምሮ የተለያዩ ፖሊስን የመጠበቅ አስቂኝ ተግባራትን በቤት ብርበራ ወቅት እንደሚያከናውኑ ስንለውም ኖረናል፡፡ አስቢው እስኪ ውዴ፤ ሕዝብ ፖሊስን ሲጠብቀው የሚኖርበት ሀገር!)
ለማንኛውም ይህ ‹ Fridge ማስረጃ› ‹አገኘሁ› የሚለው የፖሊስ ተግባር ነው… ‘The Fridgegate Scandal’ እንድል ያደረገኝ፡፡ እስርም፣ ክስም፣ ‹ማስረጃም›…. ከአሳሪዬ በኩል መምጣቱ ‹ፍርድም› ከአሳሪዬ በኩል ሊመጣ ይችላል የሚል ስጋት ውስጥ ቢከተኝም ተስፋ አልቆርጥም! ወዳጄ ‘The Fridgegate scandalን’ እንደ አንድ የክስ ሒደቱ ማሳያ ማቅረቤ ‘The Fridgegate Burgalrs’ ለፍትሕ ይቀርባሉ ብዬ በማሰብ አይደለም ወይም በባለስልጣኖቻችን መካከል ‘The Renaissance Massacre’ ተከስቶ ስልጣን ይለቃሉ የሚል ቅዠትም የለኝም፤ይልቁንም (በክርክሩ ሒደት የምናየው ቢሆንም) የቀረቡብን የሰነድ ማስረጃዎች አስቂኝነትና ምን እንደሚያስረዱ ካለመታወቃቸው አልፎ እንዲህ የአሳሪዎቻችን የቅሌት ተግባራት ውጤት መሆናቸውን ከ Alexander Hamilton የFederaliot Paper Number 78:
“The Judiciary is ‘beyond comparison the weakest of the three department of power”
ቃል ጋር አንድ ላይ ስመለከተው ‹ማስረጃ› ፈጣሪው› እና ጠንካራው አሳሪያችን ‹ደካማውን› ፍርድ ቤት እንዳይጫነው ብሰጋ ነው፡፡ ቢሆንም ግን ሁሌም ተስፈኛ ነኝ፡፡ ማሬ በሕግ ቋንቋ (በልሳን) ትንሽ አውርተን ወደ ሌላ ጉዳያችን እንሂድ፡፡ ያን ረጅም የምርመራ ሂደት አልፈንና ሕግ-አስፈፃሚው ሂደቱን እንዲያስጠብቁ በሕግ-አውጭው የወጡትን የስነ-ስርዓትና መሰረታዊ የመብት መጠበቂያ (Procedual and substantive) ሕጎችን አንድ በአንድ እየሰባበረ ለሕግ ተርጓሚው አካል ያቀረባቸውን ‹የወንጀል ድርጊት ማሳያ ማስረጃዎችን› በሕግ ትምህርት ቤት ‘The Fruits of Poisonous free’ የተባሉት ሲሆኑ፤ ተስፋዬም ከሶስቱ የመንግሥት አካላት ደካማ የተባው ሕግ ተርጓሚው አካል የቀረበለት ነገር በትክክል ‹ፍሬ› እንዳልሆነ ይገነዘባል የሚል ሲሆን፤ ያ ካልሆነም ‹ፍሬው› ከተመረዘ ዛፉ ለሕግ ተርጓሚው አካል በግድ ካልገመጥ አይለውም አይባልም፤ ዛፉን ለመመረዝ አካል ፍሬውን ለማስገመጥ አይሰንፉምና፡፡ ፍቅር! ለማንኛውም ተስፋ ጥሩ ነው፡፡
መንግስቱ ኃይለማርያም ደሳለኝን (MHD) አየኋችሁ
የኔ እመቤት! እውነት እውነት እልሻለሁ እንደ መታሰር ያለ አስተውሎትን የሚያሳድግ ነገር የለም፡፡ ምክንያቴን ከነማስረጃዬ አቀርባለሁ፡፡ ያኔ በዞን ዘጠኝ እያለሁ (ከመታሰሬ በፊት) ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝን አጠር አድርገን ‘HMD’ በሚል አፅርሆት እንጠራቸው ነበር፡፡ መታሰሬ ግን ዓይኔን አበራልኝና የእስከዛሬው አጠራራችን የፊደል መፋለስ እንዳለበት ለመረዳት ችያለሁ፡፡ እንዴት?
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስለሽብር፣ ስለእስርና ስለመንግስታቸው አቋም በቅርቡ ተጠይቀው የሰጡትን ምላሽ በኢቲቪ ተመለከትኩ፡፡ ‹‹እነዚህ አሸባሪዎች ከአስመራ እስከ ሞቃዲሾ የተዘረጋው የሽብር ሰንሰለት አካላት ናቸው (በነገራችን ላይ በቅርቡ የቀድሞው የጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንት ከደቡብ ሱዳን ጁባ ተይዘው መምጣታቸውን ተከትሎ የሽብር ሰንሰለቱ ከአስመራ-ሞቃዲሾ-ጁባ ተለጥጦ ሶስት ማዕዘን መስራቱን መንግስት እየገለፀ ነው) ጋዜጠኛ ነኝ፣ ብሎገር ነኝ እያሉ የሽብር ዓላማን ማንገብ አይቻልም፡፡ እናንት ጋዜጠኞችም ተጠንቀቁ….›› አይነት ዱላ ቀረሽ ዛቻ ሲያሰሙ ተመልክቼ እንደሰውየው ‹ ኃይለማርያም አሁንስ መንግስቱን መንግስቱን መሰልከኝ ማለቴ አልቀረም፡፡ ለዛም ነው ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ መንግስቱ ኃይለማርያም ደሳለኝን (MHD) የሚለውን ስያሜ አፌ ላይ አልጠፋ ያለው፡፡
እንደዱሮው ‹ይሄ በፍርድ ቤት የተያዘ ጉዳይ ስለሆነ አስተያየት መስጠት አልፈልግም› ማለት ቀረና እንደዳኛ ግራና ቀኝ የተቀመጡትን ጋዜጠኞች እየገላመጡ ቢሯቸው ውስጥ ፍርድ ስጡኝ፡፡ ሌላው ሁሉ ይቅር በሕግ ፊት ነፃ ሆኖ የመገመት ሕገመንግስታዊ መብቴን ያክብሩ አላልኩም፡፡ ባይሆን የቀረበብኝን ‹ማስረጃ› ተመልክተው ፍርድዎችን ይስጡም አልልም፡፡ ግን ግን ‹ለባንዲራ ፕሮጀክታችን› (የሕዳሴው ግድብ) ማሰሪያ ይሆን ዘንድ የሁለት ወር ደመወዜን ለቦንድ መግዣ (ምንም እንኳን ለቦንድ ግዢ ጠቅላላ ክፍያ ሳልጨርስ ከስራ በመሰናበቴ ምክንያት ደመወዜ ቢቋረጥም) መስጠቴን እንደውለታ ቆጥረው በቤተ-መንግስት የዘረጉት ‹የፍርድ ችሎት› ላይ ምህረት ቢያደርጉልኝ ምን አለ? ‹ወርቅ ላበደረ ጠጠር፣ እህል ላበደረ አፈር› ይሰጡታልን?
ውቤ! ለማንኛውም በጠቅላይ ሚኒስትሩ የተበየነብንን የሽብርተኝነት ካባ በፍርድ ቤት እንደማይፀናብን ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
‹የነሲቡ ችሎት›
አፈ ንጉስ ነሲቡ መስቀሉ ከ1874 ዓ.ም ጀምሮ ወደ 30 ዓመት ለሚሆን ጊዜ በዳኝነት የተለያዩ የኢትዮጵያን ነገስታት ያገለገሉ ሲሆን ፍርዳቸው እጅግ ከባድና ጠንካራ ስለነበር በዘመኑ ‹እባክህ ከነሲቡ ፊት አታቁመኝ› እየተባለ ይለመን እንደነበር መርስኤ ሀዘን ወልደቂርቆስ በዓይን ያዩትን፤ በጆሮ የሰሙትን፤ ከትበው ይነግሩናል፡፡ በተመሳሳይ ጉዳይ በንጉሱ ዘመን አርሲ፣ አሰላ ላይ እጅግ ጨካኝ ደኛ ተሹመው ፍርዳቸው ከባድ ከመሆኑ የተነሳ ‹አቤት አቤት፤ የአሰላው ፍርድ ቤት› እስከመባል ደርሶ እንደነበር አሁንም ማስረጃችን ታሪክ ነው፡፡
ውዴ! ይሔን የምፅፍልሽ የእኛው ዘመንን ‹የነሲቡ ችሎት› አስመለክቶ ትንሽ ነገር ብዬሽ ደብዳቤዬን ልቋጭልሽ በማሰብ ነው፡፡ አዋጅ ቁጥር 652/2001 (የፀረ-ሽብር አዋጅ) ከወጣበት ጊዜ ጀምሮ በሽብር ጉዳዮች ላይ ስልጣን (Juridiction) ያለው የፌዴራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት እንደሆነ በመደንገጉ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ተኛ ወንጀል ችሎት የተለያዩ በፀረ-ሽብር ሕጉ የተከሰሱ ግለሰቦችንና ቡድኖችን ጉዳይ እያየ የቆየ ሲሆን፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ‹የፀረ-ሽብር ሕጉ ሰለባዎች› እየተበራከቱ በመሔዳቸው ምክንያት 4ተኛውን ወንጀል ችሎ ለማገዝ በማሰብ 19ኛ ወንጀል ችሎ የሽብር ጉዳዮችን በማዬት ላይ ይገኛል፡፡
በፀረ ሽብር ሕጉ ተከሰውኖ 4ተኛ ወንጀል ችሎት ቀርበው ነፃ የወጡ (Acquit) ሰዎች ብዛት ለጊዜው ለማወቅ ባልችልም እጅግ በጣም ትንሽ እንደሆኑ ግን እርግጠኛ ነኝ፡፡ ይህ የሆነው ችሎቱ ከሌሎች ችሎቶች የተለየ በመሆኑ እንዳልሆነም አስባለሁ፡፡ ይልቁንም ችሎቱ የሚይዛቸው ጉዳዮች በፀረ-ሽብር ሕጉ አግባብ ለማየት ስለሚገደድ ነው፡፡ መቼም የፀረ-ሽብር ሕጉን አሳፋሪነትና ጅምላ ጨራሽነት ላንች እንዳዲስ በመንገር ጊዜሽን አላባክንብሽም፡፡ ለዛም ነው በዚህ ዘመን ‹እባክህ ከ4ተኛ ወንጀል ችሎት ፊት አታቁመኝ› ወይም ‹አቤት አቤት፣ 4ተኛው ወንጀል ችሎት› ብንል ብዙም የማያስገርመው፡፡ የፀረ-ሽብር ሕጉ ከሚሰጠው ሰፊና ጠቅላይ የሆነ የወንጀል ትርጉም አንፃር ከልብ ወለዳዊው ‘Moratorium on the Brain’ አዋጅ ጋር በተነፃፃሪ መቆም የሚችል ከመሆኑም በላይ በሽብር ጉዳይ የተሰየወን ችሎትም እጅግ አሳፋሪ ያደርገዋል፡፡
እንግዲህ የእኛም ጉዳይ የ4ተኛ ወንጀል ችሎት እህት ከሆነው 19ነኛ ወንጀል ችሎት እየታዬ የሚገኝ ሲሆን የፀረ-ሽብር ሕጉም ‹ሰለባ› ፍለጋ በችሎታችን ተገኝቷል፡፡ እንግዲህ አበባዬ ጉዳያችን በፀረ-ሽብር ሕጉ ከመታየቱ ጋር ተያይዞ ስራ አስፈፃሚው አካል ‹ማስረጃ› ፈጥሮ የከሰስን መሆኑ ነው ችሎቱን ‹የነሲቡ ችሎት› ያደረገው፡፡ ለማንኛውም ግን ይሄን ስታነቢ ታዲያ ‹ከአንበሳ መንጋጋ፣ ማን ያወጣል ስጋ› ብለሽ ተስፋ እንደማትቆርጪ አምናለሁ፡፡ እኔና አንች እኮ ተሸንፈን አናውቅም ውዴ፡፡ ሁሌም ማሸነፍ፣ ሁሌም ሌላ ተስፋ ማድረግ፣ ሁሌም ደስተኛ መሆን፣ ሁሌም መዋደድ የሕይወት ግባችን አይደለምን ? ታዲያ ይችን ክስ በድል እንዳንወጣት ማን ያግደናል? ምን አልባት አሳሪያችን፡፡ Hamilton በድጋሚ ጠቅሼልሽ ተስፋችንን አለምልመን እንለያይ፡
‘The Judiciary (…) has no influence over either the sword or the purse (…) It may truly be said to have neither force nor will, but merely judgement’
Amen!

ያንችው ዘላለም
ከብዙ ፍቅር ጋር!


እስር ቤት የሚገኙት የሽዋስ አሰፋ፣ ሀብታሙ አያሌው፣ አብርሃ ደስታና ዳንኤል ሺበሽ በጠበቃቸው እንዳይጎበኙ ተከለከሉ

Aug29,2014
Habtamu abrhayeshiwas danielእነ የሽዋስ በጠበቃቸው እንዳይጎበኙ ተከለከሉ በማዕከላዊ እስር ቤት የሚገኙት የሽዋስ አሰፋ፣ ሀብታሙ አያሌው፣ አብርሃ ደስታና ዳንኤል ሺበሽ በጠበቃቸው እንዳይጎበኙ መከልከላቸውን የሰማያዊ ፓርቲ የህግ ጉዳይ ኃላፊ አቶ ይድነቃቸው ከበደ ለነገረ ኢትዮጵያ ገለጹ፡፡ የማዕከላዊ ምርመራ ታሳሪዎቹ በሳምንት ሁለት ቀን (ረዕቡና አርብ) በጠበቃቸው እንዲጎበኙ ፈቅዶ የነበር ቢሆንም ጠበቃ ተማም አባ ቡልጉ ደንበኞቻቸውን ለማግኘት በተደጋጋሚ ወደ ማዕከላዊ አቅንተው ሳያገኟቸው ቀርተዋል ተብሏል፡፡ ተማም አባ ቡልጉ ወደ ማዕከላዊ ባቀኑባቸው ቀናት ‹‹ሌላ ቀን ታገኛቸዋለህ፣ ስብሰባ ላይ ነን›› እና የመሳሰሉትን ምክንያቶች እያቀረቡ ቀኑን ሙሉ ሲያስጠብቋቸው እንደነበርና በተለይ በዛሬው ቀን ነሃሴ 23 ደንበኞቻቸውን ለማግኘት እየጠበቁ ከዋሉ በኋላ ‹‹ከፈለክ ችሎት ላይ ታገኛቸዋለህ፡፡ ከዚህ ማግኘት አትችልም›› ተብለው እንደተመለሱ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ‹‹ታሳሪዎች በጠበቃቸው፣ በኃይማኖት አባታቸው፣ በጓደኛና በዘመድ የመጎብኘት መብት አላቸው፡፡ በሳምንት ይህን ቀን ተብሎ በህግ አልተወሰነም፡፡›› በሚል በሳምንት ሁለት ቀን ብቻ ነው የሚጎበኙት መባሉም ስህተት ነበር ያሉት አቶ ይድነቃቸው ‹‹ጭራሹን እንዳይጎበኙ መደረጉ ደግሞ ሆን ተብሎ የተፈጸመ ህገ ወጥ ድርጊት ነው›› ሲሉ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡

Friday, August 29, 2014

የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ ፈተና

August29,2014
betre-yakob
Betre Yacob – president of Ethiopian Journalists Forum
(ኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ ጋዜጣ የነሐሴ 14 እትም)
“የኢትዮጵያ መንግስት በግል ፕሬሱ ላይ የተቀነባበረ የጥፋት ዘመቻ ጀምሯል፡፡ ያሁኑ እርምጃ ቀደም ሲል ከተወሰዱት አስከፊ ፀረ-ፕሬስ እርምጃዎች የሚለየው ከ2007ቱ ምርጫ በፊት የተጀመረ መሆኑ ብቻ ነው፡፡
በዚህ በአሁኑ እርምጃ አንድ የጋዜጠኞች ማኅበርን ጨምሮ፣ በአንድ የጦማሪያን ስብስብ ላይ እና በአምስት መፅሔቶች እና አንድ ጋዜጣ ላይ ያነጣጠረ ነው፡፡ እርምጃው እንደተለመደው ሕገ መንግስታዊ ሽፋን በመስጠት የተካሄደ ከመሆኑም በላይ በተለያዩ መንገዶች የተቀነባበረ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ገና ይቀጥላልም ተብሏል፡፡
መንግሥት የግል ሚዲያው ላይ ዘመቻ የጀመረው በህትመት ዋጋ መጨመር በቋፍ ላይ ያለውን ፕሬስ በማፈንና የነፃነት በሮችን ሙሉ በሙሉ በመዝጋት ጭምር ነው፡፡
መንግሥት የ2007ቱን ምርጫ እንደ ምንም ብሎ ለመሻገር ባለው ከፍተኛ ጉጉት የተነሳ ጋዜጠኞችን በክስ በማዋከብ ላይ ይገኛል፡፡ መንግሥት ለህገወጥ የሽበባ ተግባሩ- ህጋዊ ሽፋን ለመስጠት ሲሞክር እየተስተዋለ ነው፡፡
የቀድሞው ጠ/ሚ አቶ መለስ ዜናዊ በህይወት በነበሩበት ጊዜ በዘዴ ህግ አጣጣስን ያውቁበት ስለነበር በሚወ ስዷ ቸው እርም ጃዎ ች እና በሚያቀርቧቸው ምክንያቶቹ በመጠኑም ቢሆን የሚደናገሩ ወገኖች አይጠፉም ነበር፡፡ አሁን ሥልጣን ላይ የወጣው ኃይል ግን አካሄዱ ያልተጠና የውር-ድንብር በመሆኑ ስህተቱን ለመሸፈን ተቸግሯል፡፡ ግመል ሰርቆ ተደብቆ ሆኖበታል፡፡
መንግሥት ህገ-መንግስቱ በመጣስ፣ ዓለም አቀፍ ህግ ባለማክበር፣ የሞራል ልዕልናውን ከማጣቱ ባሻገር፣ ከአንድ መንግስት ፍፁም የማይጠበቅ ተግባር እየፈፀመም ይገኛል፡፡
በተለይም እየተጠናቀቀ በሚገኘው ዓመት ያከናወነው የጥፋት ዘመቻ የዓለም መነጋገሪያ እንዲሆን አድርጎታል፡፡ ሦስት ጋዜጠኞችን (ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ፣ ጋዜጠኛ አስማማው ኃ/ጊዮርጊስ እና ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ) እና የዞን 9 ጦማሪያንን በሽብርተኛነት ከመወንጀል አልፎ በተለያዩ የፖለቲካ የክርክር መድረኮች እርቃኑን የሚያስቀሩትን ትንታግ ፖለቲከኞች ወደ እስር ቤት ርውሯል፡፡ ይህም አልበቃ ብሎ የሀሰት ጥናትን እና ዘጋቢ ፊልምን በሽፋንነት በመጠቀም ፕሬሱን የመጠራረግ ዘመቻውን አጠናክሮ ቀጥሏል፡፡
በዚህ ዓይን ያወጣ ዘመቻ በነፃው ፕሬስ ውስጥ ጉልህ አስተዋፅኦ ሲያበረክቱ የነበሩ በርካታ ጋዜጠኞች ከመድረኩ እንዲገለሉ ደርጓል፡፡ ለበርካታ ዓመታት በሙያው ውስጥ የነበሩና ሌሎች ብዙ ይሰራሉ ተብለው የሚጠበቁ ወጣት ጋዜጠኞች የስደትን መንገድ እንዲከተሉ ተዳርገዋል፡፡ ለስደት ከተዳረጉት ጋዜጠኞች በርካቶቹ የፖለቲካ ጉዳዮችን በመዘገብ የሚታወቁና አስቸጋሪውን የመንግስት ሽበባ ተቋቁመው ኃላፊነታቸውን ሲወጡ የነበሩ ናቸው፡፡ አንዳንዶችም ከሀገር ውስጥ ሚዲያዎች ባሻገር ለውጭ የሚዲያ ተቋማት የሚዘግቡ ጋዜጠኞች ሲሆኑ፣ ከነዚህ መካከል ጋዜጠኛ በትረ ያዕቆብን በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል፡፡
አሁን የቀሩት ጥቂት አልሞት ባይ ተጋዳይ ጋዜጠኞችም አጣብቂኝ ውስጥ እንዲገቡ ተደርጓል፡፡ የዚህች ሀገር ጋዜጠኝነትም ወደ ቁልቁለት እንዲወርድ ተፈርዶበታል፡፡ ከእንግዲህ በዚህች አገር ጋዜጠኝነት የተከበረ ሙያ ሳይሆን፣ በሽብርተኝነት የሚያስፈርጅ ሰዎችን ለከባድ እንግልት እና ስቃይ የሚዳርግ ሙያ እንዲሆን በመንግሥት ተፈርዶበታል፡፡
መንግሥት፣ በጣር ላይ ያለውን ነፃ ፕሬስ ቁልቁል ለመግፋት ቆርጧል፡፡ በህገ- መንግስቱ የደነገገውን አንቀፅ 29 እንኳን ሰርዞታል ወደሚባልበት ደረጃ ደርሷል፡፡ መንግሥት በጉልበቱ እንጂ በሃሳብ የበላይነቱ መቀጠል ተስኖታል፡፡ መንግሥት ቀደም ሲል ዜጠኛና አክቲቭስት እስክንድር ነጋ፣ ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ፣ ጋዜጠኛና መምህርት ርዕዮት ዓለሙ፣ ጋዜጠኛ የሱፍ ጌታቸው እና ሌሎችንም ማሰሩ የሚታወስ ሲሆን፣ ዓይን ያወጣ ፕረሱን የማፈን እርምጃውን የጀመረው ግን የዞን ዘጠኝ ጦማሪያንና ሶስቱን ጋዜጠኞችን በግፍ በማሰር ቢሆንም፣ የሽብርተኝነት ድግሱን የጠነሰሰው እና በዋነኝነት ኢላማው አድርጎት የነበረው ግን አዲስ በተመሠረተው የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ (ኢጋመ) ላይ ነበር፡፡
ኢጋመ በዚህ ዓመት በጥቅምት ወር የተመሠረተው በአንድ መሠረታዊ እና አንገብጋቢ ምክንያት እንዲሁም በሁለት ወቅታዊ ምክንያቶች ነበር፡፡ ይህ መሠረታዊ ምክንያት የሀገሪቱ ጋዜጠኞች መብት አለመከበር፣ ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት ሕገ-መንግሥቱ በሚፈቅደው መልኩ አለመረጋገጥ እና ስመጥር የሀገሪቱ ጋዜጠኞች በሀሰት የሽብር ውንጀላ በየእስር ቤቱ የሚማቅቁበት ሁኔታ ተጠናክሮ መቀጠል ነበር፡፡ ከዚህ አንፃር በጥቅሉ ማኅበሩ ያለፉት 23 ዓመታት የጋዜጠኞች ብሶት የወለደው ነው ለማለት ያስደፍራል፡፡ ለማኅበሩ መመስረት ወቅታዊ ምክንያቱ ደግሞ በጥቅምት ወር 2006 መጀመሪያ ላይ የአፍሪካ ሚዲያ ፎረም እዚህ አዲስ አበባ ላይ ሲካሄድ የሀገሪቱን ነፃ ጋዜጠኞችን በአብዛኛው ያገለለ እና የሀገሪቱን አሳሳቢ የፕረስ ሁኔታ ያላገናዘበ በመሆኑ በተፈጠረ ቁጭት እንዲሁም በተመሳሳይ ወቅት በጋዜጠኛ ኤፍሬም በየነ ላይ በተከሰተ ዘግናኝ የመኪና አደጋ ጋር የተያያዘ ስለ ነበር በሀገሪቱ ህገ-ወጥ የጋዜጠኞች እስር እና የመብት ጥሰት ሲብከነከኑ የነበሩ ጋዜጠኞች ተሰባስበው ማኅበሩን ለመመስረት ጥረት አድርገዋል፡፡
ማኅበሩ ከተመሠረተ በኋላ ግን በመንግሥት እና ፕሬሱን እንመራዋለን በሚሉ ጥቅመኛ “ጋዜጠኞች” ካምፕ ውስጥ ከፍተኛ መደናገጥ ተፈጥሮ ነበር፡፡ በተለይም ማኅበሩና ዞን ዘጠኝ ከዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተቋማት ጋር ተመጋግበው ሊሰሩ ይችላሉ የሚለው ከልክ ያለፈ ስጋት ክፉኛ አስበርግጓቸው ነበር፡፡ በወቅቱም የመንግስት የደህንነት ኃይሎች የዞን 9 አባላት ላይ ከማኅበሩ ጋር ያላቸውን ግንኙነት እንዲናገሩ ማስፈራሪያና ወከባ ሲፈፅሙ ቆይተዋል፡፡
ከዚህ ጎን ለጎን ማኅበሩ ሌሎች የጋዜጠኛ ማኅበራትን በሩቁ ሲሸሹ የነበሩ በርካታ የነፃው ፕሬስ አባላትን መማረኩና ከጎኑ ማሰለፍ መቻሉ እንዲሁም በወቅቱ የታየው ጠንካራ የትብብር መንፈስ መንግስትን እንቅልፍ አሳጥቶት ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ከጅምሩ ማኅበሩ ይበልጥ እንዲፈራ ያደረገው በጋዜጠኞች የተቋቋመ ከመሆኑ በላይ በአጭር ጊዜ ውስጥ በዓለም አቀፍ ተቋማት ተቀባይነት ማግኘቱና አብረው ለመስራት ያሳዩት ተነሳሽነት ነበር፡፡ ከዚህም ባሻገር በሀገር ውስጥ የሚገኙ ኢምባሲዎች እና ታዋቂ ግለሰቦች እምነትና ተቀባይነት ያገኘ የሙያ ማኅበር በመሆኑ ነው፡፡
የሀገሪቱን ፕሬስ በማፈን የሚታወቁ ጥቅመኛ “ጋዜጠኞች” በማኅበሩ ላይ መንጫጫት የጀመሩት ወዲያው የማኅበሩ መመስረት በተበሰረበት ማግስት ነበር፡፡ ምክንያቱም በጋዜጠኛው ሥም የሚሰበስቡትን ገንዘብ ስለሚያስቀርባቸው እና ለጋዜጠኞች ጥቅም በእውነት አለመቋቋማቸውን ስለሚያሳብቅባቸው ነው፡፡ በተመሳሳይ መንግስት የሀሰት ማኅበራቱን በሽፋንነት በመጠቀም ሙሉ ትኩረቱን በአዲስ መንፈስና በተደራጀ መልክ በመጣው ማኅበር ላይ በማሳረፍ መንቀሳቀስ ጀመረ፡፡ መንግስት በማኅበሩ የምስረታ የመጀመሪያዎቹ ሳምንታት ሶስት “የጋዜጠኛ” ማኅበራት አመራሮችን በመጠቀም በቴሌቭዥን ውንጀላ እና ማስፈራሪያ ተጀምሮ ነበር፡፡ ውንጀላና ማስፈራሪያውም የአዲሱን ማኅበር አመራር አባላት በሽብርተኝነት እና በሀገር ከሀዲነት በመፈረጅ ጋዜጠኞች ወደ ማኅበሩን እንዳይቀላቀሉ አስጠንቅቀዋል፡፡
ቀጥሎም ለማኅበሩ መመስረት የበኩሉን ሚና ሲጫወት በነበረው የማኅበሩን ፕሬዝዳንት ጋዜጠኛ በትረ ያዕቆብ ላይ ውንጀላ እና ወከባ ወደ መፈፀም ገብቷል፡፡ እዚህ ላይ ፕሬዝዳንቱን በተመለከተ የሚያትት ትልቅ ጥራዝ የሀሰት ሠነድ በማዘጋጀት የአንድ ማኅበር ፕሬዝዳንት በነበሩት ግለሰብ አማካኝነት የተካሄደው የስም ማጥፋትና የማስፈራራት ዘመቻ በዋናነት የሚጠቀስ ነው፡፡ የማኅበሩ የህዝብ ግንኙነት በነበረው ጋዜጠኛ ዘሪሁን ሙሉጌታ ላይ ይካሄድ የነበረው ወከባ በተለይ የማኅበሩን ምስረታ በተመለከተ ከማኅበሩ ፕሬዝዳንት ጋር በመሆን ለቪኦኤ እና ለሌሎችም የሀገር ውስጥ የመገናኛ ብዙሃን የሰጠውን መግለጫ ተከትሎ የደህንነት ኃይሎች ክትትል ሥር መውደቁን ለጓደኞቹና ለሥራ ባልደረቦቹ ሲናገር ነበር፡፡ በዚህ የተነሳም በማኅበሩ ውስጥ የተሰጠውን ኃላፊነት ለተወሰነ ጊዜ በአግባቡ እንዳይወጣ ተደርጓል፡፡
በዚህ መልኩ በማኅበሩ አመራሮች ላይ የተጀመረው ውንጀላ እና ወከባ እየተጠናከረ መጥቶ መጋቢት 24 በታተመው የአዲስ ዘመን ጋዜጣ “ገፅ 3” እና አይጋ ፎረም ላይ የማኅበሩን አመራሮች ስም አንድ ባንድ በመዘርዘር ሁከት ለመፈፀም በመዘጋጀት፣ አመፅ በመቀስቀስ፣ ለሽብር ተልዕኮ ከውጭ ኃይሎች ጋር በመደራጀት፣ መጭውን ሀገር አቀፍ ምርጫ ለማወክ በመዘጋጀት ወዘተ በሚል በአሸባሪነት ሊፈርጅ ችሏል፡፡ ይህም በትክክል መንግስት የማኅበሩን አመራሮቹን በሽብርተኝነት ወደ እስር ቤቶቹ ለመወርወር የመጨረሻ የዝግጅት ምዕራፍ ላይ ስለመድረሱ በግልፅ አመላካች ነበር፡፡
ከመጋቢት 24ቱ የአዲስ ዘመን ውንጀላ በኋላ የነበሩት ጊዚያት ለማኅበሩ አመራሮች ፈታኝ የነበሩ ሲሆን፣ በተለይም ቁልፍ ሚና በነበራቸው ላይ የደህንነት ኃይሎችን በመላክ የማስፈራራት እና ማዋከብ ስራ በስፋት ሲካሄድ ቆይቷል፡፡ ከአካልና የስልክ ማስፈራሪያዎች እንዲሁም ገደብ የለሽ ከሚመስለው ክትትል ባሻገር በተለያዩ መንገዶች ሲካሄዱ የነበሩ ውንጀላዎች የእስር ድግሱ እየተደገሰ ስለመሆኑ በግልፅ የሚያሳይ ነበር፡፡ ይህን ታኮ “የቀለም አብዮት ሰለባዎች” በሚል በኢቲቪ የተላፈው ዘጋቢ ፊልም የሚዘነጋ አይደለም፡፡ ይህ በመንግስት አፈቀላጤ ሚዲያዎች ሲካሄድ የነበረው ዘመቻ በማኅበሩና በፕሬሱ ላይ የተቀነባበረ አፈና እንደሚካሄድ አመላካች ነበር፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ የማኅበሩ አመራር አባላት ማኅበሩን በሁለት እግሩ ለማቆም እውቅና ወደ ሚሰጠው የመንግስት አካል በመሄድ ተደጋጋሚ ሙከራ ቢያደርጉም፣ የተለያዩ ምክንያቶችን በመደርደር ማኅበሩ ወደ ህጋዊ መስመር እንዳይገባ የበኩላቸውን ጥረት አድርገዋል፤ ጥቃቅን ጉዳዩችን ከህግ ውጭ በቅድመ ሁኔታነት በማቅረብ እውቅና የሚገኝበትን እድል እንዲዘጋና የአመራር አባላቱ በሽብርተኝነት ተወንጅለው እንዲታሰሩ ሁኔታዎችን ማመቻቸት ተያይዘውት ነበር፡፡
ምንም እንኳን መንግስት ማኅበሩን ጠልፎ ለመጣል ተግቶ ቢሰራም፣ የማኅበሩ አመራር አባላት ግን ቁርጠኛና አይበገሬ ነበሩ፡፡ እንደውም ከእውቅና ጥያቄው ጎን ለጎን የዓለም ፕሬስ ቀንን ለማክበር መጠነ ሰፊ ስራዎችን መስራት ጀምረው ነበር፡፡ ይሁን እንጅ በዚህ መሐል ሦስት እውቅ ጋዜጠኞች እና የዞን ዘጠኝ ጦማሪያን ከያሉበት ተለቃቅመው ታሰሩ፡፡ ይህን እስር ተከትሎ የመንግስት ደጋፊ የሆኑ ሚዲያዎች ፖሊስ በኢጋመ አመራር አባላት ላይ ምርመራ እያካሄደ እንደነበር እና እስሩም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገለጹ፡፡ ይህንንም ተከትሎ ውሎ ሳያድር በተመሳሳይ መልኩ አፍሪካ ሕብረት ለጠራው ስብሰባ በውጭ አገር ይገኝ የነበረውን የጋዜጠኛ በትረ ያዕቆብ ላይ የቤት ብርበራ በመፈፀምና ሌሎች የማኅበሩ አመራር አባላትን በተለይም በዚያው ሰሞን ሙያዊ ስልጠና ለመውሰድ ወደ ናይሮቢ አምርቶ በነበረው የማኅበሩ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ በነበረው ጋዜጠኛ ዘሪሁን ሙሉጌታ ላይ ይደርስ የነበረው ወከባ እና ማስፈራራት መንግስት ማኅበሩን በእንጭጩ ለመቅጨት የነበረውን ከፍተኛ ፍላጎት በግልፅ ያሳየ ነበር፡፡ ዛሬ ሁለቱ ከፍተኛ የአመራር አባላት በተቀነባበረ የማዋከብ ዘመቻ ከሀገር እንዲሰደዱ ተደርጓል፡፡ ይህም መንግስት የማኅበሩን አመራሮች ከተቻለ በማሰደድ፣ ካልሆነም በተለመደው በሽብርተኝነት ወንጀል በማሰር ማኅበሩን ለማፍረስ የነበረውን እቅድ በከፊል የተሳካ አድርጎታል፡፡
ሁለቱ የማኅበሩ የአመራር አባላት በዚህ ሁኔታ ሀገር ጥለው ከተሰደዱ በኋላ የተቀሩት የማኅበሩ አመራሮች ችግሮችን ተጋፍጠው ማኅበሩ የቆመለትን ዓላማ ከዳር ላማድረስ ከፍተኛ ጥረት አድርገዋል፡፡ በሰኔ ወር መጀመሪያ ላይ የእውቅና ሂደቱ በተለያየ ምክንያት እየተስተጓጎለ በነበረበትም ሁኔታ የሀገሪቱን አስከፊ የፕረስ ሁኔታ በተመለከተ በአፕቪው ሆቴል የግማሽ ቀን የፓናል ውይይት እንዲካሄድ አድርገዋል፡፡ በዚህ የፓናል ውይይት የአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ የኮሙኒኬሽን የትምህርት ክፍል ኃላፊ ጥሩ የሚባል ጽሑፍ ያቀረቡበት፣ እንዲሁም ከፀረ ሽብር ህጉ አንፃር ታዋቂው የህግ ባለሙያ ተማም አባቡልጉ የመወያያ ጽሑፍ ያቀረቡበት ፓናል እንደነበር አይዘነጋም፡፡ ይህ ፓናል ግን በፖሊስ ከበባና ወከባ የተካሄደ ከመሆኑ በላይ በሶስተኛው ቀን በኢትዮጵያ ቴሌቭዥንና ሬድዩ ማኅበሩ ህገ-ወጥ ነው ተብሏል፡፡
ሆኖ ይህ ማኅበር የቆመለትን ዓላማ ከግብ ለማድረስ የተቀሩት አባላቱ ተስፋ ባለመቁረጥ ከእውቅና ሰጭ አካል ጋር በሰላማዊ እና ሕጋዊ መንገድ መታገላቸውን አሁንም ቢሆን አላቆሙም፡፡ ነገር ግን ተቋሙ አንዴ ስም ቀይሩ ሲል፣ ሲቀየር፣ ሌላ ጊዜ ሌላ ሲል ከርሞ መጨረሻ ላይ ዓላማችሁን ቀይሩ በማለት ማኅበሩን አልቀበልም ብሏል፡፡ በአሁኑ ወቅት የተቀሩት አራት የማኅበሩ አመራር አባላትም ቢሆኑ በእስር ወጥመድ ውስጥ የሚገኙ ሲሆኑ፤ ከማኅበሩ ሰባት አመራር አባልት መካከል ፕሬዝዳንቱ ጋዜጠኛ በትረ ያዕቆብ፣ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው ጋዜጠኛ ዘሪሁን ሙሉጌታ እንዲሁም ሰሞኑን በመንግስት ክስ እና ጫና ሀገር ጥለው ከተሰደዱት የአዲስ ጉዳይ ጋዜጠኞች አንዱ የሆነውና በማኅበሩ ምክንያት ከባድ ማስፈራሪያ ይደረስበት የነበረው ጋዜጠኛ ብታሙ ስዩም ለስደት ተዳርገዋል፡፡ ለሀብታሙ መሰደድ እንደ አንድ ዋና ምክንያት የተጠቀሰው ይሄው ከማኅበሩ ጋር በተያያዘ የደረሰበት ከባድ ማሳፈራሪያ ነበር፡፡ እነዚህ ሶስቱ ጋዜጠኞች በኢትዮጵያ ጋዜጠኝነት ውስጥ ተስፋ የሚጣልባቸውና በሙያቸው ኃላፊነት የሚሰማቸው ጋዜጠኞች ነበሩ፡፡
ለስደት የተዳረጉት እነዚህ የማኅበሩ አመራር የሆኑ ጋዜጠኞች ከሚደርስባቸው ጫና ባሻገር ለሌሎች ጋዜጠኞች መብት መከበር ያደረጉት ጥረት በሽብርተኝነት እንዲወነጀሉ አድርጓቸዋል፡፡ የተነሱለት በጎ ዓላማ በክፋት ተመንዝሮ ወደ ዳር እንዲገፉ ተደርገዋል፡፡ ለዓመታት በተስፋ ሲጠብቁት የነበረው የጋዜጠኝነት ሙያ እድገትና የባለሙያው መብት መከበር እውን እንዲሆን የጀመሩት ጥረት በስደት እንዲቋጩት ተገደዋል፡፡
ዛሬ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ በኢትዮጵያ የጋዜጠኝነት ሙያ ዉስጥ ሁሉን አቀፍ አደረጃጀትን መሰረት በማድረግ በሁሉም ጋዜጠኞች እምነት የሚጣልበት ፣ ለሙያዉ እና ሙያዉን በሀላፊነት መንፈስ ለሚተገብሩ ጋዜጠኞች ሁሉ ጥላ ከለላ ለመሆን የነበረዉ አላማ ዛሬ በእንዲህ አይነት መልኩ ከባድ ፈተና ላይ ወድቆ ይገኛል፡፡ ከመንግስት እየደረሰበት ያለዉ መጠነ ሰፊ ጥቃት ማህበሩን አጣብቂኝ ዉስጥ የከተተዉ ሲሆን ፣ ቁልፍ የሆኑት አመራሮቹ በፍርሀትና ተስፋ መቁረጥ መሰደድም የማህበሩን ፈተና ከምን ጊዜዉም በላይ አክብዶት ይገኛል፡፡ ይህም ለእብሪተኛዉ ገዥ ሐይል ትልቅ ስኬት ሲሆን ፣ ለኢትዮጵያዉያን ጋዜጠኞች እና ለነፃዉ ፕሬስ ግን ከባድ ዉድቀት ነዉ፡፡

ሕወሃት/ኢሕአዴግ ምን ያህል እንዳከረረ (ክፍል 1) – ግርማ ካሳ

የ «ጌታቸውን » የአቶ መለስን ራእይ፣ አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ በትጋት እየፈጸሙት እንደሆነ በስፋት እያየን ነው። የአቶ መለስ ራእይ ጭቆና፣ አምባገነንነት፣ ሰላማዊ ዜጎችን ማሰር፣ ሜዲያዉን መጨፍለቅ ነው። የአቶ መለስ ራእይ በእርቅና በፍቅር አገርን ማሳደግ ሳይሆን፣ ማክረር በዜጎችን ላይ መጨከን ነው።
cartoon_691የፍቅርና የሰላም መጽሀፍን (መጽሐፍ ቅዱስን) በየቀኑ አነባለሁ በሚሉት በአቶ ኃይለማሪያም አገዛዝ ግን፣ ሕወሃት/ኢሕአዴግ በመለስ ጊዜ ከነበረው በባሰ ሁኔታ በጣም እያከረረ መጥቷል። በርግጥም አቶ ኀያለማሪያም የአቶ መለስስ ፎቶ እየተሳለሙ ቃል እንደገቡት፣ የአቶ መለስን ራእይ በትጋት እያስፈጸሙ ናቸው።
ምን ያህል አገዛዙ እንዳከረረ የሚያሳይ አንድ ጉልህ ማስረጃ፣ በተለይም በሜዴያዉ አንጻር እንዳቀርብ ይፈቀድለኝ። በምንም አይነት ሕወሃት/ኢሕአዴግ እንዲነገርና እንዲጻፍ ከሚፈለገው ውጭ መጻፍ እንደማይቻል እያየን ነው። ኢቲቪ የመሳሰሉቱ ደግሞ እንደ ሰዉ ለሰው ድራማ ያሉትን ከማየት ዉጭ፣ አስቀያሚ ሜዲያዎች ሆነዋል። በጣም አስቀያሚ !!!!! እነ ሪፖርተር፣ አዲስ ፎርቹን የመሳሰሉቱ፣ የአገዛዙ ቱጃሮች ማስታወቂያ የሚያወጡበት፣ በአገዛዙ እየተደገፉ የሚንቀሳቀሱ፣ የጋዜጠኝነት ስነ-ምግባር ኮድን የማይተገብሩ፣ በአጋር ጋዜጠኖች ላይ የሚደርሰው ግፍ የማይሰማቸውና የማይቆረቆሩ፣ ለይስሙላ የሜዱያ ነጻነት አለ ለማስባል ለአገዛዙ የፖለቲካ ፍጆታ የሚዉሉ፣ በአደርባይነት የተሞሉ ፣ ጋዜጠኖች ሊባሉ የማይገባ ጋዜጦች ናቸው።
በአቶ መለስ ጊዜ የታሰሩ ጋዜጠኖች
1. ርዮት አለሙ (የፍትህ ጋዜጣ አምደኛ)
2. እስክንደር ነጋ
ከ2002 ምርጫ በኋላ በአቶ መለስ ጊዜ የተሰደዱ ጋዜጠኖች
1. አብይ ተከለማሪያም ( አዲስ ነገር)
2. መስፍን ነጋሽ (አዲስ ነገር)
3. ታምራት ነገራ (አዲስ ነገር)
4. አቤ ቶኪቻው (አዉራምባ ታይምስ)
5. ጋዜጠኛ ዳዊት ከበደ ተሰዶ ነበር ፣ አሁን ሰላም ነው ብሎ ተመልሷል
ከ2002 ምርጫ በኋላ በአቶ መለስ ጊዜ እንዳይታተሙ ወይም ክስ የተመሰረተባቸው ጋዜጦች
1. አዲስ ነገር
በዳግማዊው መለስ ዜናዊ ፣ ኃይለማሪያም ደሳለኝ ሁለት አመት አገዛዝ፣ ወደ ወህኒ የተወሰዱ ጋዜጠኞችና ብሎገሮች (ሁሉም በሽብተኘት የተከሰሱ)
1. ተስፋለም ወልደየስ
2. አጥናፉ ብርሃኔ
3. ዘላለም ክብረት
4. ኤዶም ካሳዬ
5. ናትናኤል ፈለቀ
6. ማህሌት ፋንታሁን
7. አቤል ዋበላ
8. በፍቃዱ ኃይሉ
9. አስማማዉ ወልደጊዮርጊስ
በዳግማዊው መለስ ዜናዊ ፣ ኃይለማሪያም ደሳለኝ ሁለት አመት አገዛዝ፣ ከአገር የተሰደዱ ጋዜጠኖችና ብሎገሮች
1. ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ( የሎሚ መጽሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር)
2. ጋዜጠኛ ቶማስ አያሌው (የአፍሮ ታይምስ ማኔጂንግ ዳይሬክተር)
3. ጋዜጠኛ ዳንኤል ድርሻ (የሎሚ መጽሔት ሚዲያ ዳይሬክተር)
4. ጋዜጠኛ ሰናይ አባተ (የሎሚ መጽሔት ዋና አዘጋጅ)
5. ጋዜጠኛ ሰብለወርቅ መከተ (የሎሚ መጽሔት ከፍተኛ ሪፖርተር)
6. ጋዜጠኛ አቦነሽ አበራ (የሎሚ መጽሔት ከፍተኛ ሪፖርተር)
7. ጋዜጠኛ አስናቀ ልባዊ (የጃኖ መጽሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር)
8. አቶ እንዳልካቸው ተስፋዬ (የአዲስ ጉዳይ መጽሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተርና የሮዝ አሳታሚ ድርጅት ሥራ አስኪያጅ )
9. አቶ ኢብራሃም ሻፊ (የአዲስ ጉዳይ መጽሔት ምክትል ዋና አዘጋጅ)
10. እንዳለ ተሺና (የአዲስ ጉዳይ መጽሔት ከፍተኛ አዘጋጅ )
11. ሀብታሙ ሥዩም (የአዲስ ጉዳይ መጽሔት ዓምደኛ)
12. ዳዊት ሰለሞን (ታዋቂ ብሎገር)
13. ዘሪሁን ሙሉጌታ ( የሰንደቅ ጋዜጣ ረፖርተር)
በዳግማዊው መለስ ዜናዊ ፣ ኃይለማሪያም ደሳለኝ ሁለት አመት አገዛዝ፣ ሕተመታቸው የተቋረጠ ወይንም ክስ የቀረበባቸው
1. ፍትህ ጋዜጣ
2. ፍኖት ነጻኘት ጋዜጣ
3. የአዲስ ጉዳይ መጽሔት
4. የፋክት መጽሄት
5. የሎሚ መጽሄት
6. የጃኖ መጽሄት
7. የአፍሮ ታይምስ ጋዜጣ

በጥፍሩም በጥርሱም ለስልጣን የሚተጋ መንግሰት …… እንዴት እንታገለው!! – ከግርማ ሰይፉ ማሩ

August29/2014
በጥፍሩም በጥርሱም ለስልጣኑ የሚተጋን መንግስት በሁሉን አቀፍ ትግል መጣል አለብን ብለው ጠብ መንጃ ቢያነሱ ክፋቱ ምን ላይ እንደሆነ አልታይህም እያለኝ ነው፡፡ ለምን በጠብ መንጃ ፍልሚያ ስልጣን መያዝ እንዳለብኝ በግሌ ባይገባኝም አሁን ግን የኢህአዴግ ዓይነት መንግሰት ከደርግ እንዴት እንደሚሻል ማሰብ እያቃተኝ ነው፡፡ የሰላማዊ ትግል ሰራዊት እንዴት እንገንባ ለሚለው ጥያቄ አፋጣኝ ምለሽ ካልሰጠን በስተቀር መንግሰት በግልፅ እየደገፈ ያለው በጠብ መንጃ ሊገዳደሩ የፈለጉት ነው፡፡ በሰላም ያልነውን ሰላም እየነሳን ይገኛል፡፡ መንግሰት ሆይ ሰላም እንድትሆን ሰላም ሰላም ለምንል ዜጎች ሰላም ሰጠን የምር የቀረበ ጥያቄ ነው፡፡
በፍትሕ አደባባይ የፈለገውን ማድረግ የወሰነ መንግሰት በእጅ አዙር ደግሞ በየማተሚያ ቤቱ እየሄደ መፅሄትና ጋዜጣ ታትሙና ወዮላችሁ ማለት ተያይዞታል፡፡ ይህ ከህግ ሰርዓት ውጭ በየማተሚያ ቤቱ በግንባር እና በስልክ የሚደረገው ማሰፈራሪያ ከወሮበላነት ውጭ ምንም ሊሆን አይችልም፡፡ መንግሰት ለህዝብ ጥቅም ሲባል ክስ መስርቻለሁ ብሎዋል፡፡ ህዝቡ የሚለው ግን ሌላ ነው፡፡ መፅሄት መቼ ነው የሚወጣው ነው፡፡ በቃ!!! ፍርድ ቤት በመፅሔትና ጋዜጦች ላይ ቢፊልግ እግድ ቢፈልግ ይዘጉ እሰኪል ድረስ ምን የሚያጣድፍ ነገር መጥቶ እንደሆነ ባናውቅም የመንግሰት አሽከሮች በየጉራንጉሩ ባሉ ማተሚያ ቤቶች ደጃፍ እየዞሩ ማሰፈራራት ተያይዘውታል፡፡ ሹሞቻችን ይህን አላደረግንም ብለው እንደሚክዱ ባውቅም ይህን ዓይነት ወሮበላነት ማስቆም ካልቻሉ ተጠያቂ እንደሚሆኑ መርሳት የለባቸውም፡፡ ስህተታችውን በአደባባይ ተችተን እንዲታረሙ የሚሰጣቸው ምክር ካንገሸገቸው የመጨረሻው ቀን ሲመጣ እንደሚጠየቁ ግን ማስታወስ ተገቢ ነው፡፡ የወሮበላ አለቃነት ከወሮበላነት በላይ የሚያስጠይቅ ነው፡፡ እነዚህን ወሮበላዎች አስቁሙልን ግልፅ አቤቱታ ነው፡፡ በየሳምንት ብዙ መቶ ሺ ብር ገቢ ያገኙ የነበሩ ማተሚያ ቤቶች በህጋዊ መስመር ሳይሆን በስልክና በቃል ከወሮበሎች በሚሰጥ ማሰፈራሪያ አጅ መስጠት እና ገበያ ማባረር ደግሞ የሚያስመሰግን ፍርሃት እንዳልሆነ ልብ ሊሉት ይገባል፡፡ የእያንዳንዳችን ፍርሃት ተደምሮ ነው እነርሱም ያለምንም ይሉኝታ ሊያሰፈራሩን ቤታቸውን ድረስ የሚመጡት፡፡ በወረቀት ትዕዛዝ ይድረሰኝ ለማለት ወኔ የሌለው ማተሚያ ቤት የሙት ዓመትና ተዝካር ወረቀት ሲያትም ይኖራታል፡፡
መንግሰት በሚዲያዎች ላይ በዶክመንተሪ ጀምሮት የነበረውን ወደ ፍትህ አደባባይ ያመጣውን የግል ሚዲያ አሁንም ገና አልበቃውም፡፡ በጥፍርም በጥርስም ሊዘለዝል እየባተተ ይገኛል፡፡ ኢትቪ ቤታችን ድረስ መጥቶ ለሆዳቸው ባደሩ ምሁራን ተብዬዎች እና ሹመኞች ሲሳደብ ያመሻል፡፡ የኮሚኒኬሸን ጉዳዮች መስሪያ ቤት ውስጥ ዳይሬክተር ናቸው የተባሉ ታምራት ደጀኔ የሚባሉ ኃላፊ መሰሪያ ቤቱ የመንግሰት ደሞዝ የሚከፈላቸው እኔ ጭምር በምከፍለው ግብር መሆኑን ዘንግተው የግል ፕሬስ ከተቃዋሚዎች ጋር ወግኖ እየሰራ ነው ብለው ከገዢው ፓርቲ ጎን ቆመው ሲከሱን አምሽተዋል፡፡ እኚህ ግለስብ ከተቃዋሚ ጎን መሰለፍ ማን ሀጥያት ነው እንዳላቸው አላውቅም፡፡ ተቃዋሚዎች በህግ ተመዝግበው የሚሰሩ ተቋማት እንደሆኑ እና የሚደግፋቸውም የሚቃወማቸውም ሰዎቸ መኖራቸው የሚጠበቅ መሆኑን ዘንግተውታል፡፡ ለነገሩ እርሳቸው የሚደግፉት ፓርቲ ነገ ተቃዋሚ የሚባል ወንበር ላይ ሊኖር እንደሚችል በተሰፋ ደረጃ ማሰብ አልቻሉም፡፡ ለነገሩ ኢህአዴግ በጥቅም የተገዙ አባላቶቹ ስልጣን ሲያጣ አብረውት እንደማይቆዩ ይረዳዋል- እርሳቸውንም ጨምሮ ማለቴ ነው፡፡ ለዚህም ነው ኢህአዴግ በጥርስም በጥፍርም ፍልሚያ ውስጥ የሚገባው፡፡ አቶ ታምራት ደጀኔ እንዲረዱ የምፈልገው የግሉ ፕሬስ ተቃዋሚን ቢደግፍ አንድም ነውር እንደሌለው ይልቁንም ገዢውን ፓርቲ ለመደገፍ ገዢው ፓርቲ ብቁ እንዳልሆነ ማሳያ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ በገንዘብ የሚደግፋቸው ነገር ግን ተደግፈው መቆም የማይችሉ “የግል” ተብዬ ሚዲያዎች እንደነበሩ መርሳት የለባቸውም፡፡ ለምሳሌ ኢፍቲን፣ ዛሚ፣ ወዘተ
ሰኞ ነሃሴ 19/2006 በቀረበው ዶክመንተሪ ተብዬ ዘባተሎ ላይ ከለየላቸው የመንግሰት ሹሞኞች እስከ ዩኒቨርሲት መምህራን አልፎ ተርፎም አትሌት ሀይሌ ገብረስላሴን ያሳተፈ ነበር፡፡ እርገጠኛ ነኝ ሀይሌ በሚዲያ ላይ ስለሚታዩ ግድፈቶች አጠቃላይ ሁኔታ ነበር የሚናገረው እንጂ አሁን ክስ ስለተመሰረተባቸው የግል ሚዲያዎች አልነበረም፡፡ ቆርጦ ቀጥሉ ኢቲቪ ግን ከህዝብ ጋር ሊያጋጨው ፍላጎቱን አሳይቶዋል፡፡ ሌላው ተዋናይ ዶክትረ አሸብር ወልደጊዮርጊስ ነበሩ፡፡ ከብዙ ጊዜ በተሻለ ሁኔታ ነበር መልስ አሰጣጣቸው፣ የከሰሱትም ሪፖርተርን ነው፡፡ መንግሰት ደግሞ ከሪፖርተር ጋር ጉዳይ የለውም፡፡ እንዲከሱ ሲጠበቅ የነበረው ሌላ ነበር፡፡ ይቅር ብያለሁ ብለው አልፈውታል፡፡ የእርሳቸው ይቅር ባይነት ከመንግሰት ሰፈር ሊገኝ አልቻለም፡፡ ተበቃይ መንግሰት ለስልጣኑ ሲል በጥፍሩም በጥርሱም ከግል ሚዲያው ጋር ግብ ግብ ገጥሞዋል፡፡ ማን ያሸንፋል አና መቼ ወደፊት የሚታይ ነው፡፡
የቀረበውን ዘጋቢ ፊልም ማስታወሻ ይዜ ለሁሉም በስማቸው አንፃር ለመፃፍ ነበር የፈለኩት ይህን ዘባተሎ የበዛበት ድሪቷም ዘጋቢ ተብዬ ከዚህ በላይ ማለት ተገቢ ሆኖ ስለአልተመቸኝ ተውኩት …. ይህ ዘጋቢ ፊልም ተብዬ የተሰራበት ሙሉ ዶክመንት ለታሪክ እንደሚቀር ተሰፋ አለኝ፡፡ የዛን ጊዜ እንወቃቀሳለን፡፡ ምሁራን ተብዬዎች በእናንተ ተሰፋ ቆርጠናል ….. በእናንተ መምህርነት አንድም የተሻለ ጋዜጠኛ እንደማናገኝ፡፡ ለነገሩ ልጆቹ የአስተማሪዎች ብቻ ሳይሆን የእኛም ናቸው እና በቤታችን ይማራሉ፡፡ ሀገር ማለት ልጄ ብለን እናስተምራለን፡፡

የኦህዴድ ካድሬዎች የህዝብ ሰብልና ንብረትን እያወደሙ እንደሆነ ተገለጸ

August29/2014
ኦሮሚያ ክልል ውስጥ ጫንቃ፣ ሁርሙ፣ ዶረኒ፣ ኃይና፣ ከሚሴጎንደራ፣ በዴሳና ሄና በተባሉ ወረዳዎች የኦህዴድ ካድሬዎች የአማርኛ እና ትግርኛ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያንን ሰብልና ንብረት እያወደሙ መሆኑን ምንጮች ነገረ ኢትዮጵያ ዝግጅት ክፍል ድረስ በመምጣት ገልጸዋል፡፡
ካድሬዎቹ ሰብሉን ማውደም የጀመሩት ከሀምሌ ወር መጀመሪያ ጀምረው እንደሆነና ማሽላ፣ በቆሎ፣ ቡና፣ ባህር ዛፍ የመሳሰሉትን ሰብሎችና ንብረቶች ጨለማን ተገን በማድረግ በገጀራና በመሳሰሉት መሳሪያዎች በማውደም ላይ መሆናቸውን ምንጮች ገልጸዋል፡፡ ይህ ድርጊት እየተፈጸመ ያለው በአካባቢው የሚኖሩት ከላይ የተጠቀሱት ኢትዮጵያውያን ልቀቁ ሲባሉ ለቀው ለመውጣት ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ሰብላቸውና ንብረታቸው ከወደመ ይለቃሉ ከሚል ስልታዊ ማፈናቀል ዘዴ መሆኑን ምንጮቹ አክለው ገልጸዋል፡፡
ከሶስት አመት በፊት በቾ በተባለ ወረዳ ተመሳሳይ ተግባር እንደተፈጸመ የገለጹት ምንጮቻችን፣ በወቅቱ ይህ ሰብል የማውደም ተግባር የተመራው በሚሊሻ ጽ/ቤቱ ኃላፊ እንደነበር እማኝነታቸውን ገልጸውልናል፡፡ ይህን ተግባር የፈጸመው ግለሰብ መልካም ስራ እንደሰራ በአሁኑ ወቅት ትልቅ ስልጣን ላይ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በዚህ ስልታዊ የማፈናቀል ተግባር የኦህዴድ ካቢኔ ለሁለት እንደተከፈለ የገለጹት ምንጮቻችን ንብረት የማውደሙ ተግባር ካለፈው ሳምንት ጀምሮ ተጠናክሮ መቀጠሉ የነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ንብረታቸው እየወደመባቸው የሚገኙ ዜጎች ሌሊት ሌሊት ተደራጅተው ሰብላቸውንና ንብረታቸውን ለመጠበቅ በዝግጅት ላይ በመሆናቸው ከካድሬዎቹ ጋር ሊጋጩ እንደሚችሉና ይህንንም ካድሬዎች የህዝብ ግጭት አስመስለው ስለሚያቀርቡት በህዝብ መካከል ግጭት ሊያስነሳ ይችላል ሲሉ ስጋታቸውን አክለው ገልጸዋል፡፡

Thursday, August 28, 2014

በድርጅቶች ውህደትና ቅንጅት አገርን ማዳን!!!

August28/2014
ኢትዮጵያዊያንን በዘር እና በሀይማኖት ለያይቶን እርስ በርስ እያጋጨን በመግዛት ላይ ያለውን ወያኔን ለማሸነፍ እና ከምትኩም ከራሷ ጋር የታረቀች፤ ፍትህ የሰፈነባት፤ እኩልነት የተረጋገጠባት እና በኃያላን አገሮች እርጥባን ሳይሆን በራሷ አቅም የምትተማመን ጠንካራ ሀገር እንድትኖረን የነፃነትና የዲሞክራሲ ኃይሎት መተባበር እንዳለባቸው ሲነገርና ሲወተወት ቆይቷል። ይሁን እንጂ በህወሓት የከፋፍለህ ግዛው ፓሊሲ እና በፓለቲካ ባህላችን ኋላቀርነት ምክንያት እስካሁን የተደረጉ የትብብር ጥረቶች የተፈለገውን ውጤት ሳያስገኙ ቀርተዋል።
ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ፣ ቀድሞ የተደረጉት ጥረቶች የተጠበቀውን ውጤት አለማስገኘት ተስፋ ሳያቆርጠን ከእያንዳንዱ ጥረት ልምድ እየወሰደን የኢትዮጵያዊያን አንድነት እስኪረጋገጥ ድረስ አዳዲስ የትብብር ጥረቶችን ማድረግ ያለብን መሆኑ ያምናል። በዚህም መሠረት የትብብር መርህ ነድፎ ትግል ውስጥ ካሉ ሁሉም የፓለቲካ ድርጅቶች ጋር ሲነጋገር እና ሲደራደር ቆይቷል። እንደሚታወቀው የንቅናቄዓችን አበይት የትብብር መርሆች ሁለት ናቸው። መርህ አንድ፣ ለውጥ እንዲመጣ የምንታገለው ኢትዮጵያ በምትባል አገር ውስጥ መሆኑ ማመን ነው። መርህ ሁለት ደግሞ በኢትዮጵያ ውስጥ በሁሉም እርከኖች የመንግሥት ሥልጣን መያዝ የሚገባው በሕዝብ ነፃ ምርጫ ብቻ መሆኑን መቀበል ናቸው።
በምድር ላይ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ከሚያደርጉ ኃይሎች መካከል የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር እና የአማራ ዲሞክራሲያዊ ኃይሎች ንቅናቄ ሁለቱንም መርሆዎች የሚያሟሉ ናቸው። እነዚህ ድርጅቶች በኢትዮጵያ ሉዓላዊነት ላይ ከንቅናቄዓችን የተለየ አቋም የላቸውም። በአለፉት ሁለት ዓመታት ድርጅቶቹ ተቀራርበው እንዲሠሩ በመደረጉ ከአመራር አልፎ አባላት መካከል መልካም ወዳጅነት መመሥረት ተችሏል። የነፃነት ትግላችን የደረሰበት ደረጃ እና የድርጅቶቹም ቅርርብ በመገምገም ሶስቱ ድርጅቶች ማለትም የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር፣ የግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄና እና የአማራ ዲሞክራሲያዊ ኃይሎች ንቅናቄ መዋሃዳቸው ትግሉን ያራምዳል ተብሎ ታምኖበታል። በዚህም መሠረት ሶስቱ ድርጅቶች ለመዋሃድ ተስማምተን ስምምነታቸንን ይፋ አድርገናል። ድርጅቶቹን የማዋሃድ ዝርዝር ሥራም ተጀምሯል።
ከስትራቴጄ አንፃር የትብብር ጥረታችን በዚህ አያበቃም። በዓላማ የምንቀራረብ ሆኖ የአደረጃጀት ልዩነት ያለን የዲሞክራሲ ኃይሎች ጋር በጥምረት እየሠራን ድርጅቶቻችን ይበልጥ ለማቀራረብ ጥረት እያደረግን ነው። በዚህ ረገድ ግንባር ቀደም ተጠቃሹ የትግራይ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ትህዴን) ነው። ንቅናቄዓችን ከትህዴን ጋር ከፍተኛ በሆነ መቀራረብና መተማመን ይሠራል። ይህ መቀራረብና መተማመን ጎልብቶ አንድ የጋራ አመራር የሚፈጥርበት ጊዜ እንዲቀርብ ጥረት እናደርጋለን። ምድር ላይ ከሚገኙ ሌሎች ተመሳሳይ ድርጅቶች ጋርም በመደጋገፍ እንሠራለን። በመጨረሻም ተግባራዊ እንቅስቃሴ ላይ ካሉ ማናቸውም ኢትዮጵያዊ ድርጅቶች ጋር ለመወያየት ዝግጁዎች መሆናችንን ደግመን እናረጋግጣለን። ልዩነቶቻችን ማጥበብ እንኳን ባንችል የምንተባበርባቸው መንገዶች ይኖራሉ ብለን እናምናለን።
የጦር ኃይሉንና የስለላ መዋቅሩን ዘረኛ በሆነ መንገድ የገባውንና የኢትዮጵያን ሀብት በመዝረፍ የደረጀው ህወሓትን ለማሸነፍ ትብብር ወሳኝ ጉዳይ ነው። ከወያኔ አገዛዝ ውድቀት በኋላ ወደ ተረጋጋ ሰላምና ልማት ፊታችንን የምናዞር መሆናችን ዋስትና የሚሰጠን በአንድ እዝ የሚመራ የአገር አድን ሠራዊት ማደራጀት ስንችል ነው። የአሁኑ ውህደት የዚህ አገር አገር አድን ሠራዊት ጥንስስ ሊሆን ይችላል ብለን እናምናለን።
የኢትዮጵያ ሕዝብ ከወያኔ በኋላ የሚመጣው ምን እንደሆነ ባለማወቅ ሥጋት ውስጥ ሊገባ አይገባም። በዋና ዋና የአገሪቱ የፓለቲካ ድርጅቶች ውህደት እና ቅንጅት የተዋቀረ በአንድ ማዕከላዊ አመራር ሥር የሆነ አገር አድን ሠራዊት በተቻለ ፍጥነት ሊገነባ ይገባል።
ሶስቱ ድርጅቶች ለማድረግ በወሰነው ውህደት የዚህ የአገር አድን ሠራዊት ምሥረታን ጀምረናል። ስለኢትዮጵያ እና ሕዝቧ ወይም በኢትዮጵያ ውስጥ ላለ ማንኛውም የኅብረተሰብ ክፍል ደህንነት ያገባናል የምትሉ ወገኖቻችን ሁሉ በዚህ አገር አድን ሠራዊት ምሥረታ ላይ እንድንነጋገር አበክረን እንጠይቃለን።
የኢትዮጵያ ሕዝብም የትብብሩ መንፈስ አገርን የማዳን ግብ ያለመ መሆኑን በመገንዘብ ከተባበረው ድርጅት ጎን እንዲቆም ጥሪ እናደርጋለን። የፍትህ፣ የእኩልነት፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ጉዳይ የሚያገባው ኢትዮጵያዊ ሁሉ እንዲቀላቀለንና እንዲያግዘን ጥሪዓችንን እናቀርባለን።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

13 የኢትዮጵያ መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣኖችና የጦር መኮንኖች በስዊድን አለማቀፍ የጦር ፍርድ ቤት ክስ ተመሰረተባቸው

August28/2014
(ኢሳት ሰበር ዜና) 13 የኢትዮጵያ መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣኖችና የጦር መኮንኖች በስዊድን አለማቀፍ የጦር ፍርድ ቤት ክስ ተመሰረተባቸው ሲል ኢሳት በሰበር ዜናው ዘገበ።
እንደ ኢሳት ቲቪ ዘገባ አርከበ እቁባይ፣ በረከት ስምኦን፣ አባ ዱላ ገመዳ፣ ሳሞራ የኑስ፣ አባይ ጸሃየ፣ ጌታቸው አሰፋ፣ ሌ/ጄ ታደሰ ወረደ፣ ሃሰን ሺፋ፣ ሙሉጌታ በርሄ፣ ነጋ በርሄ፣ ወርቅነህ ገበየሁ፣ ኮማንደር ሰመረ እና አንድ ስሙ ያልተገለጸ ሰው በግድያ፣ በአስገድዶ መድፈር፣ በስቃይ፣ ሰዎችን በማንገላታትና በህገወጥ መንገድ በማሰርና ሌሎችንም ተመሳሳይ ወንጀሎች በመፈጸም በስዊድን አለማቀፍ የጦር ፍርድ ቤት ክስ ተመስርቶባቸዋል።
የስዊድን ታዋቂ ጠበቆች ያዘጋጁት የክስ ቻርጅ የስዊድ የአለማቀፉ ወንጀል መርማሪ ፖሊስ ተረክቧል።
ጉዳት ለደረሰባቸው ኢትዮጵያውያንም የ130 ሚሊዮን የስዊድን ክሮነር ካሳ መጠየቁን የዘገበው ቴሌቭዥኑ ከስዊድን አለማቀፍ የወንጀል መርማሪ ፖሊስ የተሰጠው መልስ እጅግ አስደሳች መሆኑን አዘጋጆች ለኢሳት መግለጻቸውን ዘግቧል።
የስዊድን ፖሊሶች ምርመራ መጀመራቸውን ያስታወቁ ሲሆን የክሱ አላማ በምርጫ 97 ወቅት ለተገደሉትና ለቆሰሉት ፍትህ መስጠት ነው።

የኢትዮጵያ ሕዝበ ሙስሊም ሊያውቀው የሚገባ ጥልቅ ምስጢር (ከትህዴን የተላለፈ ቪድዮ)

August 28/2014
የኢትዮጵያ ህዝበ-መስሊም ሊያወቀው የሚገባው ትልቅ ምስጢር!!
- የኣል ኣህባሽ ፤ ኣልቃይዳ ፤ ኣል-ሸባብ፤ ወደ ኢትዮጵያ እንዴት ገቡ? በማንስ ገቡ?
- ኢትዮጵያውያን መስሊሞች ለምን ከሳውዲ ኣገር ተባረሩ? ለምንስ የሌላ ኣገር ዜጎች ኣልተባረሩም?
- የኢትዮጵያውያን የእስልምና መብት ጥያቄ ምንድ ነው? ከየትስ መጣ? ከየት ወዴት እየሄደ ነው?
- እስልምና ምንድ ነው?
- ወሃቢዝም ምንድ ነው? ምን ማለት ነው?
የሚሉና ሌሎች በርካታ ጥያቄዎች በዚህ ቃለ-መጠይቅ ተካትተዋል። ህዝበ-መስሊዩም ሊያወቀው የሚገባው ትልቅ ምስጥር!!


ነጻነትን በማሳጣት ዜጎችን ለስቃይ፣ለእስራትና ለስደት የዳረገውን መንግስት ልናስወግደው ይገባል

Gezahegn Abebe (ገዛኸኝ አበበበ ከኖርዌ ሌና)
ወያኔ ኢህአዲግ የስልጣን ወንበሩን በሀይል ከተቆናጠጠበት ጊዜ ጀምሮ በስልጣን በቆየባቸው በሃያ ሶስት አመታቶች በየጊዜው በህዝባችን ላይ የሚያደርሰው ግፍ እና ጭቆና ከእለት ወደ እለት እየጨመረ መምጣቱ በአደባባይ የሚታይ እውነታ ሲሆን ከዚህም ጨቋኝና ገዳይ ስርዓት የተነሳ የሀገሪቷ ዚጓች  በሀገራቸው ላይ በሰላም መኖርና የነጻነትን ሀየር መተንፈስ በማይችሉበት ክፉ ሁኔታ ውስጥ ይገኛሉ::ለሰው ልጅ ነጻነቱ እየተገፈፈና መብቱ እየተረገጠ እንደ መኖርን የመሰለ አስቀያሚ ህይወት ያለ አይመስለኝም::ስለዚህ ነው በአሁኑ ጊዜ ከማንኛውም ጊዜ በተለየ መልኩ በሀገራችን ኢትዮጵያ  ገበሬው፣  ተማሪው፣  ፣ አስተማሪው ፣ ነጋዲው፣ ጋዜጠኛው ፣ ስፖርተኛው፣ ዘፋኙ፣ አርቲስቱ፣ ወዘተ......በማንኛውም እርከን ላይ የሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች በሀገራቸው ላይ በነጻነት መኖርን ስላልቻሉ ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ሀገራቸውን ትተው እየወጡ በየጊዜው ለስደት ሲዳረጉ የሚታዩት::

ከሰሞኑ እንኳን እንደተመለከትነው አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በኢትዮጵያ ይገኙ የነበሩ ቁጥራቸው አስራ ሁለት የሚሆኑ ጋዜጠኞች የወያኔ መንግስት ስራቸውን እንደ ሚገባ እንዳይሰሩና በነጻነት አላንቀሳቅስ ስላላቸው ሀገራቸውን ጥለው ለስደት እንደተዳረጉ ሁላችንም የተመለከትነው ነገር ነው በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ ቁጥራቸ ቡዙ የሆኑ ጋዜጠኞች በአንድ ጊዜ ውስጥ ሀገራቸውን ጥለው ለስደት መዳረጋቸው ቡዞዎቻችንን የሚያስገርምና የሚያስደነግጥ ክስተት ሊሆን ይችላል ነገር ግን ለሰዎች ሁሉ የስደት ምንጭ የሆነው የወያኔ መንግስት ከስልጣኑ እስካልተወገደ ድረስ አፈና፣ እስራት፣ግድያው ከቀን ወደ ቀን እየተባባሰ በየትኛውም እርከን ላይ የሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች መቺም ቢሆን ለስደት መዳረጋቸው የማይቀር እውነታ ነው :.

ሌላው አንድ የታዘብኩት ነገር ሀገራቸውን ጥለው ለስደት ስለተዳረጉ ስለእነዚህ ጋዜጠኞች  በተለያዩ ሰዎች የተጻፉትን ጹሁፉችን ተመልክቻለው  አንዳንድ ሰዎችም የእነዚህ ጋዜጠኞች ከሀገር ለቁ መወጣት ስላልተዋጠላቸው የተለያዩ ትችቱችንና አስተያየቶችን ሲጽፉና ሲሰጡ ተመልክቻለው መቼም ቢሆን ማንኛውም ሰው በሀገሩ ላይ መማርን ፣መስራትንና፣ መኖርን የሚጠላ ሰው ያለ አይመስለኝም :: እነዚህን ጋዜጠኞች ከሌሎች ጋዚጠኞች ጋር እያነጻጸሩ ለምን እንደ እገሌ እዛው ሀገር ቤት ቁጭ ብለው አልታሰሩም ነበር ብሎ መፍረድ አግባብነት ያለው ፍርድ አይመስለኝም :: ማንም ሰው በሀገሩ በነጻነትና በሰላም መኖር ቢሆንለት ስደትን አይፈልግም :: ምክንያቱም ዜጓች በሀገራቸው በተረጋጋ ሁኔታ ለመኑር የሚያስፈልጋቸው  ዋንኛውና ቁልፉ ነገር ሰላም እና ነጻነት ነውና::ማንኛውም ሰው በሚኖርበት ሀገር በሚኖርበት ሰፈር ወይም አካባቢ እና በሚኖርበት ቤት ውስጥ ሳይቀር በሰላምና በነጻነት መኖርን ይፈልጋል:: ነጻነት በምንም ዋጋ ሊተመን የማይችል ትልቅ ጸጋ ነውና:: ሰላም እና ነጻነት በሌለበት ሀገር የሚኖሩ ዜጓች፣   መብታቸው ይረገጣል ፣ ነጻነታቸው ይታፈናል  ዜጓች ለእስር፣ ለሞት፣ እና ለስደት ይደጋሉ::በሀገራችን ኢትዮጵያ የምናየውም በእነዚህ አስራ ሁለት ጋዜጠኞች ላይ የደረሰው ይሄው ነው::

 እንደ አለመታደል ሆኖ ሀገራችን ኢትዮጵያም በአለም ላይ ካሉት ሀገራት በግንባር ቀደምነት  የሰው ልጆች ነጻነታቸውን እና መብታቸውን ከሚገፈፉበት ሀገር ተርታ እንደምትገኝና የሀገሪቷ ዜጓች በጨቋኙ ገዥ ስርዓት ነጻነታቸውን ተገፈው ባሪያ ሆነው የሚኖሩበት ሀገር እንደሆነች በየጊዜው ከሚወጡ አለም አቀፍ ሪፖርቶች መረዳት ይቻላል::::

 ዜጓች በከፍተኛ ሁኔታ ለስደት እየተዳረጉ ባሉበት በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ የሚደረገው አፈና፣ እስራት እና ግድያው በከፍተኛ ሁኔታ ተባብሶ የሚገኝ ሲሆን ይህም በገሃድ እየታየ ያለ እውነታ ነው :: በእነዚህ ሃያ ሶስት አመታቶች በፋሺስቱ የወያኔ ቡድን ነጻነቱ እየተገፈፈና መብቱ እየተረገጠ ያለው የኢትዮጵያ ሕዝብም ከእንግዲህ ወዲህ ይሂን የወረበሎች ቡድን እሽሩሩ እያሉ የመኖር አቅም ያለው አይመሰልም :.: በአሁኑ ጊዜ ከየአቅጣጫው ከሚሰሙ ነጻነት ናፋቂ የኢትዮጵያኖቸ ሕዝብ ጩኸት ድምጽ መረዳት እንደሚቻለው ሕዝባችን ለወያኔያዊ አንባገነን ስርዓት መገዛትን የጠላበትና ከመቺውም ጊዜ በተለየ መልኩ እምቢ አሻፈረኝ ብሎ ነጻነቱን ለማስመለስ በአንድነት ለመቋም የተነሳበት ዘመን ላይ የደረሰን በሚያስመስል መልኩ ከየቦታው የሚሰማው የነጻነትና የሰላም ናፋቂዎች የጀግንነት ድምጽ ምስክር ነው::

በቅርቡ እንኳን እንደምናየው የግንቦት 7 የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ዋና ጸሀፊ የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ከየመን ታግተው በወያኔ እስር ቤት ታስረው በግፍ እየተሰቃዩ እንዳለ ይታወቃል የነጻነት ታጋዩ አቶ አንዳርጋቸው በወያኔ ሴራ ከየመን ታግተው በወያኔ እጅ ላይ መውደቃቸው ከተሰማ ጊዜ ጀምሮ የኢትዮጵያ ሕዝብ የወያኔን አውሬነት በይበልጥ በመረዳት ከዳር እስከ ዳር በአንድነት መቋሙን እያስመሰከረ ሲገኝ የፖለቲካ ግለቱም ጨምሮ የአረመኔው የወያኔን ቡድን በከፍተኛ ሁኔታ አርበድብዶት እንደሚገኝ ወያኔ ከሚሰራው ስራና ከሚያደርጋቸው ድርጊቷች ማወቅ ይቻላል::የአቶ አንዳርጋቸውን መታሰር ተከትሎ  እየከረረ ያለውን የሕዝብን ቁጭትና ቁጣ ለማጥፋት በሚያስመስል መልኩ ይኼ አረመኔው መንግስት በአሁኑ ጊዜ በሀገር ቤት በሰላማዊ መንገድ ለመብታቸው እና ለኢትዮጵያ ሕዝብ ነጻነት በህጋዊ መንገድ እንኮን ሳይቀር እየታገሉ ያሉትን ሰዎች ከየመንገዱ እየለቀመ እስር ቤት አስገብቶ እያሰቃያቸው እንዳለ ይታወቃል ::ይህንንም ተከትሎ  ሁላችንም እንደምናውቀው  የአንድነት ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ አባልና ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ የፓርቲው ምክር ቤት አባል አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ የአረና የሕዝብ ግንኙንት ኃላፊ አቶ አብረሃ ደስታና የሰማያዊ ፓርቲ ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባዔ አቶ የሸዋስ አሰፋን ጨምሮ ሌሎችም እጅግ ብዙ ለየጻነታቸው የሚታገሉ ኢትዮጵያን ወገኖቻችን  የወያኔ መንግስት በግፍ  አስሯቸው እያሰቃያቸው እንደሚገኝ ይታወቃል::

ይኼ መንግስት እሱን  የሚቃወሙትን ሰዎችንና በድፍረት እየተጋፈጡት ያሉትን የፖለቲካ መሪዎች አአሸባሪ የሚል የታርጋ ስም እየለጠፈላቸው ወደ እስር ቤት መወርወር የተጠናወጠው ክፉ ባህሪው ሆኖል:: የፖለቲካ መሪዎችንና የፖለቲካ ሰዎችን ማፈንና እየያዙ ወደ እስር ቤት መወርወር ይበልጥኑ ትግሉን እያከረረውና የኢትዮጵያን ሕዝብ ይበልጥኑ ለነጻነቱ በመታገል ለድል እያነሳሳው  ነው እንጂ ፈጽሞ ከትግል ወደ ኋላ እይመለሰው እንዳይደለ የወያኔ ባለስልጣኖች ጠንቅቀው ሊያውቁት የሚገባቸው ነገር ይመስለኛል:: የኢትዮጵያ ሕዝብ ነጻነትን ተጠምቷል ::Freedom is more than food  በአሁኑ ሰአት በሀገር ቤትም ሆነው በሰላማዊ መንገድ እየታገሉ ያሉ የፖለቲካ ድርጅቶች ይሁኑ ወይም በውጭ ሆነው በሁለገብ ትግል እየታገሉ ያሉ የፖለቲካ ድርጅቶች አላማቸውም ሆነ ጥያቄያቸው አንድ ነው የስልጣን ወይም የገንዘብ ሳይሆን የነጻነት ጥያቄ ነው :: የኢትዮጵያ ሕዝብ ነጻነት ያስፈልገዋል   ::እኛም  ሰላምና ነጻነት የናፈቀን ህዝቦች መብታችንን ለማስከበር ለነጻነት ከሚታገሉ ድርጅቷች ጎን በመቆም ለነጻነታቸው ሲታገሉ  በወያኔ አንባገነን ትህዛዝ ወደ እስር እየተወረወሩ እና በግፍ እየተሰቃዩ ላሉ ወገኖቻችን  ከመንኛውም ጊዜ በተለየ መልኩ ሀገራዊ ስሜት ተሰሞቶን ልንጮህላቸውና የእነሱንም ፈለግ በመከተል ከሁለት አስርት አመታት በላይ የዜግነት መብታችንና እየረገጠና ነጻነታችንን እያፈነ ህዝባችንን ለስደት እያደረገ ያለውን ያለውን ይኼን ሰይጣናዊና አረመናዊ ስርዓት በማንኛውም መንገድ በመታገል፣እውነተኛ ሰላምና ነጻነት በኢትዮጵያ ምድራችን እንዲመጣ ለማድረግ የወያኔን መንግስት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ዳግም እንዳይነሳ  አከርካሪውን ሰብሮ መጣል  ይጠበቅብናል እላለው::የዜጎች ነጻነት ማጣት ፣መሰቃየት፣ መታሰርና መሰደድ ግድ ብሎን እያንዳንዳችን ትግላችንም ሆነ አላማችን በእውነተኛ የነጻነት ትግል በመነሳት የወያኔን መንግስት ጥሎ ነጻነትን ለመቀናጀት በኢትዮጵያዊ  ስሜትና ተነሳሽነት ከሆነ ድልን የምንቀድጅበት ቀን ሩቅ መስሎ አይታየኝም::

  ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ !!!
gezapower@gmail.com

Wednesday, August 27, 2014

ሙስና ለሶስት የሰነጠቃቸው ቡድኖች

August27/2014
ወያኔ ኢህአዴግ በጠመንጃ ኃይል ሥልጣን ላይ ፊጥ ካለ ድፍን 23 ዓመት ቆጠረ፡፡ ህወሃት/ኢህአዴግ በአንቀልባ አዝሎ ለሥልጣን ያበቃው ዛሬ አምርሮ የሚጠላው ሻዕቢያ ነው፡፡ ወያኔ እና ሻዕቢያ ውሃ በወንፊት እንቅዳ ባሉበት የፍቅር ዘመን እነኢሳያስ አፈወርቂ ኦፊሻል ባልሆነ መንገድ ጥሬ ሥጋ ለመቁረጥ በየሳምንቱ አዲስአበባ ይመላለሱ እንደነበር የቅርብ ሰዎች የሚያስታውሱት ነው፡፡
Muktar-300x142ዛሬስ፤ እነዚህ ሁለት ኃይሎች ለመጠፋፋት የሚፈላለጉ ሆነው ተፋጠዋል፡፡ የሚገርመው ወያኔ፤ የሻዕቢያ ጉዳይ አስፈጻሚ ሆኖ ሀገርን ያህል ነገር ማስገንጠሉን፣ አሰብን አስረክቦ ሀገሪቱን ያለወደብ ማስቀረቱን ጭምር እየረሳ የዛሬ ተቃዋሚዎችን ለምን ከሻዕቢያ ጋር ታያችሁ፣ገንዘብ ተቀበላችሁ እያለ በሀገር ክህደት ጭምር ለመክሰስ ሞራል አግኝቶ ሲወራጭ ማየት ነው፡፡ የትላንቱ የነጻነት ታጋዮች ለሕዝብ ነጻነትና ዴሞክራሲ ታግለናል እያሉ ከ20 ዓመታት ጉዞ በሁዋላ የተትረፈረፈ ነጻነቱን ለራሳቸው ሰጥተው ሌላውን ለመጨፍለቅና ትላንት ባወገዙት የደርግ መንገድ ለመጓዝ አላቅማሙም፡፡
ወደ ሰሞነኛ ጉዳይ እንመለስ ጄኔራል ባጫ ደበሌ አሜሪካን ሀገር ቤት ገዛ የሚል ገራገር ዜና ሰሞኑን በማህበራዊ ድረገጾች ሳነብ አባይን ያላየ ምንጭ ያደንቃል ብዬ በውስጤ አጉተምትሜያለሁ፡፡ የሌባው ቡድን መስረቅን እንደመብት ቆጥሮ በአዲስአበባ ከተማ ቀብረር ያለ ህንጻ በዘመድ አዝማዱ ሰም ሲገነባ ትንሽ እንኳን ሼም እንደሌለው ስትታዘብ ጄኔራሉ በአድራጎቱ አፍሮ ትንሽ ራቅ፣ ደበቅ ለማለት የመፈለጉን ነገር ታመሰግናለህ፡፡ የሌባው ቡድን 5ሺ ብር የማትሞላ ወርሃዊ ደመወዝ ይዞ ልጆቹን በውጪ ሀገር ውድ ት/ቤት ጭምር ሲያስተምር፣ ሚስቱ የሚሊየን ብሮች መኪና ስታሽከረክር፣ ባለቅንጦት ቪላ ገንብቶ ሲንጎማለል ስታይ ጄኔራሉ አንድ ቤት ቢገዛ ታዲያ ምን ይጠበስ ልትል ትችላለህ፡፡ እናም የመከላከያ ወታደሮችን ይጭነቃቸው እንጂ ጄኔራሎቹማ ዛሬ ቢጠሩዋቸው የማይሰሙ ቱጃሮች ሆነዋል፡፡ የሚገርመው ግን እነዚህ ጄኔራሎች ነገ ጥቅማቸውን የሚነካ ነገር ቢመጣ ብረት ላለማንሳታቸው ልማታዊ መንግሥታችንም እንኳን እርግጠኛ መሆን አለመቻሉ ነው፡፡ ኢህአዴግ ነፍሴም «ሙስናን እንዋጋለን» በሚል መፈክር ታጥሮ የሚኖረው ለዚህ ሳይሆን ይቀራልን?!
በአሁን ወቅት ገዥያችን ኢህአዴግ ለሶስት የመሰንጠቅ አዝማማያ እየታየበት ይገኛል፡፡
ቡድን አንድ የደረጀው የሌባ ቡድንን ያቀፈ ነው፡፡ ይህ ቡድን ከፍተኛ መንግሥታዊ ሥልጣኑን የተቆጣጠረ ስለሆነ ጥቅሙን ለማስጠበቅ ማንኛውንም የኃይል እርምጃ የሚወስድ፣ ጥቅሙ ሲነካ ወይንም ይነካል ብሎ ሲሰጋ ሰዎችን የሚያስር፣ የሚያሳድድ የጨካኞች ስብስብ ነው፡፡ እስከታችኛው ድረስ የራሱ መዋቅር የዘረጋና ብዙ ጀሌዎች ያሉት በመሆኑ ተጽእኖው የሰፋ ነው፡፡
ቡድን ሁለት ሟቹ ጠ/ሚኒስትር በአንድ ወቅት እንዳመነው ነገ ይቀናኝ ይሆናል ብሎ የተቀመጠ ተስፈኞች የተሰባሰቡበት ቡድን ነው፡፡ ይህ ቡድን የሌባው ቡድን ስላላስጠጋው አምርሮ እየተቃወመና ብሶቱን እየገለጸ ያለና እንደእስስት ገላውን የሚቀያይር ቡድን ነው፡፡ በተመቸው ጊዜ የሚደግፍ፣ ያልተመቸው ሲመስለው የሚቃወም እበላ ባይ የአደገኛ ሰዎች ስብስብ ነው፡፡ ይህ ቡድን በአመዛኙ በታችኛው እርከን ላይ ተከማችቶ የሚገኝ በመሆኑ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በማባባስና በማወሳሰብ ዘወትር ቢወቀስም ምንም ለውጥ ማምጣት ያልቻለ ነው፡፡
ሶስተኛው የኢህአዴግ አባልም ደጋፊም ሆኖ እውነተኛ ዜጋ ሲሆን ሁለቱን ወገኖች የሚጠላ፤ ግን ተጋፍጦ ለመታገል አቅምና ድፍረት ያጣ ነው፡፡
በሒደት አንዱ ነጥሮ መውጣቱ የማይቀር ነው፡፡

( የእኔ የለጣፊው አስተያየት- አጠቃላይ ድርጅቱ የሚጠፋበት ጊዜ ሩቅ አይሆንም

ከፖለቲካ ተሰናባቹ አቶ ሙሼ ሰሙ ስለ ኢትዮጵያ ወቅታዊ ፖለቲካ

August 27/2014
“የኢህአዴግ አስቸጋሪ ባህሪዎች ትግሉን ውስብስብና እልህ አስጨራሽ አድርገውታል”
“ተቃዋሚ ፓርቲዎች መንግስት ለመሆን የሚያስችል ቁመና አልፈጠሩም”
የኢትዮጵያውያን ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ)ን ከመሰረቱት አንጋፋ ፖለቲከኞች አንዱ የነበሩት አቶ ሙሼ ሰሙ ባለፈው ሳምንት ከፖለቲካ ፓርቲ ራሳቸውን ማግለላቸውን አስታውቀዋል፡፡ ኢዴፓን ከ92 ዓ.ም ጀምሮ በህዝብ ግንኙነት ሃላፊነት፣ በዋና ፀሐፊነትና በፕሬዚዳንትነት ያገለገሉት አቶ ሙሼ፤ ከፓርቲያቸው መልቀቃቸውን ምክንያት በማድረግ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው በአገሪቱ ወቅታዊ ፖለቲካ ዙሪያ በስፋት አነጋግራቸዋለች፡፡ በተለይም በተቃዋሚ ፓርቲዎች የፖለቲካ እንቅስቃሴ ዙሪያ፣ኢዴፓና እሳቸው ለአገሪቱ ስላበረከቱት አስተዋጽኦ፣ስለመጪው ምርጫ፣ ስለተከሰሱት የግል የፕሬስ ውጤቶች፣ ስለኢህአዴግ…እና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን ተጠይቀው ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
Mushe Semu
Mushe Semu
– ባለፈው ሳምንት ከፓርቲ ፖለቲካ ራስዎን እንዳገለሉና ለፓርቲዎ የመልቀቂያ ደብዳቤ እንዳስገቡ በይፋ አስታውቀዋል፡፡ ምክንያትዎን ቢያብራሩልን?
አቶ ሙሼ ሰሙ- ከኢዴፓ ጋር ላለፉት 15 ዓመታት ቆይቻለሁ፡፡ በፓርቲው ውስጥ የአመራርነት ሚና ነው የነበረኝ፡፡ ሰነድ በማዘጋጀት፣ የፓርቲውን የፖለቲካ ፍልስፍናና አቅጣጫ በመቅረፅ—ስራ እሳተፍ ስለነበር ፋታ ኖሮኝ አያውቅም፡፡ የኢትዮጵያ የተቃውሞ ትግል ጫና የበዛበት ነው፡፡ በዚህ ቦታ በአንድ መስክ ተሰማርቶ መቆየት ቆም ብሎ ራስን ለመፈተሽና ለመገምገም ጊዜ አይሰጥም፡፡ የሄድኩበት መንገድ ምን ያህል ውጤታማ እንደነበረ፣ ከዚህስ ማህበረሰቡ ምን ተጠቅሟል—የሚለውን ለመረዳት ትንፋሽ መውሰድ —- ራሴን ማረጋጋት አለብኝ ብዬ ወስኛለሁ፡፡ ከተቋማዊ አሰራር ወጣ ብዬ ራሴን መገምገም ፈልጌአለሁ፡፡
የኢትዮጵያ የተቃውሞ ትግል ውስጥ እንደ ባህል የተለመደ ነገር አለ፡፡ ሰዎች ሰሩም አልሰሩም፣ፋይዳ ኖራቸውም አልኖራቸውም ተቃዋሚ ፓርቲ ውስጥ ዝም ብሎ የመቆየት ባህል፡፡ እየታገሉ መኖር ይቻላል፤ ነገር ግን ለመኖር ብቻ የሚኖርበት ሁኔታ አለ፡፡ እዚያ ፓርቲ ውስጥ መቆየቴ አንድ ቀን ለውጥ ይመጣና የማገኘው ጥቅም ይኖራል ብለው የሚያስቡ አሉ፡፡ ወይንም ደግሞ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ይሻሻልና ሚናዬን ለመፈተሽ እድል ይሰጠኛል በሚል ሊቆዩ ይችላሉ፡፡
አቶ ሙሼ ሰሙ-
 እኔ ግን በአንድ ፓርቲ ውስጥ እስከአለሁ ድረስ ስራዬን መስራት አለብኝ ብዬ አምናለሁ፡፡ የሚገባውን ሰዓትና ጊዜ ሰጥቼ ኃላፊነቴን መወጣት አለብኝ፡፡ አሁን ባለሁበት ሁኔታ የስራዬ ባህሪ፤ ለረዥም ጊዜ ባለማቋረጥ በትግሉ ውስጥ በመቆየቴ፤ የቆየሁባቸውም ጊዜያቶች በከፍተኛ አመራር ውስጥ በመሆኑ—-ቆም እንድልና ራሴን እንድመረምር አስገድዶኛል፡፡ ለእንጀራ የሚሰራ ስራም ቢሆን እኮ 15 ዓመት ይሰለቻል፡፡
-የእርስዎን ከፓርቲ ፖለቲካ ራስን ማግለል አስመልክቶ አንዳንድ ወገኖች “መጪውን የ2007 ምርጫ ሽሽት ነው፤ ከፖለቲካ ጫና ራስን ለማግለል ነው” የሚል አስተያየት ሲሰነዝሩ ይሰማል…
አቶ ሙሼ ሰሙ-
ሰዎች ብዙ ነገር ሊሉ እንደሚችሉ እገምታለሁ። ቁምነገሩ ግን ከእኔ እምነትና አስተሳሰብ ጋር ነው ያለው፡፡ በአለፉት 15 የትግል ዓመታት ከተቃዋሚዎችና ከመንግስት በኩል የተለያዩ ጫናዎችን አሳልፌያለሁ፤ ታስሬያለሁ፤ ተሰድጃለሁ፡፡ ይሄን ሁሉ ጫና ተቋቁሜ መጥቻለሁ፡፡ ከ1997 ዓ.ም በኋላ ደግሞ ተቃዋሚው ኃይል የነበረው ጫና፣ ግፊት፣ ስም ማጥፋትና ዘመቻው እጅግ ከባድ ነበረ፡፡ በዚያን ጊዜም ቢሆን ሃሳቤን አልለወጥኩም። ጫናን የምፈራ ቢሆን ኖሮ ወደ ትግሉ አልመጣም ነበር፤ እነዚያን የጫና ዘመኖች ተቋቁሜ አላልፍም ነበር፡፡ በምርጫ ወቅት የስራ ጫና ይበዛል፤ የሚያሳድረው ተፅዕኖም ቀላል አይደለም፡፡ በየአካባቢው ተሂዶ አባላት ከመመልመል ጀምሮ ቅስቀሳ እስከ ማድረግ ያለው ስራ ከባድ ነው፡፡ “እንደዚህ አይነት ከባድ ስራ አሁን መቋቋም ትችላለህ ወይ?” ብትይኝ፣ አሁን አልችልም። እረፍት እፈልጋለሁ፤ ትንፋሽ መውሰድ አለብኝ፤ ራሴንም ቆም ብዬ መገምገም ያስፈልገኛል፡፡ እንደ ሀገራዊ ምርጫ ያለን የምርጫ ዘመቻ ለመምራት ጊዜ ያስፈልጋል፣ መረጋጋትን —- አእምሮ ነፃ ሆኖ መዘጋጀትን ይጠይቃል።
-ምርጫውን ሽሽት ነው የሚሉ ተሳስተዋል ማለት ነው?
አቶ ሙሼ ሰሙ-
በኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት አምስት ጊዜ አገር አቀፍ ምርጫ ተደርጓል፤ በአራቱ ተሳትፌያለሁ፡፡ የተለየ የምርጫ ባህሪ የታየበት 1997 ዓ.ም ነው፡፡ የተለየ ባህሪ እንዲኖረው ያደረገው ትግሉ የሄደበት መንገድ የፈጠረው ችግር ነው፡፡ በፖለቲካው ታስሬበታለሁ፡፡ ከምርጫው ውጪ በነበረ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ታስሬያለሁ፣ ተሰድጃለሁ፡፡ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ትግል ውስጥ ከዚህ በላይ ሊኖር አይችልም፡፡ መጪው ምርጫ እንደዚህ ቀደሙ አስቸጋሪና የተወሳሰበ ነው ብዬ አላምንም፡፡ በውጤቱም ቢሆን ብዙ ትርጉም ያለው ነገር ይገኝበታል ብዬ አላስብም፡፡ ተቃዋሚውም ኃይል በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ መንግስትን የሚገዳደርበት ጉልበት እየፈጠረ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ስለዚህ መጪው ምርጫ ለተቃዋሚው በጎ ነገሮች አያመጣለት ይሆናል እንጂ ችግር የሚከሰትበት ነው ብዬ አላምንም፡፡ የ2007 ዓ.ም ምርጫ ከእኔ ውሳኔ ጋር ምንም ግንኙነት የለውም፡፡
-አሁን ባሉት የኢዴፓ አመራሮች ፓርቲው በመጪው ምርጫ ውጤት ያመጣል ብለው ያስባሉ?
አቶ ሙሼ ሰሙ-
 ሰዎች እንደየአቅማቸው የተለያየ ባህሪና አቋም ይኖራቸዋል፡፡ ለፖለቲካ ፓርቲዎች ጠቃሚ የሆኑ ሰዎች ይኖራሉ፡፡ አሁን ኢዴፓ ውስጥ ያሉት አብዛኞቹ አመራሮች ወጣቶች ናቸው፡፡ በትግል ተመክሮዋቸው ጠልቀው የሄዱ አይደሉም፡፡ ነገር ግን ሌሎች ጠንካራ ጐኖች አሏቸው። እኛ ስንጀምር ኢዴፓን ኢዴፓ ለማድረግ ትልቁ ጉልበታችን ወጣቶች መሆናችን ነበር፡፡ አሁን አርጅተናል ማለቴ አይደለም፡፡ ሰርተን አይደክመንም፤ ሀሳባችንን በሰዎች ዘንድ ለማስረፅ አንታክትም፡፡ ያ የፓርቲያችን ጠንካራ ጎን አሁንም ኢዴፓ ውስጥ አለ፡፡ አሁን ፓርቲው ውስጥ ያሉት ልጆች እየተማሩ ያሉ ናቸው፡፡ በሚኖሩበት አካባቢ እና በማህበረሰቡ ዘንድ ተቀባይነት ያላቸው ልጆች ናቸው። የእኛን ዓይነት ተመክሮ ላይኖራቸውና አጋዥ ኃይል ላይሆናቸው ይችላል፡፡ ይሄ አስቸጋሪም ቢሆን መታለፍ ያለበት ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ በሰው ላይ እየተማመኑ ፖለቲካ ማራመድ አይቻልም፡፡ እያንዳንዱ ሰው ትግሉን እየተገዳደረ እያሸነፈ፣ እየሰበረ፣ እየለወጠ መሄድ አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ ሊቸገሩ ይችላሉ፤ ችግሩ ግን የትግሉ አካል ነው፡፡ አቅማቸውን ለማጠናከርና ለማጎልበት ጥረት ማድረግ አለባቸው፡፡ ያለው ተጨባጭ ሁኔታም ያግዛቸዋል፡፡ ምክንያቱም በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው ቅሬታ የሰላ ነው፡፡ ማህበረሰቡ ለኢህአዴግ ያለው እምነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሸረሸረ መጥቷል። ድህነት፣ ረሃብ፣ ስራ አጥነት፣ የአገልግሎት እጦት፣ የትራንስፖርት ችግር— እነዚህ ሁሉ ቅራኔዎች በቅጡ ከተያዙና ከተጠቀሙባቸው ሌላ ተጨማሪ መታገያ ያስፈልጋቸዋል ብዬ አላምንም፤ እናም ለውጤት ብዙ ሩቅ አይደሉም፡፡
- “ሶስተኛ አማራጭ” የሚለው የፓርቲው ስትራቴጂ አሁንም ቀጥሏል?
አቶ ሙሼ ሰሙ-
 ሶስተኛ አማራጭ የፓርቲው መሰረታዊ አቋም ነው፡፡ ይሄን አቋም የሚሸረሽርበት፤ አስተሳሰቡን የሚለውጥበት ምክንያት ይኖረዋል ብዬ አላምንም፡፡ እስካሁን ካለኝ ተመክሮ ለኢዴፓ የተለየ ዋጋ ከሚያሰጡት ነገሮች አንዱና ሊደርስበት ላሰበው ግብ እንደ ትግል ስልት የሚጠቅመው መንገድ ይሄ ብቻ ነው ብዬ ነው የማምነው፡፡ ከዚህ በተረፈ እኔ የምወስነው ጉዳይ አይደለም፡፡ አሁን እኔ ኢዴፓ ውስጥ አይደለሁም፤ ኢዴፓ ውስጥ ያሉ ሰዎች “ለትግል የሚያዋጣን ስልት ይሄ ነው” ብለው እስከአመኑ ድረስ ይቀጥሉበታል፡፡ ይሄ የእነሱ ውሳኔ ነው የሚሆነው።
-በ15 ዓመት የትግል ዘመንዎ፣ ለኢትዮጵያ ምን አበረከትኩ ብለው ያስባሉ?
አቶ ሙሼ ሰሙ-
ትልቁ ነገር ኢዴፓን መመስረታችን ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘበት ጊዜ ጀምሮ ኢዴፓ ፓርቲ እስከሆነበት ጊዜ ድረስ የህብረ ብሄራዊ አስተሳሰብና አጀንዳ እጅግ የተዳከመበት ጊዜ ነበር፤ ህብረ ብሄራዊነት የሚያዋጣ የትግል ስልት እንደሆነ አምነን፤ ህዝቡንም አሰባስበን ለሚፈልገው ግብ ለማድረስ፣ አደረጃጀትን በዚህ መንገድ መቀየድ ጥሩ ነው የሚለውን ነገር እንደ አስተሳሰብ በህብረተሰቡ ውስጥ እንዲሰርፅ ማድረጋችን ትልቁ ድላችን ነው፡፡ በዚያን ወቅት በህብረ ብሄራዊ አስተሳሰብ የተደራጀ ማንም አልነበረም፡፡ ለረዥም ጊዜ በህብረ ብሄራዊነት መደራጀት ተቀባይነት የሌለው አስተሳሰብ ሆኖ የቆየበት ጊዜ ስለነበር፣ ያ ትልቁ አስተዋፅኦዬ ነው እላለሁ፤ እንደ ድርጅት፡፡
ሰላማዊ ትግል ብቸኛው አማራጭ መሆኑን፣ በሰላማዊ ትግል ውስጥም ህገ መንግስቱን ማክበርና ልዩነቶችን በግልፅ አውጥቶ መታገል እንደሚቻል… ይሄን አስተሳሰብ በተቃዋሚ ፓርቲዎችና በህዝቡ ውስጥ ማስረጽ ችለናል፡፡ እኛ ወደ ትግሉ ከመምጣታችን በፊት ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች በአብዛኛው ህገ መንግስቱን የሚያዩበት መንገድ የተዛባ ነበር፡፡ ህገ መንግስቱን ያለመቀበል (አንዳንዶቹ እንደውም ቀዶ መጣል ነው የሚል አስተሳሰብ ነበራቸው) ሁኔታ ይታይ ነበር፡፡ ያንን ሁሉ ማሸነፍ ችለናል ብዬ አምናለሁ፡፡ ያ ደግሞ ትልቁ አስተዋፅኦ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ በኢትዮጵያ የተቃውሞ ትግል ውስጥ በበርካቶቹ ዘንድ የተለመደው መፈክር ነበር፡፡ ብዙዎቹ የፖለቲካ ፓርቲዎች ርዕዮት ዓለም፤ የፖለቲካ ፍልስፍና አልነበራቸውም፡፡ የፖለቲካ ፍልስፍናን በኢትዮጵያ የተቃውሞ ትግል ውስጥ አስተዋውቀናል፡፡ ማስተዋወቅ ብቻ አይደለም፤ ቀላል የማይባሉ ሰነዶችን አዘጋጅተናል፡፡
የፓርቲውን ፕሮግራም፣ በብሄራዊ እርቅ፣ በአብዮታዊ ዴሞክራሲ—ወዘተ አምስት ጥራዝ ሰነድ አዘጋጅተናል፡፡ ከዚያም በተከታታይ ሰፊ ሰነድ አዘጋጅቷል ኢዴፓ፡፡ ቀደም ሲል ትግሉን የሚመሩት አስተሳሰቦች ሳይሆኑ መፈክሮች ነበሩ፡፡ ዛሬ ሁሉም የተቃዋሚ ፓርቲዎች የፖለቲካ ርዕዮት አለም ሰነዶች አሏቸው፡፡ ሌላው ኢዴፓ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ያስተዋወቀው ለምርጫ ክብር መስጠትን ነው፡፡ በሰላማዊ ትግል ውስጥ ምርጫ ብቸኛው የስልጣን ማግኛ መንገድ እንደሆነ በማያሻማ መልኩ በተቃዋሚው ዘንድ እንዲሰርፅ አድርገናል፡፡ ለምርጫ የሚመጣ ማንኛውም ኃይልም አማራጭ ሃሳብ ይዞ እንዲመጣ (ማኔፌስቶ እንዲያዘጋጅ) አነቃቅተናል፡፡ የመጀመሪያ የማኔፌስቶ ባለቤት ኢዴፓ ነው፡፡ ለቅንጅትም ማኔፌስቶ ያበረከትነው እኛ ነን። ፈፅሞ የተዘነጋውና ትርጉም የለውም ተብሎ ይቆጠር የነበረውን የባህር በር ጥያቄ ዛሬ የሁሉም ፓርቲዎች መፈክር ማድረግ ችለናል፡፡ ከ1.5 ሚሊዮን በላይ ፒቲሽን አስፈርመን ለተባበሩት መንግስታት አቅርበናል፡፡ ውጤቱ ምንድን ነው ብለሽ እንዳትጠይቂኝ፡፡
ከ1997 ዓ.ም የምርጫ ጊዜ በኋላም ትግሉ አደጋ ደርሶበት በነበረበት ጊዜ ማህበረሰቡ ቆም ብሎ ጉዳዩን እንዲያጤን፣ በስሜት ሳይሆን በምክንያት እንዲታገል ሶስተኛው አማራጭን እንደ ሀሳብ ፓርቲው ይዞ መጥቷል፡፡ እነዚህ የጠቀስኩልሽ ነገሮች በሙሉ በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ የእኔ አሻራ አለባቸው፡፡
-ቀጣዩ ምርጫ በ97 ዓ.ም. ከነበረው ምርጫ ጋር ሲነፃፀር ሊሰጠው የሚገባውን ግምት ሊገልጹት ይችላሉ?
አቶ ሙሼ ሰሙ-
በአሁኑ ጊዜ ያሉ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች በምርጫ አሸንፈው ስልጣን የሚይዙ ናቸው ብዬ አላምንም፡፡ ኢህአዴግን ግን ሊገዳደሩት ይችላሉ። በርከት ያለ ቁጥር አግኝተው ተወካዮች ምክር ቤት የመግባት እድል ሊኖራቸው ይችላል፡፡ በተረፈ ግን በተጨባጭ መንግስት ለመሆን የሚያስችል ቁመና አልፈጠሩም፡፡ ግልፅ ነው፤በቂ ህዝብ በደጋፊነት ማሰለፍ አልቻሉም፡፡ ኢህአዴግም ብዙዎች እንደሚያወሩት ዝም ብሎ ለጥቅማቸው፣ ለሆዳቸው፣ ለጊዜያዊ ፍላጎታቸው ያደሩ ሰዎች የተሰበሰቡበት አይደለም፡፡ እንደ ድርጅት በእምነት የሚከተሉት ቀላል የማይባል አባላቶች አሉት። የሚደረገው ውድድር ዝም ብሎ በአየር ላይ ካለ ድርጅት ጋር አይደለም፡፡ ውድድሩ በደንብ በህዝቡ ውስጥ መደላደል ይዞ ከሚንቀሳቀስ ድርጅት ጋር ነው። በፋይናንስ፣ በሰው ሃይል አቅም… መንግስት በመሆኑ ከሚፈጥረው ተፅዕኖ አኳያ በቀላሉ ልታሸንፊው የምትችይው ፓርቲ አይደለም፡፡
ከዚህ አኳያ ተቃዋሚዎችን ስታይ ደግሞ በተቃራኒው ነው፡፡ በሰው ሃይል ሲታዩ በተደጋጋሚ ተመሳሳይ አመራሮች የሚታዩበት እውነታ ነው ያለው፡፡ የተለያዩ ሰዎች በተለያዩ ጊዜ በቅለው ሲጎለብቱና ሲጠነክሩ አናይም፡፡ ሁሌም የተለመዱ ፊቶች፣ ሰዎች፣ አመራሮችን ናቸው ያሉት፡፡ ከአንዱ ፓርቲ ወደ አንዱ ፓርቲ ሲሄዱ ነው የምናው፡፡ ይሄ አንደኛው የድክመታቸው መገለጫ ነው፡፡ በአብዛኛው ከተማ ተከል ናቸው፡፡ ከአዲስ አበባና ከክልል ከተሞቹ ውጭ ገጠር ሄደው አርሶ አደሩን በቅጡ መድረስ የቻሉ አይደሉም፡፡ ለዚህ ምክንያት ሊደረደር ይችላል፡፡ አብዛኛው ማህበረሰብ በገጠር የሚኖር እንጂ በከተማ የሚኖረው 15 ፐርሰንቱ ነው። አጠቃላይ የከተማው 15 ፐርሰንቱ ቢደግፋቸውም እንኳን በምርጫ ሊያመጡት የሚችሉት ነገር የለም፡፡ እነዚህ ሃይሎች ለዚህ ያበቃቸው መሰረታዊ ምክንያት በ1997 ዓ.ም. የተፈጠረባቸው ችግር ነው ከተባለ— አዎ። በርግጥ ብቸኛው ምክንያት አይደለም፡፡ አብዛኞቹ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች በአፈጣጠራቸው ችግር አለባቸው፡፡ በውስጣቸው ዲሞክራሲያዊ አስተሳሰብ በደንብ ሰርጽዋል ብዬ አላምንም፡፡ በምርጫ ሲወርዱና ሰዎች ሲተኩ አናይም፡፡ በውስጣቸው ዲሞክራሲ ያላበበ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ለህዝብ ዲሞክራሲ ለመስጠት ዝግጁ ናቸው ብሎ የሚያምናቸው የለም፡፡ ከባህሪም አኳያ ስታይው እየተካሄደ ያለው ትግል የአስተሳሰብ የበላይነትን ከመፍጠር ይልቅ የአርበኝነት መንፈስ ያየለበት ነው፡፡ የምናየው ኢህአዴግን ለመጣል የሚደረግ ትግል እንጂ አስተሳሰብን በህዝቡ ውስጥ አስርጾ መንግስት ለመሆን የሚያስችል አቅም ወይንም አቋም አይደለም፡፡ በአንድ ወይም በሌላ መንገድ ኢህአዴግ እንዲወድቅ መመኘት ብቻ ነው፡፡ በርዕዮት ዓለም አለምም ደረጃ ጠንከር ጠብሰቅ ብለው የሚሰሩ ነገሮች አይታዩም፡፡ እነዚህ እነዚህ ሁሉ ከመነሻቸው ድክመቶቻቸው ናቸው፡፡
-በ1997 ዓ.ም. የተፈጠረው ችግር ደግሞ የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች በህዝብ ዘንድ የነበራቸውን እምነት እንዲያጡ አድርጓል፡፡ መከፋፈሉ፣ የተፈጠረውን እድል መጠቀም አለመቻላቸው፣ በኋላም ከእስር ቤት ወጥተው ራሳቸውን አጎልብተው በብቃት አለመራመዳቸው —- ህዝብ የነበረውን እምነት ጥርጣሬ ላይ ጥሎታል፡፡
በዚህ ሁሉ ሂደት የኢህአዴግ አስተዋጽኦ ምንድነው?
አቶ ሙሼ ሰሙ-
 የኢህአዴግን ችግርን ማየት ይቻላል፡፡ ኢህአዴግን እንደ ድርጅት ሳየው አንድ የተለየ ተልዕኮ ይዞ እንደመጣ ተዓምር አድርጐ ነው ራሱን የሚያስበው፡፡ ይሄንን የሚደግፈው ደግሞ ሰማዕታትንና የተከፈለውን መስዋዕትነት በመጥቀስ ስለሆነ፣ የአስተሳሰብ የበላይነትን ለመቀበል የተዘጋጀ ድርጅት አይደለም፡፡ ስለዚህ ለረጅም ዘመን በስልጣን ላይ ለመቆየት ሲል ማንኛውም ተፅዕኖ ያደርጋል፡፡ ቀድሞ ግብ አስቀምጦ፣ ከግቤ ከመድረሴ በፊት ማንኛውንም ሃይል መታገስ አልችልም ብሎ የሚያምን ድርጅት ነው፡፡ ምርጫ ይካሄዳል፡፡ ምርጫ ማድረግ ብቻውን ግን አንድን አገር ዲሞክራሲያዊ አያስብላትም፡፡ የምርጫ ውጤትም ትርጉም አለው፡፡
መንግስት በተቃውሞ ትግል ውስጥ ያለው ሚና መንግስት እንደ ኢህአዴግ፤ ኢህአዴግ እንደ ኢህአዴግ ማየት ይቻላል፡፡ መንግስት ብዙ ጊዜ መንግስትነቱና ኢህአዴግነቱ ይምታታበታል፡፡ የዚህ ስርዓት ፈጣሪም ባለቤትም ስለሆነ፣ ይሄ ስርዓት በሌላ አስተሳሰብ ተፈትሾ፣ ከስልጣን ወርዶ ስለማያውቅ ስርዓቱንና ኢህአዴግን መንካት አንድ ሆነዋል፡፡ ስርዓቱን ስትታገይ ኢህአዴግን መታገል ነው፤ ኢህአዴግን ስትታገይ ስርዓቱን መታገል ነው፡፡ እነዚህ ነገሮች እየተፈራረቁ በመጡበት ሁኔታ መቼም ቢሆን የአስተሳሰብ ለውጥ በአገሪቱ ውስጥ እንዲሰርፅ አያደርግም፡፡ የኢህአዴግ አስቸጋሪ ባህሪዎች ትግሉን ውስብስብ፣ በጣም አድካሚና እልህ አስጨራሽ አድርገውታል፡፡
-ስለ ህዝቡስ አስተያየትዎ ምንድነው?
አቶ ሙሼ ሰሙ-
ህዝቡም ጋር ስትመጪ ቀላል የማይባል ችግር አይደለም ያለው፡፡ ህብረተሰቡ ለፖለቲካ ያለው ዝንባሌ በፍርሃትና በስጋት የተሞላ ነው፡፡ የትግሉ ባለቤት መሆን አልቻለም፡፡ ከተቃዋሚዎች የሚቀርብበት ወቀሳ ሊኖር ይችላል፡፡ የማህበረሰቡ ንቃተ ህሊናና ለመረጃ ያለ ቅርበት በራሱ ችግር ነው፡፡ ትግሉ በእነዚህ መንገዶች በማይታገዝበት ሁኔታ የተቃዋሚዎች ሚና ደካማ መሆኑ አይቀርም፡፡ ተቃዋሚዎች ተጨባጭ ሁኔታው የማይፈቅድላቸው ነገር አለ፡፡ ስራውን ለመስራት የሚያስችል በቂ ምህዳር የለም፡፡ ከኢህአዴግ በኩል ያለው ተፅዕኖ በጣም ከባድ ነው፡፡ ማህበረሰቡ ውስጥም ራስን የትግሉ ባለቤት አድርጎ የሚገኘውን ጥቅም ለመጋራት በቂ ተነሳሽነት አታይም፡፡
-የተቃዎሚ ፓርቲዎች ወዲያው ተዋህደው ወዲያው መከፋፈል፤ እርስ በርስ መወነጃጀል… ህብረተሰቡን ተስፋ አያስቆርጠውም ይላሉ?
አቶ ሙሼ ሰሙ-
በፖለቲካ አስተሳሰብ ዙሪያ ካልተሰባሰብሽ ጥላቻ ፖለቲካ ሊሆን አይችልም፡፡ ጥላቻ ሊወስድ የሚችለው መንገድ አለ፡፡ ኢህአዴግን መጥላት ብቻ በራሱ በቂ ርቀት ሊወስድ አይችልም፡፡ ፍልስፍና ሆኖ፣ የሰው ልብ ገዝቶ ትግልን ሊያጎለብትና ሊያጠነክር አይችልም፡፡ የመቻቻል፣ እውቅና የመስጠት፣ የተሞክሮ አለመኖር፣ የድርጅታዊ ብቃት ማነስ፣ የስልጣን ጥም—- እነዚህ ሁሉ የሚጫወቱት ሚና አለ፡፡ ከፖለቲካ ፍልስፍናው ውጪ፡፡ በአስተሳሰብ ዙሪያ ስትሰባሰቢ እምነትሽ አስተሳሰብ ይሆናል፡፡ ማንም ያንን አስተሳሰብ ቢያራምደው የአስተሳሰብ ባለቤት እስከሆንሽ ድረስ ችግር አይኖርብሽም፡፡ ሲጀመር የጠራ አስተሳሰብ አይደለም ያለው፡፡ ሁሉም የራሱን አስተሳሰብና እምነት በበላይነት ማራመድ ስለሚፈልግ ሽኩቻው የማያቋርጥ ነው የሚሆነው፡፡ ኢዴፓ ውስጥ ጥሩና ጠንካራ የምለው አስተሳሰባችን የጠራ መሆኑ ነው፡፡ እኛ ግለሰብ ላይ ሳይሆን በአስተሳሰባችን ላይ ነው የምናተኩረው። ቦታው ላይ በተቀመጠው ሰው ችግር የለብንም፡፡ በፓርቲ ውስጥ ክፍፍል የሚያመጡት እነዚህ ናቸው፡፡ በውስጣቸው በርካታ ችግር አለ፡፡ ፖለቲካ በትምህርት የሚመጣ ነገር አይደለም፡፡ በተግባር፣ በተሳትፎ ነው ፖለቲካን ማጠናከርና ማዳበር የሚቻለው። ድርጅት የሚጠነክረውና የሚጎለብተው በተሳትፎ ነው፡፡ ጥሩ ጥሩ ሰዎች ስለተሰበሰቡ አይደለም ፓርቲ ጠንካራ የሚሆነው። ፓርቲ በሂደት ነው ሙሉ የሚሆነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ የመድብለ ፓርቲ ሥርዓቱ፣ የተቃውሞ ፖለቲካ ዕድሜው እና ተመክሮው አጭር ነው፡፡ የሚፎካከሩት ድርጅት ደግሞ ያለው ተሞክሮ ቀላል አይደለም፤ የስርዓቱ ባለቤትና ፈጣሪውም ነው፡፡ ስለዚህ ለተቃዋሚዎች ፈተና ነው፡
-በቀጣዩ ምርጫ እንደ ተቃዋሚ ወይንም እንደተፎካካሪ ኢህአዴግን ሊገዳደረው የሚችል ተቃዋሚ ፓርቲ አለ ብለው ያስባሉ?
አቶ ሙሼ ሰሙ-
 እኔ ኢዴፓ ነው፣ ነው የምለው፡፡ ኢዴፓ ውስጥ ስላለሁ አይደለም፡፡ ኢህአዴግ የምርጫ ስርዓቱን ዴሞክራሲያዊ ካደረገው፣ የሚዲያ ተጠቃሚነትን ከፈጠረ፣ ሃሳቦች በደንብ እንዲንሸራሸሩ ሁኔታዎችን ካመቻቸ፣ ሰዎችን ማፈናቀሉን ካቆመ፣ ኢህአዴግን በአስተሳስብ በመገዳደር ብቁ ነው ብዬ የማስበው ድርጅት ኢዴፓ ነው፡፡ የጠራ የጠነከረ አስተሳሰብና አመለካከት ያለው ኢዴፓ ነው፡፡
-በቅርቡ የተከሰሱ የግል የፕሬስ ውጤቶች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ጋዜጠኞችም ሃገር ጥለው ተሰደዋል፡፡ መጪው ምርጫ ነው—-
አቶ ሙሼ ሰሙ-
ከትጥቅ ትግሉ በኋላ ለመጀመሪያዎቹ ሶስትና አራት አመታት በህዝቡ ዘንድ ኢህአዴግ ታማኝነት የነበረው ድርጅት ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ ግን በህዝብ ላይ ያለው እምነት ሁልጊዜ በጥያቄ የተሞላ ነው፡፡ በዚህ ምክንያት አማራጭ ሃሳቦች አንዲጎለብቱና እንዲዳብሩ አይፈልግም፡፡ እናም ማድረግ የሚችለው መረጃዎች ወደ ህዝብ የሚደርሱበትን ድልድዩን ማጥፋት ነው፡፡ የግል ጋዜጦች፣ መጽሔቶች ላይ የሚደርስባቸው ቅጥቀጣ እነሱ የተለየ አስፈሪ ስለሆኑ አይደለም፡፡ በማህበረሰቡና በአስተሳሰቡ መሃል ድልድይ በመሆናቸው ነው፡፡ ስለዚህ ኢህአዴግ እነሱ ላይ የሚያሳድረው ተፅዕኖ ድልድዩን ለመስበር ነው፡፡ ህዝብ ባወቀ በነቃ በተደራጀ ቁጥር እንደሚፈታተነው ያውቃል። ህዝቡን ያወናብዱብኛል፣ ህዝቡን ያሳስቱብኛል፣ እኔ ከምፈልገው መንገድ ያስወጡብኛል የሚል ስጋት አለው። ስለዚህ የህዝብ ልሳን፣ አንደበት ሆነው በማገልገል ላይ ያሉትን ጋዜጦች፣ መጽሔቶች ያዳክማል፡፡
አሁን በቅርቡ መጽሄቶች ላይ የደረሰው ነገር ለእኔ ግልጽ ነው፡፡ ኢህአዴግ አለማቀፍ ተጽዕኖውን አይፈልግም፤ ምክንያቱም ተበዳሪ መንግስት ነው፡፡ በተለያዩ መልኩ የሚደርሱበትን ተፅዕኖዎች ከወዲሁ ለመቋቋም እቅድ አድርጎ ኢህአዴግ የወሰደው የሚመስለኝ፣ የክስ ቻርጁን በግላቸው ከመስጠትና ከማሰር በፊት በቴሌቪዥን እንደ ቀይ ሽብር ማወጅ ነው፤ እናም ተነስተው ይጠፉለታል፡፡ ከዚያ ተገላገልኩ ነው የሚለው፡፡ ሙከራው በከፊል ተሳክቷል፡፡ ጋዜጠኞቹ ጥለው እየሄዱ ነው፡፡ በአዋጅ መልክ ክስ ከቀረ 23 ዓመቱ ነው፡፡ ደርግ ነበር ይሄን ያደርግ የነበረው፡፡ እነዚህ መጽሔቶች በብዙ አቅጣጫ ከፋይናንስ፣ ከአደረጃጀት፣ ከሰው ሃይል አኳያ ቀላል የማይባል ጉልበት የፈጠሩ ናቸው፡፡ ባለፈው አምስት ዓመት እንዴት ህትመታቸው፣ ስርጭታቸው፣ እንደሚጎለብትና እንደሚጠነክር ያውቃል። እነዚህን ማዳከም ነው የያዘው፡፡ በእነሱ ምትክ አዲስ ጋዜጣ ያስገባል፤ አቅማቸው ደካማ ነው፣ እየተቆራረጡም እየተንጠባጠቡም ነው የሚቀጥሉት፡፡ በበቂ ደረጃም ህዝቡን አይደርሱም፤ ይቆማሉ፡፡ ስለዚህ ቀጣይነት፣ ወጥነት፣ ተከታታይነት ባለው መንገድ የሚታገሉትን መጽሔቶች ነው እንዲሰደዱ ወይም ፍርድ ቤት እንዲቆሙ ያደረገው፡፡ ይሄ ምርጫው ላይ ተጽዕኖ ለማሳደር ከመፈለግ ውጭ አይደለም፡፡ ሰው ይወናበዳል፣ ተወናብዶ እኔን አይመርጠኝም፤ የሚል ስጋትና ጥርጣሬ ስላለው ነው፡፡ በዚህ የተነሳ ኢህአዴግ ከእሱ ቁጥጥር ውጪ የሆነ ማንኛውም ሃሳብን ለማራመድ የሚያገለግል መሳሪያ የሚፈልግ አይመስለኝም፡፡ እንደ እኔ አስቡ፣ እንደ እኔ ገምቱ የሚለው ደግሞ አያስኬድም፡፡
-በዓለም ላይ የየሀገሩ ስጋት ተብለው የሚጠቀሱ የሀይማኖት፣ የዘር፣ የአምባገነናዊ ስርዓቶች አሉ፡፡ የኢትዮጵያ ስጋት የትኛው ነው?
አቶ ሙሼ ሰሙ-
ሰዎች በተፈጥሮዋቸው አማራጭ ይፈልጋሉ፤ መፈለግ ብቻ ሳሆን አማራጭንም መፈተሽ ይሻሉ፡፡ አንድ መንግስት ለረዥም ጊዜ እንዲገዛቸው ፈቃደኛ አይደሉም፤ ይሰለቻሉ፡፡ ሰው ስሜቱን፣ ሃሳቡን፣ ፍላጎቱን እንዲያወጣ፣ እንዲገልጽ የሚያደርጉት ጋዜጦች፣ መጽሔቶች ተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶች በተዳከሙ ቁጥር በሰው ውስጥ ያለውን ነገር ለማወቅ እንዴት ይቻላል? ይሄ ደግሞ ወደ አመጽ፣ ወደ አለመረጋጋት ለመለወጥ የማንንም ይሁንታ አይጠብቅም፡፡ በደህንነትና በስለላ መዋቅር የሚቆም አይደለም፤ እንደ ጋዜጦችና እንደ ፓርቲዎች፡፡ ፓርቲዎችን አመራሮችን ሰብስቦ አስሮ፣ ትግሉን ማዳከም ይቻላል፡፡ በህዝብ ውስጥ ያለ ቁጣና ብስጭትን ግን መቆጣጣር አይቻልም፡፡ አንዳንዴ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚታዩ ግጭቶች የዚያ ውጤት ናቸው ብዬ ነው የማስበው፡፡ ኢትዮጵያ እንደ ሃገር ችግር ይገጥማታል ብዬ አላስብም፤ ሊሆንም አይችልም፤ ሆኖም አያውቅም፡፡ ግን ስርዓቱ አደጋ ላይ ይወድቃል፡፡ ስርዓቱ በዚህ መንገድ ያሉትንም እድሎች እያጠበበ፣ እየጨፈለቀ በሄደ ቁጥር ሰዎች በውስጣቸው የሚቀጣጠለው ነገር የበለጠ እየጠነከረ እየጎለበተ ነው የሚሄደው፡፡ ጥያቄያቸው እያደገ ነው የሚመጣው፡፡ የተገኘውን እድል ተጠቅመው ፍላጎታቸውን ለማራመድ ወደ ኋላ አይሉም፡፡ ይህችን አገር ወደ መልካም አስተዳደርና ወደ ዲሞክራሲያዊ አስተሳሰብ ለመውሰድ ከተፈለገ፣ ተጨባጭ ሁኔታው በሚፈቅደው ልክ አሳታፊ የሆነ ስርዓት መገንባት ያስፈልጋል፡፡ ግዴታ ነው፡፡
ግብጽን ብናይ እስከ አሁን ድረስ መውጣት ባልቻለችበት የፖለቲካ ቀውስ እየታመሰች ነው ያለችው። ቀደም ብሎ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ግብጽ ውስጥ በበቂ ሁኔታ ተደራጅተው፤ ትክክለኛ ቦታቸውን አግኝተው፣ ሃሳባቸውን ለመግለፅና ለማራመድ በሩ ክፍት ቢሆን ኖሮ፣ በአመጽና በህዝብ ቁጣ ሳይሆን በተቃዎሚ ፓርቲ ሃይሎች የስልጣን ሽግግር ሀገሪቱ ቀጣይነትዋን ታረጋግጥ ነበር፡፡ ህዝቡ ስሜቱን የገለጸው በምርጫ አይደለም፤ በአመጽ ነው፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎች መኖራቸው ጥቅሙ ህዝብ ፍላጎቱን በምርጫ እንዲገልፅ እድል ይሰጠዋል፡፡ ስለዚህ ለእኔ የሚታየኝ ስጋት ነው። ኢትዮጵያ ውስጥ መንገድ አልተሰራም፤ ልማት አልተካሄደም እያልኩሽ አይደለም፡፡ ስራ አጥነትን ለመቀነስ እንቅስቃሴ የለም፣ ማለቴ አይደለም፡፡ ግን በዚህች አገር ጉዳይ ያገባኛል ብሎ የተነሳ፣ የእኔ አማራጭ ነው የሚሻለው የሚልም አለ፡፡ ይሄ ሰው ሃሳቡ በዲሞክራሲያዊ መንገድ ተደምጦ፣ በምርጫ ተሸንፎ ካልሆነ፣ በጉልበት በማፈን እንዳይራመድ ከተደረገ መጨረሻ ላይ ህዝቡ ውስጥ የሚፈነዳው ሌላ ነገር ነው፡፡

Source: Addis Admas