Friday, June 23, 2017

ሰራዊቱን ዝም ለማሰኘት የታቀደ የመጀመሪያ ዙር ስራ የተቃዋሚ ደጋፊ የተባሉ ወታደሮችን ለማጥቃት የታቀደ ግምገማ ሊደረግ መሆኑ ታውቋል

Juni 23,2017
ከጦር ሃይሎች የተገኘው መረጃ እንደተመለከተው በመከላከያ ሰራዊቱ ሁሉም እዞች በወታደሮች ላይ ግምገማ ሊደረግ መሆኑ ታውቋል::የግምገማው ዋናው ሂደት በሰራዊቱ ውስጥ የተገኘው የኢሕአዴግ ድምጽ አነስተኛ መሆኑ እና ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል ከሚል አንጻር ተጠርጣሪ የተቃዋሚ ደጋፊ የተባሉ ወታደሮችን ለማጥቃት የታቀደ ግምገማ ሲሆን በግምገማው ላይ ሞባይሎች እንደሚፈተሹ እና ተቃዋሚዎችን በተመለከት ውስጥ ለውስጥ ፕሮፓጋንዳ ያራግባሉ እንዲሁም አለማቀፍ ጉዳዮችን በተመለከተ ከሚዲያ መረጃዎችን ይዘው መተው ያወራሉ የሚባሉ ወታደሮች የግምገማው ሰለባ እንደሚሆኑ ውስጥ አዋቂ ምንጮች ተናግረዋል::የመከላከያ ሰራዊቱ ከሲቭል ደህንነት እና ከኢንሳ በተመደቡ እና የወታደሩን ካኪ ለብሰው በመመሳሰል በሚሰልሉ የሕወሓት አባላት አቅራቢነት ወንጀሎች ተቀነባብረው ግምገማውን እንደሚያጦዙት ይጠበቃል ሲሉ ምንጮቹ አክለው ገልጸዋል::
የለውጥ ፈላጊ ሃይሎችን ደግፋችሁሃል በሚል ለጥቃት የተዘጋጀው ይህ ግምገማ አለመተማመን እና ጥርጣሬ በሞላው የመከላከያ ሰራዊቱ ውስጥ ልዩነቶችን በማስፋት በአንድ ብሄር የበላይነት የሚተዳደረውን አምባገነን ወታደራዊ አመራርን በማጠናከር ሌሎች ብሄሮች በፍርሃት እና በስጋት እንዲኖሩ ለማሸማቀቅ የሚያደርግ እንዲሁም ሰራዊቱን ለለውጥ ያነሳሳሉ የሚባሉ መኮንኖችን እና ወታደሮችን ሰብስቦ ለማሰር እና ደብዛቸውን ለማጥፋት የታቀደ እንደሆነ ታውቋል:ግምገማው የሚመራው በተለያዩ እና በጄነራልነት ማእረግ ባላቸው የሕወሓት መኮንኖች ሲሆን ሰራዊቱን ዝም ለማሰኘት የታቀደ የመጀመሪያ ዙር ስራ መሆኑን ምንጮቹ ገልጸዋል::
ይህ በእንዲህ እንዳለ 450 የሕወሓት አባላት ተመልምለው ለወታደራዊ ስልጠኛ በሚል በተለያዩ የምስራቅ አውሮፓ አገሮች ለትምሕርት ሊላኩ መሆኑ ሲታወቅ ከአንድ ብሄር ብቻ ለምን/እንዴት ይህ ሆነ የሚል ጥያቄ መነሳቱን እና ምንም አይነት ምላሽ እንዳልተሰጠው ታውቋል::ምንጮቹ አያይዘው እንዳሉት ልሰላም አስከባሪ ሃይል ከፍተኛ አመራር እንዲሆኑ ለስልጠና የታጩት የሕወሃት አባላት ጉዟቸው እንደማይሰረዝ እና ጉዞውን ለተቃወሙት መኮንኖች ከፍተኛ ጉዳት ሊያስከትል ይችላል ሲሉ ገልጸዋል::
ቆንጂት ስጦታውm