Monday, April 21, 2014

በአፋር የተነሳውን ተቃውሞ ተከትሎ 8 ሰዎች በፌደራል ፖሊሶች ተገደሉ

April 21/2014 

 ቁርቁራ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ በአፋር እና በሶማሊ ጎሳ አባላት መካከል የተነሳውን ውዝግብ ተከትሎ የፌደራል ፖሊስ በወሰደው እርምጃ 8 ሰዎች መገደላቸውን የአካባቢው ሰዎች እና የአፋር ሰብአዊ መብቶች ድርጅት ሲገልጽ ፣ አፋር ህዝብ ፓርቲ ባወጣው መግለጫ ደግሞ የሟቾቹን ቁጥር 12 አድርሶታል።
የፌደራል ፖሊስ የወሰደውን እርምጃ ተከትሎ በአዋሽ ሰባት ኪሎ አካባቢ ህዝቡ ወደ ወደ አውራ ጎዳናዎች በመውጣት ወደ ጅቡቲ የሚሄዱትን መኪኖች ለ12 ሰአታት ያክል አግዷል። የአፋር ክልል ባለስልጣኖች ወደ አካባቢው በመሄድ ህዝቡን ለማነጋገር ቢኖክሩም፣ ህዝቡ ግን አትወክሉንም የሚል መለስ እንደሰጣቸው ታውቋል። 3የመከላከያ ሰራዊት መኮንኖች በ10 ቀናት ውስጥ ችግሩ እንደሚፈታ ቃል ገብተው የመኪና እገታው እንደተጠናቀቀ የደረሰን መረጃ ያመለክታል።
አንድ ስሟ እንዳይገለጽ የፈለገች የአፋር ተወላጅ የ85 ዓመት አዛውንትን ጨምሮ 8 ሰዎች በአሰቃቂ ሁኔታ መገደላቸውን ማየቷን ከኢሳት ጋር ባደረገችው ቃለምልልስ ገልጻለች አንዲት እርጉዝ ሴትም እንዲሁ ልጇን ሲገድሉባት በልጇ ላይ ስትወድቅ በእርሷም ላይ በተፈጸመ ድብደባ የእርሷም ህይወት አደጋ ላይ ወድቋል። መንግስት ሶማሊያ ገብቶ የሌሎችን ጸጥታና ሰላም ለማስከበር ሲሞክር ፣ እኛን ዜጎቹን ግን ረስቶናል በማለት አክላለች ።
የአፋር ሰብአዊ መብቶች ተቆርቋሪ ድርጅት ሊ/መንበር የሆኑት አቶ ገአስ አህመድ የሟቾች ስም ዝርዝር እንደደረሳቸው ገልጸው፣ ህዝቡ መንገድ ለመዝጋት የተገደደው በማቾች በመበሳጨታቸው መሆኑን ተናግረዋል።
አቶ ገአስ የሁለቱን ድንበሮች ለማካለል በድሬዳዋ ስብሰባ እየተካሄ መሆኑን ገልጸዋል።
አቶ ገአስ የአፋር ህዝብ የራሱን መብት ለማስከበር እንዲህ አይነት እምቢተኝነት አስፈላጊ በመሆኑ የ አፋር ህዝብ ትግሉን እንዲቀጥል እንዲሁም ሁሉም ፓርቲዎችና አለማቀፍ ሰብአዊ መብት ድርጅቶች ከጎናቸው ሆነው ድርጊቱን እንዲያወግዙ ጠይቀዋል።
በጉዳዩ ዙሪያ የመንግስት ባለስልጣናትን አስተያየት ለማካተት ያደረግነው ሙከራ አልተሰካም።
ኢሳት ዜና :

No comments: