Monday, June 30, 2014

ምርጫ ይራዘምን ምን አመጣው? ማንን ይጠቅማል? በግርማ ሰይፉ ማሩ (የፓርላማ አባል)

June30/2012

የሰላማዊ ትግል አማራጮች ብዙ እንደሆኑ የሰላማዊ ትግል መስመር የመረጡ ዜጎች እንደሚረዱት እሙን ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ፅሁፍ ያቀረበው ጄን ሻርፕ ከአንሰታይን ኢንስቲትዩት አንዱ ሲሆን ይህም በህዳር 1998 ወደ አማርኛ ተመልሶዋል፤ እርገጠኛ ነኝ ይህ ፅሁፍ እንዲተረጎም ያደረጉት ሰዎች ድህረ ምረጫ 97 የገጠመንን የሰላማዊ ትግል ክፍተት የተረዱ ናቸው፡፡ አሁን ደግሞ  “የሰላማዊ ትግል 101” በሚል አንድ መፅኃፍ በሰላማዊ ትግል አቀንቃኙ ግርማ ሞገስ ለገበያ ቀርቦዋል፡፡ ይህ መፅሃፍ የቀረበበት ጊዜም ከምርጫ 2007 መቃረብ ጋር ሰናያይዘው ብዙ እንደምንማርበትና ስላማዊ ትግል ፈታኝ መሆኑን የሚያስረዳ ነው፡፡ የሰላማዊ ትግል ያልገባቸው እንደሚሉትም የፈሪዎች መሰመር አይደለም፡፡ በሁለቱም መፅሃፎች የቀረቡትን የሰላማዊ ትግል መንገዶች ኢህአዴግ “ነውጥ” ሊላቸው ቢችልም የሀገራችን ተጨባች ሁኔታና የገዢዎችን እና አባሎቻቸውን ስነልቦና በአገናዘበ መልኩ ሊተገበሩ የሚገባቸው እንደሆኑ ይታመናል፡፡ ከአምባገነናዊ አገዛዝ ወደ ዲሞክራሲ ለመሸጋገር ሰላማዊ አምቢተኝነት – ነውጥ አልባ አብዮት እንደሚያስፈልገን ማንም ያምናል፡፡

ለነገሩ አሁን ያሉት ገዢዎች ለዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ብለው ጠመንጃ ያነሱ መሆናቸውን ስናሰታውስ እና አሁን ደግሞ የትግል ሰልት መራጭ መሆን ሲያምራቸው ጉዳዩን ምፀት ያደርገዋል፡፡ ከእነርሱ ቀድመው የነበሩት ንጉሡም ሆነ ደርግ አንባገነኖች ነን አላሉም- ኢህአዴግም አንባገነን ነኝ ብሎ እንዲያምን አናስገድደውም፤ እኛ ግን አንባገነን መሆኑን እናምናለን፡፡ የትግል ስልት ምርጫም ቢሆን ከኢህአዴግ አናስፈቅድም፡፡ አሁን የመረጥነው “ሰላማዊ ትግል” ኢህአዴግን ስለሚያስደስት ሳይሆን ዘመኑን የዋጀ አዋጭ የትግል ስልት ነው ብለን ስላመንን ብቻ ነው፡፡

የንጉሡ እና የደርግ ጊዜን ከኢህአዴግ የሚለየው አሁን ዓለም ካለችበት ሁኔታ በተጨማሪ በስራ ላይ ያልዋለም ቢሆንም እጅግ ብዙ ዓለም አቀፋዊ ሰምምነቶችን ጨምሮ ብዙ ሰብዓዊ ዲሞክራሲያዊ መብቶች በግልፅ የሰፈሩበት ህገ መንግሰት መኖሩ ነው፡፡ በደርግ ጊዜ “ዲሞክራሲያዊ መብቶች እውቅና ያግኙ” የሚለው አንዱ ትግል የነበረ ሲሆን አሁን ደግሞ ትግሉ ተግባራዊ ይሁኑ ነው፡፡ የዲሞክራሲያዊ መብቶች ተግባራዊ ከሚሆኑበት መንገድ አንዱ ደግሞ በህዝብ ይሁንታ የሚመረጥ መንግሰት መመስረት ነው፡፡ ይህ ሂደት በሁሉም መስኩ ልምምድ ይጠይቃል፡፡ ከዚህ በተቃራኒው ግን ምርጫው ይቆይ የሚሉ ድምፆች እየተበራከቱ ነው፡፡ የዛሬው ፅሁፌም መነሻም ይህ እንዲሆን ፈለግሁ፡፡
ለዛሬ ትኩረቴን የሳቡት ከምርጫው በፊት ሀገራዊ እርቅ ይቅደም እና ከምርጫው በፊት በመስከረም አብዮት ይኑር የሚሉት እንዲሁም በአብዮት ለውጥ ቢመጣስ ማን ይረከባል የሚሉ ሃሳቦች ናቸው፡፡ የእነዚህ አሰተያየቶች ዋናው ገፊ ምክንያት አስተያየት አቅራቢዎች በገዢው ፓርቲ መማረራቸው ከማሳየት በተጨማሪ ለለውጥ ያላቸውን ፍላጎት ነው፡፡ ገልብጠን ስናየው ግን ከጥቅማቸው ይልቅ ጉዳታቸው የሚያመዝኑ አሰተያየቶች ናቸው ብዬ ነው የምወሰድው፡፡
ከምርጫ ሀገራዊ እርቅ ይቅደም አሰተያየት የተደመጠው ከዶክተር ያዕቆብ ሀይለማሪያም ከአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ጋራ ባደረጉት ቃለ ምልልስ ሲሆን ይህ መልዕክት ምርጫን እንደ የትግል ስልት ይልቁንም የምናገኛቸውን አንድ አንድ ውጤቶችን የምንቋጥርበት(Anchoring intermediate results) መሆኑንም የዘነጋ አስተያየት ይመሰለኛል፡፡
ዶክተር ያዕቆብ በፖለቲካ እንቅስቃሴዎች ውስጥ በንቃት እየተሳተፉ እንደሆነ ሁላችንም የምንረዳው ነው፡፡ በፓርቲ ፖለቲካ ውስጥ ግን በይፋ የሉበትም ስለዚህ ምርጫን በሚመለከት በግንባር ቀደም ተወዳዳሪነት አንጠብቃቸውም በግል ዕጩ ካልሆኑ በስተቀር፡፡ ስለዚህ አሁን የሰጡት አስተያየት በቀጥታ የሚጠቅመው ኢህአዴግን ሲሆን ጉዳቱ ደግም በምርጫ ፖለቲካ ዝግጅት ለሚያደርጉ ፓርቲዎች ላይ ነው፡፡  ይህ አስተያየት ደግሞ በቅርቡ አንድነት ከመኢህአድ ጋር ውህደት እንዲፈፅም ሲያደርጉት ከነበረው ጥረት ጋር የሚጣጣም አይደለም፡፡ ውህደቱ የሚያስፈልገው ከእርቅ በኋላ ለሚደረገው ምርጫ ነው ካለሉን በስተቀር፡፡ እንደ ዶክተር ያዕቆብ ኃይለማሪያም ያለ ተደማጭነት ላለው የአደባባይ ሰው እንዲህ ዓይነቱ አስተያየት ቀላል የማይባል ሰው ምርጫ ዋጋ የለውም ብሎ ከመራጭነት፣ ከታዛቢነት ከፍ ሲልም ከዕጩ ተወዳዳሪነት እራሱን እንዲያርቅ ያበረታታል፡፡ ይህ አሰተያየት ኢህአዴግን ካልሆነ ማንን ይጠቅማል?
ኢህአዴግ የዶክተር ያዕቆብን ምክር የሚሰማ ቢሆን ኖሮ አስተያየቱ ተቀባይነት ሊኖረው ይችል ነበር፡፡ ኢህአዴግ እንዲህ ዓይነት ስልጣኑን በጥያቄ ምልክት ውስጥ የሚያስገባ አሰተያየት እንዴት ሊቀበል እንደሚችል ማሰብ በራሱ ከባድ ነው፡፡ ዶክተር ያዕቆብ ይህን እርቅ ይቅደም አስተያየት ሲሰነዝሩ መቼም በዚህ የእርቅ ማዕድ ኢህአዴግ አዳዲስ አባላት አፍርቶ ዕጩ እንዲያፈራ  ሳይሆን ተቃዋሚ ፓርቲዎች ሊደግፉ የሚችሉ ሰዎች ከፍርሃታቸው ተላቀው ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንዲጠናከሩ ነው፡፡ ይህን ጉዳይ ኢህአዴግ የሚፈልገው ቢሆን ኖሮ የእርቅ ማዕድ ሳይሆን የሚያስፈልገው በ1997 እንደተደረገው እንከን የለሽ ምርጫ ማድረግ አለብን ብሎ ማወጅ ለዚህም ምቹ ሁኔታዎችን በኢህአዴግ በኩል ሳይሆን በመነግሰት መስመር እንዲከፈት ማድረግ ነው፡፡ የ1997 ምርጫ ሁሉም እንደሚያስታውሰው ከምርጫ በኋላ እንከን በእንከን ሆኖ ተጠናቆዋል፡፡ ያለብንን የሰላማዊ ትግል ሠራዊት ዝቅተኝነትና ዝግጁነት ተጠቅሞ ኢህአዴግ የንፁሃን ዜጎች ህይወት እዳ ወሰዶ አፍኖታል፡፡ በአሁኑ ሰዓት ሰለምርጫ ስናሰብ ግን ከምርጫ 97 የምንማረው የመኖሩን ያህል በምርጫ 97 መተከዝ አለብን ብዬ አላምንም፡፡ ምርጫ 97 ታሪካችን እንጂ ምርጫ ድሮ ቀረ እያልን የምናላዝንበት መሆን የለበትም፡፡
እንደ እኔ አምነት የዶክተር ያዕቆብን ሃሳብ ለመቀበል ኢህአድግ ከተዘጋጀ ኢህዴግ መንኩሶዋል ማለት ነው፡፡ እንደ ጳውሎስ ቀደም ሲል የሰራውን ግፍና መከራ ትቶ ወደ መልካምነትና ቅዱስነት ተሸጋግሯል ማለት ነው፡፡ አንባገነን መንግሰታት ባህሪ አይቀይሩም ማለት ባይሆንም ኢህአዴግ በዚህ ደረጃ እንዲያድግ እኛም ተገቢውን ግፊት አላደረግንም የሚል እምነት ስላለኝ ነው፡፡ እሰከ አሁን የሄድንበት መንገድ የተለመደ እና ኢህአዴግ ደግሞ እንዴት እንደይሰሩ ማድረግ እንዳለበት በደንብ ያውቃል፡፡ ሰለዚህ እኛም የተለየ መንገድ ማሰብ ይኖርብና፡፡
ምርጫው ይራዘም የሚል አሰተያየት የቀረበው ከዶክትር ያዕቆብ ብቻ ሳይሆን የፋክቱ ቋሚ አምደኛ ተመስገን ደሳለኝም አቅርቦታል፡፡ የተመስገን ምርጫው ይራዘም ጥያቄ ተግባራዊ የሚሆነው በመስከረም ቢሆን የመረጠው የህዳሴው አብዮት የሚመጣ ከሆነ ነው፡፡ የተመስገንን የህዳሴው አብዮት ማስፈፀሚያ ስትራቴጂ ጥሪ ተቀብለው በተለይ ደግሞ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰብ አብዮቱን የመሩት ከሆነ የአብዮቱ መሪዎች የምርጫውን ቀን የሚወስኑት ሲሆን፤ መቼም ይህ ከሆነ በእቅድ የተመራ አብዮት ተብሎ በታሪክ የሚመዘገብ ይሆናል፡፡ ይህ ገና ለገና በቢሆን የቀረበ የህዳሴ አብዮት ጥሪ ተግባራዊ ካልሆነ ከዚህ አሰተያየት የሚጠቀመው አሁንም ኢህአዴግ እንጂ ለምርጫ ዝግጅት የሚያደርጉ ፓርቲዎችን ሊሆኑ አይችሉም፡፡ መቼም ተመስገን ደሳለኝ በህዝብ ዘንድ ያለውን ተቀባይነት ሰናሰብ የዚህ አሰተያየት ጉዳት ከፍ ያለ ይሆናል ብዬ አምናለሁ፡፡
ንጉሡ ቢወርዱ ማን ይተካቸዋል፣ ደርግ ቢወድቅ ማን ይተካል ሲባል እንደነበረ ሁሉ ዛሬም ከኢህአዴግ በኋላ ማን ሀገር ሊመራ ይችላል የሚል መሞገቻ ይዞ በሸገር ሬዲዮ ዋዘኛ በሚል አዲስ የተጀመረ ፕሮግራም ላይ የተመስገን ደሳለኝን ህዳሴ አብዮት አሰተሳሰብ ሲሞግት ሰምተናል፡፡ ጋዜጠኛው የተመስገንን የህዳሴ አብዮቱን መሞገቱ እንደተጠበቀ ሆኖ ይህችን ትልቅ ሀገር ከኢህአዴግ ሌላ ማን ይመራታል? ብሎ አማረጭ የሌለን አድርጎ ማቅረብ ጤነኛ ሃሳብ አድርጌ ለመውሰድ እቸገራለሁ፡፡ ይህን ፕሮግራም የሰማሁት በዛሚ ወይም በፋና ቢሆን አይገርመኝም፤ በሸገር ሲሆን ግን ብዙ ዜጎችን ያሳሰታል ብዬ ሰለምሰጋ ነው፡፡ ሀገራችን ትልቅ ነች ሰንል በቆዳ ሰፋት ብቻ አይደለም ባላት ምርጥ የሰው ሀይል ጭምር ነው፡፡ እነዚህ ዜጎች ለምን ከኢህአዴግ ጎን አይታዩም? ለሚለው ጥያቄ መልሱ ኢህአዴግ የምርጦችና የምጡቃን ስብስብ ቤት ስላልሆነ ነው፡፡ ኢትዮጵያን ሊመሩ የሚችሉትን ሰዎች በኢህአዴግ አፈና ምክንያት በፊት ለፊት ከተቃዋሚ ጋር ወይም ከኢህአዴግ ጋር ስላላየናቸው የሉም ማለት ግን ትልቅ ሰህተት ነው፡፡
በእኔ እምነት በዚህ ጊዜ የሚያስፈልገው ለምርጭ ዝግጅት ህዝቡ እንዲነቃቃ ማድረግ ለታዛቢዎች አሰፈላጊውን የሞራል ትጥቅ ማስጨበጥ ዕጩዎች በግል ከሚያደርጉት ዝግጅት በተጨማሪ የሚጎድላቸውን በሞራልም በፋይናንስም ድጋፍ ማድረግ ነው፡፡ በተለይ ዶክተር ያዕቆብ እና ተመስገን በኢትዮጵያችን ለውጥ እንዲመጣ ያላቸውን ጉጉት ሰለምረዳ፤ የሚፈልጉት ለውጥ ግን ደረጃ በደረጃም ቢሆንም ሊመጣ እንዲችል  ተጨባጭ ድጋፍ ሊያደርጉ ይችላሉ ብዬ አምናለሁ፡፡ በዋነኝነት እነዚህ የአደባባይ ሰዎች ምርጫ ይራዘም ከሚለው አቅጣጫ ወጥተው በቁርጠኝነት ምርጫውን በግላቸው መደገፍ እና አድናቂዎቻቸውም በምርጫ እንዲሳተፉ ግፊት ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ያገባናል ከሚሉ የአደባባይ ሰዎች በአሁኑ ጊዜ የሚጠበቀው፤
  • ደጋፊዎቻቸው እና አድናቂቆቻቸው በምርጫው ለመሳተፍ በመራጭነት፣ በታዛቢነት ብሎ በዕጩነት እንዲነሳሱ ማበረታታ እና
  • ደጋፊዎቻ   የሚችሉትን ድጋፍ ለማድረግ እንዲችሉ ለማበረታት ደግሞ እራሳቸውን በአራሃያነት ማቅረብ
ነው፡፡ ይህን ካደረግን በሁለት ሺ ሰባት በሚደረግ ምርጫ ቀላል የማይባሉ የምርጫ ክልሎችን ነፃ ማውጣት እንዳለብን ማመን የግድ ይላል፡፡ አማራጭ የለም ብለው ወደኋላ የሚሉትን ለመሳብ ፓርቲዎች የሚቻለውን ሁሉ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡
ባለፈው የምርጫ ፖለቲካን አስመልክቶ የፃፍኩትን አሰተያየት አንብቦ አንድ ወዳጄ አማራጭ ሳይኖር ለምርጫ መመዝገብ ምን ዋጋ አለው ብሎ ጠየቀኝ፡፡ የእኔም መልስ “በእኔ በኩል ኣማራጭ የለም በሚለው አልሰማማም፡፡ በቂ አማራጭ አለመኖሩን ግን መካድ አይቻለም ነገር ግን የምርጫ ካርድ የወሰደ ሰው አማራጭ የለም ብሎ ካመነ የምርጫ ካርዱን ይዞ ያለመምረጥ መብት አለው፡፡” የሚል ነበር፡፡ ይህን ማድረግ ትልቅ የፖለቲካ መልዕክት ያስተላልፋል፤ በገዢው ፓርቲ አፈና ምክንያት አማራጭ አጥተናል ብለን ካመንን የምርጫ ካርዳችን ላይ በምርጫ ያለመሳተፋችንን የሚገልፅ ምልክት አድርገን ምርጫ ቦርድ ጊቢ ወይም ፓርላማ ጊቢ ውስጥ በመወርወር ተቃውሞ ብናደርግ ተቃውሟችን በመረጃ የተደገፈ ለማድረግ ይረዳናል፡፡ ባለፈው ለማሳየት እንደሞከርኩት በምርጫ የተሳተፈ ህዝብ ድምፃችን ይከበር ብሎ መንግሰትን ሊያስገድድ ይችላል፡፡ ያልመረጠ ግን ምን ድምፅ አለው? ምንስ ሞራል ይኖረዋል ድምፃችን ይከበር ለማለት? ድምፃችን ይከበር ለማለት በምርጫ መሳተፍ የግድ ይላል፡፡ ሁላችንም የምርጫውን ግንባር ለመደገፍ እንትጋ ከአደራ ጋር የማስተላልፈው መልእክት ነው፡፡
ቸር ይግጠመን

ጊዜ የማይሠጥ ሀገራዊ ጥሪ አለብን!

June30/2014
እስከመቼ ባለንበት እንረግጣለን?
eskemechie


ራሱን “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” ብሎ የሰየመው ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት (ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት)፤ ሀገራችንን ዕለት ከዕለት ወደ ባሰ አዘቅት እንድትገባ እየጎተታት ነው። የፖለቲካ ፍልስፍናውና የአስተዳደር መመሪያው የሀገራችንን ሕልውና በንጥልጥል ላይ እንዲቀመጥ ሌት ከቀን እየጣረ ነው። በአንፃሩ ደግሞ ለኢትዮጵያዊያንና ለኢትዮጵያ በመቆም፤ በተለያዩ ድርጅቶች ከፍተኛውን መስዋዕትነት በመክፈል፤ ከዚህ ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት ጋር እየተዋደቁ ያሉ ታጋዮች አሉ። ይህ በዚህ ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥትና በኢትዮጵያ ሕዝብ መካከል እየተደረገ ያለው ግብግብ፤ ለረጅም ዘመን እንዳለ ሆኖ፤ ፀረ-ኢትዮጵያዊው መንግሥት የፈለገውን እያደረገ ያለበትና፤ በታጋዩ ወገን ያለው ክፍል ደግሞ ላለፉት ፳ ፫ ዓመታት ባለበት የሚረግጥበት ሁኔታ አልተለወጠም። ከጊዜ ወደ ጊዜ ይህ ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት የሚጠናወተው ክፍል እየበዛ፤ በአሁኑ ሰዓት ሀገሪቱ ይኼው ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት ሊቆጣጠረው በማይችልበት ቀውስ ውስጥ ልትገባ አዝምማለች። ከዚህ እንድታቀና ሁላችን እንፈልጋለን። ይኼን ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት ማስወገድ ሁላችን እንፈልጋለን። እስካሁን የደከምንባቸው መንገዶች ውጤታቸው አመርቂ ስላልሆነ፤ አዲስ መንገድ መቀየስ አለብን። የሀገራችን ችግርና መከራ፣ በምኞት አይቀረፍም። ይህ በትግላችን የሚከናወን ነው። ይኼን ለማሳካት እንዴት እንደምንበቃ ምርጫ የሌለው አንድ መንገድ አለን። ሁላችን እናውቀዋለን፤ ኢትዮጵያዊያን በአንድነት ተነስተው ሀገራችን እያሉ እንደሆነ ሁሉ፤ እኛም በያለንበት ለኢትዮጵያዊያን ከጎናቸው ቆመን፤ ሀገራችንን አስቀድመን፣ በአንድ ተሰልፈን መነሳት ነው። የዚህ መንገድ ጠቃሚነቱ፤ ፀረ-ኢትዮጵያዊውን መንግሥት ማስወገዱ ላይ ብቻ ሳይሆን፤ ቀጥሎ ለምትመሠረተው ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ አስተማማኝ መሆኑ ነው። በዚህ ሂደት ሁሉም ድርጅቶች ባለቤቶች ናቸው። በዚህ ሂደት እያንዳንዷ ኢትዮጵያዊት ባለቤት ናት። በዚህ ሂደት እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ባለቤት ነው። ትኩረቱ፤ በሚሰቃየው ወገናችን፣ የጋራችን በሆነችው ሀገራችን፣ እና በጠላታችን ፀረ-ኢትዮጵያዊው መንግሥት ላይ ነው። ይህ የጋራችን ፈተና ነው። ማናችንም ከዚህ ውጭ አይደለንም። ከሀገር መለስ ብዙ የምንለያይባቸው ጉዳዮች አሉ። ነገር ግን ክብደታቸው ከሀገር ነፃነት ጋር ሲነፃፀር፤ ሁለተኛ ደረጃን የያዘ ስለሆነ፤ ቅድሚያን ለሀገር እንድርግ። በመካከላችን ያለው ልዩነት የዴሞክራሲያዊ አሠራርን የሚጠይቅና በዚያው መንገድ የሚፈታ ነው። የዚህ ጽሑፍ ዓላማ፤ ከተለያየ ቦታና የተለያየ ተመክሮ ያለን ግለሰብ ኢትዮጵያዊያን፤ ከድርጅት አባል መሆን አለመሆን ይልቅ፤ የወገናችንን ብሶት ማስወገድና የሀገራችንን ሕልውና ማስጠበቅን በማስቀደም፤ በአንድነት በመቆም፤ የትግሉን ሂደትና መደረግ ያለበትን ተረድተን፤ በሀገራዊ ጥሪው ሁላችንም ኢትዮጵያዊያን እንድንሰባሰብ ነው። ይህ ብዙዎቻችንን ያሰባስባል። ይህ በአንድነት ለተግባር ያሰልፈናል። ይህ፤ የምናደርገው ጥረት ለሀገራችን መሆኑን ያረጋግጣል። ይህ በፍጥነትና በተጠናከረ ጉልበት ለወገናችን እንድንደርስ ያደርገናል።
ውድ አንባቢ፤
በሀገራችን ላለው የፖለቲካ ውጥንቅጥ፤ ላንዴና ለመቼውም መፍትሔ ለማስገኘት የመጨረሻው ደወል ተደውሏል። ሀገራችን ስላለችበት የፖለቲካ ሀቅ እርስዎም ሆነ እኔ ነጋሪ አያስፈልገንም። ኢትዮጵያዊያንን ለረጅም ዘመን አቆራኝቶ የያዘንን የኢትዮጵያዊነት ትስስር ለመበጣጠስ የተነሳን ድርጅት፤ በምንም መመዘኛ ብንለካው ፀረ-ኢትዮጵያዊ ከመሆኑ ሌላ፤ ምንም ገላጭ ቃል አይገኝለትም። በመካከላችን ያለውን አንድነት ሰብሮ፤ እርስ በርሳችን በጥርጣሬ እንድንተያይ ያደረገን፤ ይኼው ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት ነው። ሀገራችንን እየገዛ ያለው ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት፤ ሀገራችንን እየወሰዳት ያለበት አዘቅት፤ አደገኛና መመለሻ የሌለው ነው። ዴሞክራሲያዊነት፣ ፍትኅን አክባሪነት፣ ለሕዝብ ተቆርቋሪነት፣ ለድሃ ቋሚነት፣ ሀገር ወዳድነትና ለሕግ ተገዥነትን የወደደ፤ የትውልድ ቆጠራን ከውሉ አያስገባም። እኒህ፤ ተግባራዊ ለማድረግ ፍላጎት ባላቸው ግለሰብ ኢትዮጵያዊያን እጅ ያሉ ጥበቦች ናቸው። ከተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች የተገኘን ወገኖች፤ በምን መንገድ ተለያይተን ልንተያይ ነው? ኢትዮጵያዊ ብለን በእኩልነት ካልተቀባበልን፤ መበታተኑ ማንን ነው የሚጠቅመው? የየተንገንጣዩ ልሂቃን ሥልጣን ይዘው የገነጣጠሉንን ወገናቸውን ለመግዛትና ኪሳቸውን ለማሳበጥ ከመሯሯጥ ውጪ፤ ለኛ ለተራ ግለሰቦች ምን ሊያስገኙልን ይችላሉ? ዴሞክራሲ ለየብቻ ስንሆን ብቻ ነው የሚሠራው ያለው ማነው? ትናንት በኤርትራ የደረሰውን ለምን እንረሳለን? አሁንም የተያዘው ጉዞ፤ ሀገሪቱ አንድነት አጥታ መገዛት የማትችልበት ሁኔታ እንዲፈጠርና፤ ስግብግብ የሥልጣን ጥመኞች ተጠቃሚ የሚሆኑበትን ሁኔታ ለመፍጠር ነው። በሀገራችን ያለውን የጨቋኝና የተጨቋኝ ጉዳይ “የብሔር ጥያቄ ዋነኛው የሀገራችን ቅራኔ ነው” ብሎ የተነሳው ይሄ ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት፤ ይህ ቅኝቱ አሁን ሀገራችን እንደ አንድ ሀገር እንዳትቆምና ሕዝቧም እንደ ኢትዮጵያዊነቱ ሕልውናውን እንዲያጣ ቀን በመቁጠር ላይ ነው። ለሥልጣን መወጣጫና በሥልጣኑ መስንበቻ የቀመረው ጉዳይ፤ አድሮ በራሱ ላይ ተጠምጥሞ መታነቂያው ሆኗል። በየክልሉ ያሉ የተለያዩ ኢትዮጵያዊያን እንዲፈጠሩ ያሰላውና የየክልሉ ነዋሪዎች፤ ሌሎችን “መጤዎች” በማለት እንዲያባርሩ ያፋፋመው ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት፤ ኢትዮጵያን ወደ ማጥፋቱ አምርቷል። በአንፃሩ ግን፤ ኢትዮጵያዊያን ከሰሜን እስከ ደቡብ፤ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ ሀገራችን አንድ ናት ብሎ ተነስተዋል።
በኢትዮጵያ ውስጥ የሚካሄደው የፖለቲካ ጉዳይ፤ ከጀርባው ኢትዮጵያን ለማጥፋት በደንብ የተቀመረ እርምጃና አራማጅ አለው። ይህ በፀረ-ኢትዮጵያዊው መንግሥት የሚተገበረው ጥፋት፤ ከጀርባው የውጭ ሀገር እጅ ያለበት ለመሆኑ ማናችንም ጥርጥር ሊኖረን አይችልም። በፖለቲካ ምንም ነገር ለብቻው የሚሄድ የለም። በምንም መንገድ የውጭ ሀገር መንግሥታት ለኢትዮጵያዊያን ጥቅምና ለዴሞክራሲ ይቆማሉ ብለን ማሰብ የለብንም። እነሱ የቆሙት ለሀገራቸው ጥቅምና ከኛ የሚያገኙትን ጥቅም ለማብዛት ነው። ከአሜሪካ አንስቶ እስከ ኤርትራ ድረስ፤ ለዴሞክራሲ ወይንም ጠንካራ ኢትዮጵያን ለመመሥረት የቆመ የለም። ባለቤቶችም ሆን ባለዕዳዎቹ፤ ታጋዮችም ሆን አሳልፎ ሠጪዎቹ፤ እኛው ነን። የኢትዮጵያን መንግሥታዊ ሥልጣን በውጭ መንግሥታት ፈቃድና ቡራኬ ለመቀበል የተዘጋጁ የድርጅቶች መሪዎች፤ ምን ያህል ሀገር ወዳድ ናቸው? የውጪ ሀገሮች አደግዳጊ የሆነ ቡድን በሀገራችን የሥልጣን ወንበር ከተቀመጠ፤ አሁንም ፖለቲካችን እንቧለሌ ዙሪያ ነው የሚሆነው፤ ወጣቶቻችንን ለጦርነት፣ የሀገራችንን ሀብት ለጥቂት ግለሰቦች፣ ድህነትና ረሃብን ለወገናችን ማውረስ ነው። የአክራሪዎች (ቴረሪስት) ተግባር የኢትዮጵያዊያን የፖለቲካ ችግር አይደለም። የአሜሪካ ችግር ነው። የኛ ችግር ፀረ ኢትዮጵያ መንግሥት በላያችን ላይ መጫኑ ነው።
የምንታገለው ለሚከተሉት የትግል ዕሴቶቻችን ነው፤
ሀ) የኢትዮጵያ ሕዝብ ሉዓላዊነቱ ተከብሮ፤ ሕዝቡ የኢትዮጵያ መንግሥት ባለቤትነቱ እንዲረጋገጥ፤
ለ) ሀገራችን ኢትዮጵያ አንድነቷ ተጠብቆ፤ ለሙ መሬቷና ዳር ድንበሯ ለኢትዮጵያዊያን እንዲሆን፤
ሐ) በሀገራችን ኢትዮጵያ፤ በሕዝቡ የጸደቀ ሕግ-መንግሥት ኖሮ የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን፤
መ) የእያንዳንዷ ኢትዮጵያዊትና የእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ የግለሰብ መብት በሕግ እንዲደነገግና በተግባር እንዲገለጥ፤
እነዚህ ናቸው የምንታገልላቸው። እኒህ ደግሞ በማንኛውም ታጋይ ደርጅት ዘንድ ተቀባይነት አላቸው። በተግባር ላይ እንዲውሉ ደግሞ እያንዳንዱ ግለሰብ ኢትዮጵያዊና ኢትዮጵያዊ ድርጅት የኔ ብሎ መነሳት አለበት። ሀገራችንን ከዚህ ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት ለማስለቀቅ በሚደረገው ትግል፤ በዚህ መለስተኛ በሆነው ሀገራዊ ጥሪ ለመሰባሰብ፤ የተለያዩ ድርጅቶች መኖራቸው ወይም አዳዲስ መፈጠራቸው አስፈላጊ አይደለም። ይልቁንስ የሚያስፈልገው ሁላችንም ወደ አንድ የምንመጣበት መንገድ ነው። አሁን በታጋዮች ወገን ያለው ሀቅ አያኮራም። ከአንደኛው የፖለቲካ ዝማሜ እስከሌላው ጫፍ ድረስ ተዘርግቶ ያለው የፖለቲካ ድርጅቶች ስምሪት፤ የፖለቲካ ማኅደሩን ከማጨናነቅ ያለፈ፤ አመርቂ ውጤት አላሳየም። እናም ሊቀጥል አይገባውም። ከዚህ መውጣት አለብን። ለሥልጣን በመሰለፍ ላይ እግራቸውን የተከሉ ሁሉ፤ የኢትዮጵያን ዘለቄታ ጥቅም ስላላዘሉ፤ ውጤታማ ቢሆኑም፤ ለኢትዮጵያዊያ መልሶ እምቦጭ ነው።
ነገ እንድትመጣ የምንፈልገዋን ኢትዮጵያ፤ በአንድነት ልናረጋግጥበት የምንችለው በዚህ መንገድ ነው። ከሺ ዘጠኝ መቶ ሃምሳ ሶስቱ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራና ከሺ ዘጠኝ መቶ ስድሳዎቹ የተማሪዎች እንቅስቃሴ ጀምሮ እስካሁን ድረስ ያለው ትግል፤ ይኼንኑ የዴሞክራሲ ጥያቄ ነው አንግቦ የዘመተው። ሕዝባዊ ያልሆነ ሥልጣን ያባልጋል። በቀላሉ አይለቀቅም። መንገዱን ሁሉ በማጥበብ ዘለቄታን ይሻል። እናም አምባገነን ነው። መንግሥቱ ኃይለማርያምን ማጥናቱ የበለጠ ያረጋግጣል። ኢሳያስ አፈወርቂን ያየ ሌላ አይሻም። መለስ ዜናዊን ያየ ሌላ መረጃ አይጠይቅም። የሀገራችን ምጣኔ ሀብት ሥምሪት ዘግናኝ ነው። ጥቂቶች ከመጠን በላይ ባለሀብቶችና፤ እጅግ በጣም ብዙዎች መንገድ አዳሪዎች ያሉበት ሀቅ ነው። ሥራ ፈላጊው ቁጥሩ እየጨመረ ነው።
ኢትዮጵያ ውስጥ የሚታገሉ ወገኖቻችን ስንመለከት፤ በየጊዜው በሚለዋወጥ ሕግ እጅና እግራቸው ተፈጥርቆ፤ ይኼን ካደረጋችሁ እንዲህ ትደረጋላችሁ እየተባሉ፤ ከፍተኛውን መስዋዕትነት በመክፈል ይገኛሉ። ሆኖም ግን መሠሪ በሆነው የገዥው ቡድን ተንኮልና የስለላ ድር ተሸብበው እንቅስቃሴያቸው ውስን ሆኗል። ደስ የሚል የትብብር ጅማሬ እየታዬ ነው። ይበርታ እንበል። ሆኖም ግን፤ አሁንም አንድ የሆነ ማዕከል ኖሮ፤ ሁሉም በአንድነት የሚሰለፉበት መንገድ ካልተፈጠረ፤ ከሚገኘው ድል ይልቅ መስዋዕትነቱ እየበለጠ፤ የታጋዩን ቁጥር ለጊዜውም ቢሆን እንዳያሳሳው ያሰጋል። እናም የአንድነት ጥሪው አሁንም መጠንከር አለበት።
በውጭ ሀገር ያለን ኢትዮጵያዊያን ለረጅም ጊዜ በያለንበት ስንታገል ብዙ ዓመታት አሳልፈናል። በአንድነት ሕብረትን ፈጥረን፤ አንድ ሀገር፤ አንድ ራዕይ፤ አንድ ትግል ብለን ካልተነሳን፤ አሁንም ዓመታትን ከመቁጠር ሌላ የረባ ልንሠራ አንችልም። ትግል ሥነ ሥርዓት አለው። ትግል መስዋዕትነት አለው። ትግል ታታሪነትን ይጠይቃል። ትግል ቀጣይነትን ይጠይቃል። ሲያመቸንና ደስ ሲለን የምንቀላቀለው፤ ደስ ያላለን ጊዜ ደግሞ ንቀን የምንተወው ከሆነ፤ የትም አይደርስም። ቆራጥነትን፣ ታታሪነትን፣ አልቸነፍም ባይነትን ይዘን ነው ወደፊት መሄድ የሚገባን። ለዚህ ደግሞ አሰባሳቢና አነሳሽ ራዕይ ያስፈልጋል። ፀረ ኢትዮጵያ መንግሥት በሀገራችን ቆሞ፣ ሕዝቡ ከዕለት ወደ ዕለት ኑሮው እያሽቆለቆለ፣ ጥቂቶች ሀብታቸውን ሽቅብ አጉነው ባለንበት ሀቅ፤ ሀገርን ከዚህ ፀረ ኢትዮጵያ መንግሥት ነፃ ለማውጣት ከታጋዩ ሕዝብ ጎን አብረን መሰለፉ ይገባናል።
አሁን ምን እየሠራን ነው? እያንዳንዳችን መጠየቅ ያለብን ራሳችንን ነው። ዛሬ፣ ትናንት፣ የዛሬ ሳምንት፣ ያለፈው ወር፣ ባለፈው ዓመት፣ ባለፈው አምስት ዓመት ምን ሠራን ብለን ራሳችንን እንጠይቅ? ከዚህ ተነስተን ሌሎች የሚያደርጉትን መገመትና መገምገም እንችላለን። ታዲያ ወገናችንን ማፍቀራችንን እና ሀገራችንን መውደዳችን የት ላይ ነው? እኛስ ካልታገልን ማን ታግሎ ነፃ እንዲያወጣን እንጠብቃለን? በውጭ ያለን ኢትዮጵያዊያን የተለያዩ መድረኮች አሉን። ሃሳቦቻችንን ልንለዋወጥባቸው የሚያስችሉን፤ ድረገፆች፤ የመወያያ ክፍሎች፣ ሬዲዮ ጣቢያዎች፣ ፌስቡክ፣ ትዊተር፣ እና ሌሎችም አሉን። እኒህን በመጠቀም አንድነትን እያራመድን፤ ትግሉን ማጠናከር እንችላለን። ይህ ፍላጎቴ አይሠራም ወይንም ትክክል አይደለም የምትሉ ካላችሁ፤ የናንተን የሚሠራ አቅርቡና ልከተላችሁ። ዋናው ነገር ተግባራዊ ሆነን መገኘታችን ነው።
አዲሲቷን ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ ለማቋቋም ያለው መንገድ፤ በአንድነት ሁላችን ተሰባስበን የምንመሠርተውና የምንቆምለት ድርጅት እየመራን፤ ይኼን ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት ከሥሩ ስንመነግለው ነው። ጊዜ ባለፈው የአፄው ዘመነ መንግሥት የታጋዮች ጥያቄ፤ የዴሞክራሲ ጥያቄ ነበር። ለዚህም ከፍተኛውን መስዋዕትነት በመክፈል ትግሉን ወደፊት ገፍተውታል። በሰው በላው የመንግሥቱ ኃይለማርያም አምባገነን መንግሥት ዘመን የታጋዮች ጥያቄ የዴሞክራሲ ጥያቄ ነበር። ያንን አረመኔ መንግሥት በማፋጠጥ፤ ከፍተኛ መስዋዕትነትን ከትንሹ እስከ ትልቁ ከፍለው ትግሉን ወደፊት ገፍተውታል። በፋሽስቱ ጣሊያን ወራሪ መንግሥት የታጋዮች ጥያቄ የሀገራችን ነፃነት ነበር። ለሀገር ነፃነት በአንድነት ሁሉም ሀገሬ ብሎ ተነስቶ፤ ለጦርነት ተጉዘው ያልተመለሱ አርበኞቻችን ሀገራችንን ለኛ አትርፈውልናል። በሀገራችን አሁን ያለው መንግሥት የዴሞክራሲ ጥያቄዎችን የምናቀርብለውት መንግሥት አይደለም። ሕግን የሚያከብር መንግሥት አይደለም። እኩልነትን የሚቀበል መንግሥት አይደለም። የሕዝብን ድምጽ የሚያከብር መንግሥት አይደለም። በኢትዮጵያዊነት እየገዛ አይደለም። ፀረ ኢትዮጵያ መንግሥት ነው። እናም እንደፋሽስቱ የምንታገለው መንግሥት ነው። ለፀረ ኢትዮጵያ መንግሥት ደግሞ መልሱ በአንድነት ሀገሬ ብሎ መነሳት ነው። በዚህ ሂደት፤ ብዙ የተለያዩ አጀንዳዎች ሊነሱ ይችላሉ። በቅድሚያ ግን ሁሉም ኢትዮጵያዊያን እና ኢትዮጵያዊ ድርጅቶች ወደ አንድ መምጣት አለባቸው። ጠላታችንን እንዴት እንደምናፈልሰው አንድነት ሊኖረን ይገባል። ከጠላታችን መፍለስ በኋላ መከተል ስላለበት የመንግሥት አመሠራረትና አካሂያድ አንድነት ሊኖረን ይገባል። ይህ ደግሞ ከፍ ባለ ትክክለኛ ተራማጅ ድርጅት መዋቀርና መመራትን ግድ ይላል። ሁሉም ከሀገር መለስ ያሉት ጉዳዮች ከሀገር መዳን በኋላ የሚነሱ ሁለተኛ ጉዳዮች ናቸው። በዚህ ጉዳይ ላይ ከማንም ጋር ለመወያየትና አብሮ ለመነሳት ፈቃደኛ ነኝ። አብሬህ አለሁ በማለት እንድንወያይ የምትፈልጉ በ(eske.meche@yahoo.com ) ጻፉልኝ።

እያበበ የመጣዉ ህዝባዊ ትግል

June 29/2014
ኢትዮጵያ ህዝብ ለብዙ ዘመናት እንወድሀለን በሚሉት ነገስታት ተረግጧል፤ ህብረተሰብዓዊነት አመጣንልህ ባሉት ወታደራዊ አምባገነኖችም ለ17 አመት እጅና እግሩን ታስሮ ተገዝቷል። እነዚህ ሁለት ለህዝብ ደንታ የሌላቸዉ መንግስታት ተራ በተራ በህዝብ ትግል ተንኮታኩተዉ የታሪክ ቅርጫት ዉስጥ ገብተዋል፤ ሆኖም ሁለቱንም መንግስታት በመራራ ትግል አሸንፎ የጣለዉ የኢትዮጵያ ህዝብ የትግሉን ዉጤት ማስጠበቅ ባለመቻሉ ይህ ኃያልና የረጂም ዘመን ታሪክ ባለቤት የሆነ ህዝብ ዛሬም ነፃ አወጣንህ በሚሉት ዘረኛ አምባገነኖች እየተረገጠ ነዉ። አዎ! የኢትዮጵያ ህዝብ ዛሬም እየተረገጠ ነዉ። ዛሬም አየታሰረ ነዉ። ዛሬም እየተገደለ ነዉ። ዛሬም ይህንን ሁሉ በደል የሚያደርሱበትን የአንድ ወንዝና የአንድ መንደር ምርት የሆኑ ዘረኛ አምባገነን ገዢዎችን ከጭንቅላቱ ላይ ለማዉረድ እየታገለ ነዉ። በእርግጥም የኢትዮጵያ ህዝብ ከምን ግዜም በተለየ መልኩ የወያኔን ዘረኛ አገዛዝ አምርሮ እየታገለ ነዉ፤ በተለይ በዚህ በያዝነዉ አመት ወያኔንና ሃያ ሁለት አመት ሙሉ የገነባዉን ዘረኛ ስርዐቱን ለመደምሰስና ኢትዮጵያ ዉስጥ በፍትህና በእኩልነት ላይ የተመሰረተ ስርዐት ለመገንባት የሚደረገዉ የሞት የሽረት ትግል ተጠናክሮ ቀጥሏል።
ወያኔ እግሩ አዲስ አበባን ከረገጠበት ግዜ ጀምሮ የጭቆና ተቋሞቹን በየቦታዉ ተክሎና ተደላድሎ ህዝብን እንዳሰኘዉ መርገጥ እስከጀመረበት ግዜ ድረስ አንዴ ሰዉ በላዉን የደርግ ስርዐት አስወገድኩላችሁ እያለ ሌላ ግዜ ደግሞ ፌዴራል ስርዐት መስርቼ ብሄር ብሄረሰቦችን ነፃ አወጣሁ እያለ ለተወስነ ግዜም ቢሆን የኢትዮጵያን ህዝብ ቀልብ መሳብ ችሎ ነበር። ሆኖም ብዙም ሳይቆይ ያ በፌዴራሊዝም፤ በዲሞክራሲና በይስሙላ ምርጫ የተሸፈነዉ የወያኔ አስቀያሚ ገበና ይፋ እየሆነ መጥቶ ወያኔ አርግጫዉንና ግድያዉን የኢትዮጵያ ህዝብ ደግሞ ትግሉን፤ እስሩንና ስደቱን ተያያዙት።
የወያኔን መሰሪ አላማ ገና ከጧቱ የተረዱ ኢትዮጵያዉያን ባለፉት ሃያ ሦስት አመታት ይህንን መሰሪ አገዛዝ በተደራጀ፤ ባልተደራጀ፤ በተባበረና በተበታተነ መልኩ ሲታገሉ ቆይተዋል። ሆኖም የአገራችንን የፖለቲካና የኤኮኖሚ መዋቅሮች ሙሉ ለሙሉ ከሚቆጣጠረዉ ወያኔ ጋር በቁጥር፤ በአይነትና በይዘት የሚመጥን ትግል ማካሄድ ባለመቻላቸዉና እንዲሁም ብትራቸዉን ወያኔ ላይ ብቻ ከመሰንዘር ይልቅ እርስ በርስ ስለሚላተሙበት ምንም አይነት ህዝባዊ ድጋፍ በሌለዉ ወያኔ ላይ የትግል የበላይነት ማግኘት አልቻሉም፡፡ ወያኔም እኛዉ ዉስጥ ከመካከላችን የበቀለ እሾክ በመሆኑና ደካማ ጎናችንን በሚገባ ስለሚያዉቀዉ በዚሁ ደካማ ጎናችን እየገባና እርስ በርስ እያባላን የስልጣን ዘመኑን እስከዛሬ ማራዘም ችሏል።
ወያኔ የአንድን አካባቢ ህዝብ ከሌላዉ አካባቢ ህዝብ፤ አንዱን የህብረተሰብ ክፍል ከሌላ የህብረተሰብ ክፍል ጋር በሆነዉ ባልሆነዉ ምክንያት እየፈጠረ ማጋጨቱን አሁንም አላቆመም፤ እንዲያዉም ይበልላችሁ ብሎ በስፋት እንደቀጠለበት ነዉ። ዘንድሮ ግን ህዝብ፤ የተቃዋሚ ኃይሎችና በወያኔ ተንኮል ተታልለዉ የእርስ በርስ ሽኩቻ ዉስጥ ገብተዉ የነበሩ የህዝብ ወገኖች ሁሉ የወያኔን የከፋፍለህ ግዛዉ ደባና ሴራ በሚገባ ያወቁ ይመስላል። ለምሳሌ በቅርቡ አምቦና በተለያዩ የኦሮሚያ ክልል ዩኒቨርሲቲዎች ዉስጥ ከፍተኛ ፀረ ወያኔ የተቃዉሞ ሰልፍ በተካሄደ ግዜ የወያኔ ካድሬዎች የኦሮሞ ህዝብ ቁጣና መነሳሳት አቅጣጫዉን ቀይሮ በትግል አጋሩ በአማራ ህዝብ ላይ እንዲያተኩር ለማድረግ ያልፈነቀሉት ዲንጋይ አልነበረም። ሆኖም ወያኔን ከስልጣን ለማባረርና የአገራቸንን ወደፊት በህዝብ እጅ ላይ ለማስቀመጥ ቁልፉ መተባባርና አንድ ላይ መቆም መሆኑን የተረዳዉ የኦሮሞና የአማራ ህዝብ ቁጣ ይበልጥ በወያኔ ላይ ነደደ እንጂ አንደቀድሞዉ ለወያኔ የተንኮል ሴራ እጁን አልሰጠም።
ወየኔን በተለያዩ የትግል ስልቶች የሚፋለሙ የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ኃይሎች በፀረ ወያኔ አቋማቸዉና በአላማቸዉ የኢትዮጵያ ህዝብ ሙሉ ድጋፍ ከጎናቸዉ እንዳለ እንኳን እኛ ወያኔም በሚገባ ያዉቃል። ህዝብን የመሰለ እንደ ዉኃ ማጥለቅለቅ የሚችል ኃይል ከጎናቸዉ ያሰለፉ ድርጅቶች ደግሞ ወያኔን የመሰለ ምንም ህዝባዊ መሰረት የሌለዉን ኃይል ቀርቶ ፊታቸዉ ላይ የቆመን ምንም አይነት ኃይል ከማሸነፍ የሚገታቸዉ ምንም ነገር የለም።
ሆኖም ዉኃም ቢሆን ምን ያክል ኃይለኛ መሆኑ የሚታወቀዉ ተገድቦ ወደ ተፈለገበት አቅጣጫ እንዲሄድ ሲደረግ ነዉና የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ኃይሎችም ከጎናቸዉ የቆመዉን ህዝብ አስተባብረዉ አገራችንን ወደ ድል መምራት የሚችሉት መጀመሪያ እነሱ ተባብረዉ ህዝብን በአንድ አላማና በአንድ አመራር ስር ማሰለፍ ሲችሉ ብቻ ነዉ። ዛሬ በሁሉም አካባቢዎች ባይሆንም አገር ዉስጥና ካገር ዉጭ በተለያዩ አካባቢዎቸ ይቅናችሁ በሚያሰኝ መልኩ ጎልተዉ የሚታዩ ብዙ የትብብርና የትግል ቅንጅት ጅምሮች አሉ። በገበሬዉና በሰራተኛዉ፤በወጣቱና በወታደሩ በተለይ ደግሞ በተለያዩ ብሄረሰቦችና በተለያዪ የፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ከመለያየት ይልቅ የመቀራረብ፤ ከመወቃቀስ ይልቅ የመወያየት ከመጠላለፍ ይልቅ የመተቃቀፍ አዝማሚያዎች በብዛት እየታዩ ነዉ።
ከ1997ቱ ምርጫ በኋላ ጀምሮ እስከቅርብ ግዜ ድረስ የተቃዋሚዉን ጎራ በተለይም አገር ዉስጥና ከአገር ዉጭ የሚገኙትን የኢትዮጵያ የፖለቲካ ልህቃን ለሁለት ከፍሎ ሲያጨቃጭቅ የከረመዉ ወያኔን በህዝባዊ አመጽ ወይስ በህዝባዊ እምቢተኝነት ታግለን እናዉርደዉ የሚለዉ ጥያቄ ዛሬም ድረስ አዎንታዊ እልባት ባያገኝም ዛሬ ሌላ ቢቀር እንደቀድሞዉ የተቃዋሚዉን ጎራ ለሁለት ከፍሎ የወያኔ መጠቀሚያ ማድረግ አይችልም። የኢትዮጵያ ህዝብም እኔ ያለሁት ጉድጓድ ዉስጥ ነዉና ወይ ተደጋግፋችሁ አዉጡኝ አለዚያም በቻላችሁትና በሚታያችሁ መንገድ አዉጡኝ ነዉ የሚለን እንጂ በኛ መጨቃጨቅ የሱ የጉድጓድ ዉስጥ ቆይታ ዬትየለሌ እንዲሆን አይፈልግም። ዛሬ ይህንን ተደጋግፋችሁ ነጻ አዉጡኝ የሚለዉን የኢትዮጵያ ህዝብ ጥሪ ሰምተዉ በየጫካዉና በየበረሃዉ ከወያኔ ጋር የሞት የሽረት ትግል ለማድረግ የቆረጡ ኃይሎች የሚያደርጉት መሰባሰብና በተባበር ወገንን እጅግ የሚያበረታታ ጠላትን ደግሞ ያንኑ ያክል የሚያንቀጠቅጥ መልካም ጅምር ነዉ።
ከተለያዩ የአገራችን ኣካባቢዎችና ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተዉጣጥተዉ ወያኔን በሚገባዉ ብቸኛ ቋንቋ ለማነጋገር ቆርጠዉ የተነሱት የኢትዮጵያ ልጆች ወያኔን አንከባልለዉ የሚጥሉት ባነገቡት ጠመንጃ ብቻ ሳይሆን በህብረታቸዉና በአላማ ጽናታቸዉ እንደሆነ በሚገባ ያዉቃሉ። ለዚህም ነዉ ዛሬ እነዚህ ጀግኖች ባሉበት ጫካና በረሃ ሁሉ የሚሰማዉ መዝሙር . . . . ላንቺ ነዉ ኢትዮጵያ . . . ላንቺ ነዉ… ላንቺ ነዉ ኢትዮጵያ ላንቺ ነዉ… ላንቺ ነዉ ኢትዮጵያ ደሜን የማፈሰዉ የሆነዉ።
ዛሬ አገራችን ኢትዮጵያን ከዘረኞችና እነሱ ከገነቡት ዘረኛ ስርዐት ለማላቀቅ ዉስብስብነት ገብቷቸዉ ይህንን ዉስብስብ ትግል ከመታግል ዉጭ ሌላ ምንም አማራጭ እንደሌለ ተረድተዉ የትግል ህብረትና አንድነት የጀመሩ ብዙ ወገኖች አሉ። ይህ የሚያበረታታና ተስፋዉ የለመለመ ጅምር የሁላችንም ድጋፍና ተሳትፎ የሚያስፈልገዉና አለንልህ ሊባል የሚገባዉ አገራዊ ጅምር ነዉ። በዚህ ጅምር ዉስጥ ትንቅንቅ አለ፤ በዚህ ጅምር ዉስጥ መስዋዕትነት አለ፤ በዚህ ጅምር ዉስጥ ድል አለ። በህዝባዊ እምቢተኝነቱ ጎራ ከቅርብ ግዜ ወዲህ በብዙ የኢትዮጵያ ከተማዎች ዉስጥ ህዝቡ የወያኔን ግልምጫ፤ እስርና ድብደባና ግድያ ከምንም ባለመቁጠር በየአደባባዩ ወያኔን ፊት ለፊት መጋፈት ጀምሯል። ወያኔን በብዕራቸዉ የሚታገሉ ወጣቶችም ከዘላለም ባርነት የአንድ ቀን ነጻነት ይሻለናል ብለዉ በሰላ ብዕራቸዉ ህዝብን እንዳስተማሩ ቃሊቲ ወርደዋል። በህዝባዊ አመጹ ጎራ ደግሞ የአባቶቹን ታሪክ ለመድገም ቆርጦ የተነሳዉ የኢትዮጵያ ወጣት አዲሱን የኢትዮጵያ የፍትህ፤ የነጻነትና የእኩልነት ታሪክ በደሙ ለመጻፍ የከተማ ኑሮ በቃኝ ብሎ የጫካና የበረሃ ኑሮዉን ተያይዞታል።
ዛሬ ይህንን እንዳባቶቹ ዱር ቤቴ ብሎና ጠመንጃቸዉን አንግቦ ከወያኔ ጋር ትንቅንቅ የጀመረዉን ህዝባዊ አርበኛ የብሄረሰብ ስብጥር የተመከለተ ማንም ሰዉ የአገራችን ኢትዮጵያ ዳግማይ ትንሳኤ ደጃፍ ላይ መሆኑን በሙሉ አፉ ደፍሮ መናገር ይችላል። ወያኔ በነጋ በጠባ ከሚያስረዉና የወደፊቱን ካጨለመበት ወጣት ጀምሮ ገዳማቸዉን ካፈረሰባቸዉ መነኮሳትና ቤ/ክርስቲያናቸዉን አስካረከሰባቸዉ ካህናት ድረስ የትግሉ ጎራ ሁሉንም አይነት ኢትዮጵያዉያን በብዛት አካትቶ ይዟል።
ወያኔ ስልጣን እንደያዘ በሚቆይባት በእያንዳንዷ ቀን ተጨማሪ ወጣቶች እንደሚታሰሩ፤ተጨማሪ ሰላማዊ ሰልፈኞች እንደሚገደሉ፤ተጨማሪ ጋዜጠኞች ሽብርተኞች ተብለዉ እንደሚታሰሩ፤ ተጨማሪ ምሁራን አገራቸዉን ለቅቀዉ እንደሚሰደዱና የአገራችን የኢትዮጵያም አንድነት የበለጠ እየላላ እንደሚሄድ ሁላችንም በሚገባ እናዉቃለን። በሌላ አነጋገር ወያኔ ስልጣን እንደያዘ የመቆየት አንድ ተጨማሪ ቀን በሰጠነዉ ቁጥር የኛም ሆነ የአገራችን ህልዉና በቀላሉ የማናበጀዉ እጥፍ ድርብ ችግር ዉስጥ ይወድቃል። ይህ እናት አገራችን ኢትዮጵያ ላይ የተደቀነዉ ችግርና መከራ ገና ከጧቱ የታያቸዉ ኢትዮጵያዉያን ባለፉት ሃያ አመታት የየራሳቸዉን እርምጃ ሲወስዱ ቆይተዋል። በዚህ ሂደት ዉስጥ አንዳንዶች ዉድ ህይወታቸዉን ገብረዋል፤ ሌሎች ደግሞ ታስረዋል፤ ተደብድበዋል፤ አገር ለቅዉ ተሰድደዋል። እዚህ ላይ አንድ ሁላችንም በትክክል ልንገነዘበዉ የሚገባን ሀቅ አለ፤ እሱም የኢትዮጵያ ችግር የአንድና የሁለት ሰዉ ችግር አይደለም፤ በአንድና በሁለት ሰዎች የሚፈታ ችግርም አይደለም። ኢትዮጵያ የሁላችንም አገር ናት፤ ችግሩም የሁላችንም ነዉ፤ ወያኔን በቆራጥነት ታግለን አገራችንን ከመበታተን ህዝባችንን ደግሞ ከዘረኝነትና ከድህነት ማላቀቅ ያለብንም እኛዉ ነን። ወያኔ ስለጠላነዉ፤ ስለሰደብነዉ ወይም ስለጮህንበት ብቻ በህዝብና በአገር ላይ በደል መፈጸሙን አያቆምም:፡ እነዚህ በደሎችና ችግሮች የሚቆሙትና የኢትዮጳያ ህዝብ የሰላም አየር መተንፈስ የሚችለዉ ወያኔ ከስልጣን ሲወገድና በምትኩ ኢትዮጵያዉያንን በእኩልነት የሚያስተናግድ መንግስት በኢትዮጵያዉያን ተመርጦ ስልጣን ሲይዝ ብቻ ነዉ።
የኢትዮጵያ ህዝብ ለሰብዓዊ መብቱ፤ ለነጻነቱና ለእናት አገሩ አንድነት መከበር ትናንት ካደረገዉ ትገል የዛሬዉ እጅጉን የሚያበረታታ ቢሆንም አሁንም ይህንን ህዝባዊ አደራ ከተሸከሙ ኃይሎች የሚጠበቅ ብዙ ስራ አለ። ከላይ ከፍ ሲል ደጋግመን እንደጠቀስነዉ ከወያኔ ጋር በሚደረገዉ የትግል ሂደት ዉስጥ የህዝብ ኃይሎች የሚመኩበት ትልቁ ኃይል ህብረታቸዉና ከጎናቸዉ የተሰለፈዉ የኢትዮጵያ ህዝብ ነዉ። የተቃዋሚ ኃይሎች አለመተባበርና አለመግባባት ከጎናቸዉ በተሰለፈዉ ህዝብ ዉስጥም አለመግባባትና አለመተባበር ይፈጥራል:፡ ዘረኛዉ የወያኔ አገዛዝ እየተቃወምነዉና እየታገልነዉ ዛሬ ድረስ የደረሰዉ እኛ ዉስጥ የነገሰዉ አለመተባበርና አለመግባባት እየረዳዉ ነዉ። ስለዚህ ዛሬ ወያኔን ለማስወገድ ብቻ ሳይሆን ወያኔ ከተወገደ በኋላም የሚገጥሙንን ዲሞክራሲያዊ ተቋማትን የመገንባትና ህዝባዊ ስርዐትን የመፍጠር አደራ ጭምር ለመወጣት በህብረትና በአንድነት መቆም አለብን። አንድነታችንና ህብረታችን አንድ ስራ ሰርቶ ወያም አንድ ነጣላ አላማ ከግብ አድርሶ የሚቆም ሳይሆን የእኛን ሀላፊነት ተወጥተን ለልጅ ልጆቻችን የምናስተላልፈዉ ብሄራዊ ቅርስ መሆን አለበት።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!

Sunday, June 29, 2014

የዞን ዘጠኝ ጦማርያን ዛሬ ፍርድ ቤት ቀረቡ

June29/2014
ኢ.ኤም.ኤፍ – በድረ ገጾች ላይ ሃሳባቸውን በጽሁፍ ሲገልጹ የነበሩ፤ የዞን ዘጠኝ ጦማርያን ማህሌት፣ ኣቤልና በፈቃዱ በተሰጣቸው ቀጠሮ መሰረት ዛሬ እሁድ አራዳ ፍርድ ቤት ቀርበው ነበር። ሆኖም እንደተለመደው ተጨማሪ ጊዜ ቀጠሮ ተጠይቆባቸው ለተጨማሪ ምርመራ እንደገና ወደ እስር ቤት ተመልሰዋል። በዚህ አይነት የፍርድ ቤት ምልልስ ወጣት ጦማሪዎቹ ሁለት ወራትን አስቆጥረዋል።ከጦምሪዎቹ መካከል አቤል፣ ማህሌትና በፍቃዱ በፍርድ ቤቱ የተገኙት ከጠበቃቸው ኣመሃ መኮንን ጋር ነበር።
የዛሬውን ውሎ ከዘገቡት ድረ ገጾች መካከል ኢትዮ ሪፈረንስ እንዲህ በማለት ዘገባውን አቅርቧል። ጠበቃ አምሃ እንዳሉት ፖሊስ እንደለመደው 28 ቀን የጊዜ ቀጠሮ ጠይቆ የነበረ ሲሆን፣ ዳኛዋ የጠበቆቹን አስተያየት ሳትጠይቅ 14 ቀን ጦማሪዎቹ በእስር እንዲቆዩ ፈቅዳለች።በዚህም መሰረት ቀጣዩ ቀጠሮ ለሃምሌ 7 ተብሎኣል ።በዚያች በነበረችው የ ኣስር ደቂቃ የችሎት ጊዜ ጦማሪ በፈቃዱ ዘሃይሉ ”በፖሊሶች ሃሰተኛ ቃል አንድሰጥ ማሰገደድ ተደርጎብኛል” ሲል ለፍርድ ቤቱ ማስረዳቱ ተገልጿል።
በዛሬው ዕለት የጦማሪዎቹን የፍርድ ሁኔታ ለመከታተል ከ300 በላይ ሰዎች በስፍራው የነበሩ ቢሆንም የኣራዳን ግቢና ኣካባቢውን ለቀው እንዲሄዱ ፖሊሶች ሲያስገድዷቸው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል።
ዛሬ የታሰረው ዮናታን
ዛሬ የታሰረው ዮናታን
ወጣት ምኞት መኮንን
ወጣት ምኞት መኮንን
ከአነዚህም መሃል፣ የሰማያዊ ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ሃላፊን ዮናታን ተስፋየን (ፎቶ ይመልከቱ) ”ፎቶ ስታነሳ ነበር” በማለት ወደ አስር ቤት አንደወሰዱት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።በተመሳሳይ መልኩ በስፍራው  የነበረች  ወጣት ምኞት መኮንንም (ፎቶዋን ይመልከቱ) ”ፎቶ ኣንስተሻል” በሚል በፍርድ ቤት ፊት ለፊት በፖሊሶች ተደብድባ ወደ አስር ቤት መወሰዷ ተመስክሯል።
የጦማሪያኑን የፍርድ ውሎ የሚከታተለው ሰው ዛሬም እንደወትሮው በጠዋት ነው የተገኘው፡፡ አራት ሰዓት ካለፈ በኋላ የጦማሪያኑ ጠበቃ ‹‹መዝገብ ቤቷ ስለሌለች ነገ ከሰዓት ተብሏል›› ብለው ሲነግሩን በርካታ ህዝብ በተገኘበት አንዲት መዝገብ ቤት በመቅረቷ ብቻ የፍርድ ውሎው እንዲራዘም መደረጉ ገርሞን ስለጉዳዩ እያወራን ለጥቂት ደቂቃዎች ግቢው ውስጥ ቆየን፡፡ ከደቂቃዎች በኋላ ደግሞ እየመጡ ነው ተባለ፡፡
የውሎው ትዕይንት እዚህ ላይ ነው የተጀመረው፡፡
“ያለፈቃድ መሬቱንም ቢሆን ፎቶ ማንሳት አይቻልም” በማለት ፖሊስ ህዝቡን ያንገላታ እንደነበር የገለጸው ደግሞ ‘ፍሪደም ፎር ኢትዮጵያ’ የተባለው ድረ ገጽ ነበር። ዝርዝር ዘገባውን እንዲህ በማለት አቅርቧል።
ሶስቱም ጦማሪያን ሲመጡ ህዝቡ በጭብጨባ ተቀበላቸው፡፡ በድንገት እዚህ እዚያ የሚራወጡት ፖሊሶች ወደተሰበሰበው ሰው እየሮጡ በመምጣት የሰማያዊ ፓርቲ የሴቶች ጉዳይ አባል የሆነችውን ምኞት መኮንንን ‹‹ፎቶ ግራፍ አንስተሻል፡፡›› በሚል ማንገላላት ጀመሩ፡፡ በኃይል እየጎተቱ ሲወስዷትም ዮናታን ተስፋዬ ‹‹እኔን ውሰዱኝ›› ብሎ ምኞትን በኃይል እየገፈተሩ የሚወስዱት ፖሊሶች መሃል ገባ፡፡ ፖሊስ ግን እሱንም ማንገላላት ጀመረ፡፡ እሱንም አብረው ወሰዱት፡፡ ምኞትና ዮናታን ጦማሪያኑን ተከትለው ችሎቱ ወደሚገኝበት ቦታ ከተወሰዱ በኋላ ፖሊሶቹ ህዝቡ እንዲበተን ማስፈራራት ጀመሩ፡፡
ፖሊሶቹ ከሚመጡበት በኩል የርዕዮት ዓለሙ አባት ጠበቃ አለሙ፣ እህቷ እስከዳር አለሙ፣ ጋዜጠኛ ነብዩ ኃይሉ፣ 6 ያህል የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት አባላትና ሌሎች ጥቂት ሰዎች ‹‹ወዴት ነው የምንሄደው?›› በሚል እንደማይወጡ አሳወቁ፡፡ ፖሊሶቹ ‹‹ታዘነ ነው፡፡ ትወጡ እንደሆነ ውጡ!›› እያሉ ማስፈራራት ጀመሩ፡፡ ከፊት ያሉት ሰዎች ‹‹ችሎት መከታተል መብታችን ነው!›› ብለው አንወጣም ሲሏቸው እነ ምኞት ላይ የተወሰደውን እርምጃ ትክክለኛነት ለመግለጽ ፎቶ ማንሳት ክልክል መሆኑን አጽንኦት ሰጥተው ማስፈራራት ቀጠሉ፡፡ በተለይ አንዱ ፖሊስ ‹‹ያለ ፈቃድ ፎቶ ማንሳት አይቻልም፡፡ ሳይፈቀድ መሬቱንም ቢሆን ፎቶ ማንሳት አይቻልም›› ያለበት ሁሉንም ያስገረመ ነበር፡፡ በዚህ ፖሊስ አባባል የተሰበሰበው ሁሉ እያረረም ቢሆን ፈገግ ብሎበታል፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ ቃል አቀባይ በበኩሉ ይህንን መልዕክት አስተላልፏል። በዛሬው በአራዳ ችሎት ከተገኙት የሰማዊ ፓርቲ አባላትና አመራሮች መሀከል የህዝብ ግንኙነት ሀላፊ ሆነው ዮናታን ተሰፋዬን እና የሴቶች ጉዳይ አባል የሆነችውን ምኞት መኮንን “ፎቶ አንስታችኋል ለጥያቄ እንፍልጋችኻለን” በማለት የውስዷቸው ሲሆን በአሁኑ ሰአት የት እንዳሉ ስንጠይቅ ማእከላዊ “ኑ፡ የሚል መልስ ሰጥተውናል፤ ብሏል።
የጦማርያኑን ሁኔታ በቅርብ ሲከታተሉ ከነበሩት መካከል ጋዜጠኛ ደረጀ ሃብተወልድ “ሁሉም ያው ናቸው” በማለት ትዝብቱን አስፍሯል። የጋዜጠኛ ደረጀን አስተያየት ከዚህ ቀጥሎ አቅርበነዋል።
<<በፖሊስ 28 ቀን ተጨማሪ ቀጠሮ ተጠይቆ 14 ቀን ብቻ ተፈቀደ፤ ዻኛዋ አቃቤ ህግን አስጠነቀቁ…” ምናምን የሚለው ነገር ብዙውን ጊዜ ድራማ ነው። ፍትሐዊ ዻኝነት እንዳለ ለማስመሰል የሚደረግ የተቀናጀ ጨዋታ ነው። ለህሊናውና ለሙያው ያደረ እውነተኛ ዳኛ ቢኖርማ ብርቱካን ሚዴቅሳ- ስዬን እንዳሰናበተቻችው ፦<<እኚህን ልጆች ዋስትና የሚያስከለክል ቀርቶ አንድም ቀን እስር ቤት የሚያሳድር ክስ አላገኘሁባቸውም” ብሎ ቢያንስ በዋስ ያሰናብታቸው ነበር። ይህን ስል አንዳንድ ደፋር ወሳኔ የሚሰጡ፣ለሙያቸው እና ለህሊናቸው ያደሩ ዳኞች የሉም እያልኩ አይደለም። ለምሳሌ የጦማርያኑ ክስ እንደተጀመረ ጉዳዩን ይዘውት የነበሩትንና በጦማርያኑ ላይ የተመሰረተውን የሽብርተኝነት ክስ ያልተቀበሉትን ዳኛ መጥቀስ ይቻላል። ሆኖም አልፎ አልፎ እንደዛ ያሉ ደፋር ዳኞች ብቅ ሲሉ ከሚያስችሉት ችሎት ተነስተው በሌሎች እንዲተኩ ይደረጋሉ። ብዙዎቹ ግን <<አስፈቅደው>>ለማስመሰል ደፈር ያለ ነገር እየተናገሩ በ አጉል ተስፋ ንጹሀንን የሚያሹ፣የሚቀጡና በፍትህ ስም እኩይ ተልእኮ የሚፈጽሙ ሆዳሞች ናቸው።
አንዳንዴማ ልክ ቁጪ በሉዎች ሊሰርቁ ሲሉ እንደሚፈጥሩት የውሸት አምባጉዋሮ፤ ዳኞችና አቃቤ ህጎች እርስበርስ የውሸት እሰጥ እገባ በመግባት ድራማ እስከመሥራት ይደርሳሉ።ያኔ ልጁ፣እናቱ፣አባቱ፣ወዳጁ… የታሰረበት ፍትሕ የተጠማ ወገን ከጭንቀቱ ማየል የተነሳ የሰማው እሰጥ እገባ እውነት እየመሰለው <<ዳኛው እንዲህ አሉ፣ አቃቤ ህግን ገሰጹ፣ማረሚያ ቤትን አስጠነቀቁ …ፖሊስ ይህን ያህል ቀን ተጨማሪ ቀጠሮ ጠይቆ ይህን ያህል ብቻ ፈቀዱ..” እያለ ትንሽ ተስፋ ያደርጋል።
እውነታው ግን ሌላ ነው። የችሎት ሂደቱ የሚሄድበትም ሆነ ተከሳሾች የሚቀጡበት ወሳኔ ከመጋረጃ ጀርባ በቀጭን ሽቦ የሚመጣ እንጂ ከፍርድ ቤቱ መዝገብ የሚወጣ አይደለም። አዎ፣ የፍትሕ ስርዓቱ ምንም ተስፋ የለውም-ምንም! እዛ ፍርድ ቤት የሚደረገው ነገር ሁሉ ቴአትር ነው። ጉዳዩን እያስቻሉ ያሉት ዳኞች የድርሰቱ መሪ ተዋናይ ናቸው። ለህሊናቸው ያደሩ እውነተኛ ዳኞች ንጹሀን አንድ ቀንም እንዲታሰሩ አይፈቅዱም። የእውነተኛ ዳኞች መርህ፦” አንድ ንጹህ ሰው ያለጥፋቱ ከሚታሰር፤ እልፍ ተጠርጣሪዎች ቢያመልጡ ይሻላል” የሚል ነው። እውነተኛ ዳኞች በሙያቸውና በህሊናቸው የሚመሩ እንጂ፤ በባለስልጣናት ትእዛዝ የሚሽከረከሩ አይደሉም።
እና…እኒህኞቹ ማለትም፣ 28 ቀን ቀጠሮ ሲጠየቅ- 14 ቀን እያሉ፣ ተክሳሾች በማረሚያ ቤት ተደበደብን ሲሉ ደብዳቢውን በመቅጣት ፋንታ ፦” ሁለተኛ እንዲህ ያለ ነገር እንዳይደገም…” እያሉ የሚቀልዱት ዳኞች ከዐቃቤ ህጎቹና ከባለስልጣናቱ የተለዩ አይደሉም። እንደውም ከስርአቱ ቁንጮዎችና ከዐቃቤ ህጎቹ ባልተናነሰ ሁኔታ በህግም፣በታሪክም ተጠያቂ መሆን ያለባቸው፤ ንጹሀን የሚንገላቱበትን የትእዛዝ(የድርሰት) ፍትህ በመተወን እያስፈጸሙ ያሉት እንዲህ ያሉ አስመሳይ ዳኞች ናቸው።
ድሮ ሀገሬው በጉቦ ተቸግሮ ፍትሕ ቢያጣ ጊዜ፦
የጅብ ሊቀ-መንበር፣የዝንጀሮ ዳኛ፣ የጦጣ ጸሀፊ፣
ሁሉም ሌቦች ናቸው፣ ዘራፊ ቀጣፊ>> ብሎ ነበር። አዎ፣ሁሉም ያው ናቸው።

መዝገቦቹ መልሰው ተቀራረቡ የእምነት ክህደት ቃል በኃይል አስፈርመዋቸዋል

June29/2014
መዝገቦቹ መልሰው ተቀራረቡ
የእምነት ክህደት ቃል በኃይል አስፈርመዋቸዋል
ጽዮን ግርማ
የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት በስድስቱ ጦማሪያንና በሦስቱን ጋዜጠኞች ላይ የፌደራል ፖሊስ የተለያየ ምክንያት እየሰጠ ቀጠሮ የሚያራዝመውን ሁለት መዝገብ አንዴ ሲያቀራርበው መልሶ ደግሞ ሲያራርቀው ቆይቶ አሁን ደግሞ መዝገቦቹን መልሶ አቀራርቧቸዋል፡፡እስረኞቹ ራሳቸውን መከላከል በማይችሉበት ኹኔታ ፖሊስ ያረቀቀውን የእምነት ክህድት ቃል ተገደው እንዲፈርሙ አድርጓቸዋል፡፡
የሦስቱ ብሎገሮች አቤል ዋበላ፣በፍቃዱ ኃይሉና ማኅሌት ፋንታሁን ቀጠሮ ለዛሬ ሰኔ 22 ቀን 2006 ዓ.ም እንዲቀርቡ የሚል የነበረ ሲኾን ከጠዋት ጀምሮ ችሎቱን ለመታደም የመጣውን ቤተሰብ፣ጓደኞቻቸው፣ጋዜጠኞች፣ዲፕሎማቶችና የወጣቶች ደጋፊዎች በአጠቃላይ ወደ ሦስት መቶ የሚጠጋ ሰው ከችሎት ውስጥ የሚሰማውን አዲስ ነገር ለመጠበቅ በግቢው ውስጥ ቆመው ነበር፡፡ ከጠዋቱ አራት ሰዓት አካባቢ የእስረኞቹ ጠበቃ አቶ አመኃ መኮንን ተጠርተው የመዝግብ ቤት ጸሐፊዋ ስለሌለች ችሎቱ ለከሰዓት በኋላ እንደተዛወረ ይነገራቸዋል፡፡ እርሳቸውም ችሎቱን ለመከታተል ለቆመው ሰው መልዕክቱን ያስተላልፋሉ፡፡ ጥቂት ሰዎችም ይህን መልዕክት ሰምተው ግቢውን ለቀው ይወጣሉ ብዙኃኑ ግን እዛው እንደቆሙ መጨረሻውን ለማየት መጠባበቅ ይጀምራሉ፡፡
ሠላሳ ደቂቃ ያህል እንደተቆጠረ የእስረኞቹ መምጣት በጉምጉምታ መወራት ጀመረ፡፡ሁሉም ሰው ወደ ጓሮው በር ዐይኑን ተክሎ ቀረ፡፡ አቤል ዋበላ፣በፍቃዱ ኃይሉ እጃቸውን በሰንሰለት እንደታሰሩ ማኅሌት ፋንታሁ ከካቴና ውጪ ኾና እንደተለመደው በከፍተኛ የፖሊስ ጥበቃ ታጅበው ወደ ፍርድ ቤት ግቢ ውስጥ ዘለቁ፡፡ ወጣቶቹ ወደ ግቢው ፊታቸው ላይ የጥንካሬ መንፈስ የነበረ ሲኾን ተሰበሰበውም ሕዝብ በጭብጨባ ነበር የተቀበላቸው፡፡በዚህ መካከል እስረኞቹን አጅበው የመጡት ፖሊሶች ወደተሰበሰበው ሰው ዘለው በመግባት ፎቶ ስታነሳ ነበር ያሏትን ምኞት መኮንንን (የሰማያዊው ፓርቲ አባል) የተባለች ወጣት የያዘችውን ስልክ ቀምተው እየጎተቱ ወሰዷት፡፡ፖሊሶች በወጣቷ ላይ የሚፈጽሙት ማንገላት ያስቆጣው ዮናታን ተስፋዬ የተባለ ሌላ ወጣት ድርጊቱን በማውገዝ ለመገላገል ሲጠጋ እርሱንም ጨምረው ወስደውታል፡፡
ፍርድ ቤቱ ይህን ችሎት ማየት ከጀመረ ወዲህ እስረኞቹን አጅበው የሚመጡት ፖሊሶች ቀጠሮ ባለ ቀን ሁሉ ችሎት ለመከታተል የሚመጣውን ሰው ሲያንገላቱ፣ሲሰድቡና ሲዘልፉ ልክ እንደ መብታቸው የሚቆጥሩት ሲኾን እዛ ግቢው ውስጥ የተገኘው ሰው ችሎት ውስጥ ገብቶ በሚገባ መቀመጫ ቦታ ተሰጥቶት ችሎት የመከታተል መብት እንዳለው ቅንጣት ታክል አስበውት የሚያውቁ አይመስል፡፡ እንዲኹም ከችሎቱ ውጪ ፍርድ ቤት ግቢ ውስጥም ቢኾን ‹‹ፎቶ ማንሳት ክልክል ነው›› የሚል ማስጠንቀቂያ እስካልተለጠፈ ድረስ ከሁለት ሰው በላይ የኾነ ማንም ሰው የተሰበሰበበት ቦታ ላይ ፎቶ የማንሳት ሙሉ መብት እንዳለ የሚያውቁ አይመስሉም፡፡ በአጠቃላይ በዛ ቦታ ላይ ከእነርሱ ውጪ ሌላ ሰው የመቆም መብት ጭምር እንደሌለው ጠንቅቀው ስሚያውቁ ወደ ተሰበሰበው ሰው ተመልሰው፤‹‹ሁላችሁም ግቢውን ለቃችሁ ውጡ›› ሲሉ ትእዛዝ ሰጡ፡፡
ከፊት ለፊት ቆመው የነበሩት ሰዎች ከግቢው ላለመውጣት እንቢተኝነታቸውን አሳዩ፡፡በተለይ በእስር ላይ የምትገኛው ጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙ እህት እስከዳር ዓለሙ፣አባቷ አቶ ዓለሙ እና ሌሎች ወጣቶች አንድ ላይ ኾነው ግቢ ውስጥ መቆም መብት እንዳላቸው በመግለጽ ለመውጣት ፍቃደኛ ሳይኾኑ ቀሩ፡፡ የፖሊሶቹ ማስፈራሪያና ዘለፋ ግን ቀጠለ ሕዝቡ ግቢውን ለቆ የማይወጣ ከኾነ አድማ በታኝ ፖሊስ እንደሚጠሩ ጭምር በመግለጽ ማስፈራራት ቀጠሉ፡፡ፎቶ ማንሳት የተከለከለ እንደኾነ እና እንኳን ሰውን መሬቱንም ጭምር ማንሳት እንደማይቻል በማስፈራራት ጭምር በመግለጽ ሰውን ከግቢው ውስጥ ገፍተው ወደ ውች አስወጡት፡፡
ግንቦት ዘጠኝ ቀን 2006 ዓ.ም ውሎ በነበረውና ከዚያም ቀጥሎ በነበረው ችሎት ላይ እያንዳንዱ ተጠርጣሪ የወከለው ቤተሰብ አባል ወደ ችሎት እዲገባለት ተደርጎ የነበረ ሲኾን አሁን ግን ይህም መብት ተከልክሎ ችሎት ውስጥ በእስረኞቹ በኩል ከጠበቃቸው ከአቶ አመሐ መኮንን በስተቀር ማንም ችሎት ሳይገባ ቀርቷል፡፡ችሎት ከገቡም በኋላ ፖሊስ በተጠርጣሪዎቹ ላይ ተጠማሪ ሃያ ስምንት ቀን እንዲፈቀድለት የጠየቀ ሲኾን ፍርድ ቤቱ፤‹‹ከዚህ በኋላ የሚሰጣችሁ ሃያ ስምንት ቀን የለም ዐሥራ አራት ቀን ይበቃችኋል፡፡ ችሎቱም ከዚህ በኋላ እሁድ ስለማይሰየም ቀኑ አንድ ቀን ተቀይሮ ሰኞ ሐምሎ 7 ቀን 2006 ዓ.ም›› ሲል ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
የጊዜ ቀጠሮው መዝገብ ሲከፈት የአቤል ዋበላ፣በፍቃዱ ኃይሉና የማኅሌት ፋንታሁንን ጉዳይ የያዘው መዝገብ ከሌሎቹ ከስድስቱ አስረኞች ጋራ በአንድ ቀን ይለያይ የነበረ ሲኾን በመካከሉ አንዲት ዳኛ የሃያ ስምንት ቀን ጥያቄውን ባለመቀበላቸው ጉዳዩ በዐሥራ አምስት ቀን ተለያይቶ እንደነበር ይታወሳል አሁን ደግሞ መዝገቦቹ መልሰው ተቀራርበዋል፡፡ የስድስቱ ቅዳሜ ሐምሌ 5 ቀን ይታያል የሦስቱ ደግሞ ሰኞ ሐምሌ ሰባት ቀን፡፡
በዛሬው ቀጠሮ በፍቃዱ ኃይሉ ያላመነበትን የእምነት ክህደት በኃይል እንዲፈርም መገደዱን ተናግሯል፡፡ እንደምንጮች ገለጻ ከኾነ አብዛኞቹን እስረኞች በከፍተኛ ጫናና በድብደባ በመርማሪ ፖሊሶች የተረቀቀውንና በእነርሱ ሐሳብ የተዘጋጀ የእምነት ክህደት ቃል ላይ ‹‹የሰጠሁት ቃል የኔ ነው ጥፋተኛ ነኝ›› ብለው እንዲፈርሙ ተደርጓል፡፡
የፍርድ ቤቱ መዝገቡን ማጠጋጋትና የእምነት ክህደት ቃሉ ፊርማ እስረኞቹን ለመክሰስ ዝግጅቱ መጠናቀቁን ማሳያዎች በሚል በሕግ ባለሞያዎች ተገምቷል፡፡
(ፎቶዎቹ ከታምሩ ጽጌ ገጽ ላይ የተገኙ ናቸው)
Tsion Girma's photo.
Tsion Girma's photo.
Tsion Girma's photo.

ኢትዮጵያዊው-ኖርዌጂያን ኦኬሎ ኦካይ ኦቻላ ”ሞት ሊበየንበት ይችላል” -በሽብርተኝነት ክስ ሞት ተፈርዶባቸው ሞታቸውን የሚጠባበቁ 127 ሰዎች ኣሉ

June29/2014

በኖርዌይ ሃገር ውስጥ በኖርዌጂያንኛ የሚታተመው ዳግብላደት የተባለው ጋዜጣና ድረ-ገጽ ”ኢትዮጵያዊው-ኖርዌጂያን” ኦኬሎ ኦካይ ኦቻላ በሚቀጥለው ሳምንት ሞት ሊበየንበት ይችላል” ሲል ኣውጥቶኣል።

”ባለፈው ሳምንት ለማወቅ እንደተቻለው ዕድሜው 52  የሆነና  ኦኬሎ ኦካይ ኦቻ  የተባለ ኖርዌጂያን ኢትዮጵያ ውስጥ በሽብርተኝነት ተከሶ በእስር ላይ ይገኛል።” tiltalt for terror በማለት የጀመረው የኖርዌዩ ዳግብላደት ሲቀጥልም…”የኢትዮጵያ መንግስት ቃለ ኣቀባይ እንደሚለው ገንዘብ ኣሰባስቦና ኣጥቂ ቡድን መልምሎ ኣደጋ ለማድረስ ሲሞክር ያዝነው በማለት መከሰሱን ያትትና በበኩላቸው የኖርዌዩ የሰብኣዊ መብት ጥበቃም ሆኑ የዓለም ኣቀፉ ሰብኣዊ መብት ተሟጋቾች ድርጊቱን በጥብቅ ያወገዙት ሲሆን፣ ኣያይዘውም ለዚሁ ድረ-ገጽ ታሳሪው ግለሰብ ያለበት ሁኔታ ከወትሮው የከፋ እንደሆነም ስጋታቸውን እንደገለጹለት ያወሳል።

 ኢትዮጵያንም ሆነ የቀድሞው የጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንት፣ በኣሁኑ ወቅት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ውስጥ የሚገኙትን  ኦኬሎ ኦካይ ኦቻ ”በሚገባ ያውቃሉ” ያሉዋቸውን የሰብኣዊ መብት ተሟጋችና ኖርዌጂያን ፈሊክስ ሆርነ ን  ኣነጋግሮ ድረ-ገጹ ያገኘው መልስ ”ኖርዌጂያኑን ኦኬሎ በሚቀጥለው ሳምንት የሚሰየመው ችሎት ሞት ሊበይንበት ይችላል” በማለት የገለጹ ሲሆን ኣክለውም፣
”በሃገሪቷ ውስጥ በሽብር ወንጀል የሚከሰሱት ዜጎች የሚገጥማቸው የሞት ፍርድ ነው። ነገር ግን እነዚህ ሞት የሚፈረድባቸው ዜጎች ምንም ማስረጃ ያልቀረበባቸው ናቸው። በሽብር ክስ ስለተከሰሱ ብቻ ዕድላቸው ይሄው ነው። በሞት ቀጠና የሚገኙትን ዜጎች የሚዘግበው ዓለም ኣቀፉ ድርጅት በኢትዮጵያ በእስር ቤት ውስጥ በሞት ቀጠና (ሴል) የሚሰቀሉበትን ወይም የሚገደሉበትን ጊዜ የሚጠባበቁ 127  ዜጎች  ይገኛሉ ሲል ፈሊክስ ሆርነ ለድረ- ገጹ ገልጸዋል።
 ሌላው ኣምነስቲ ኢንተርናሽናል ውስጥ የሚሰሩት ጌራልድ ካዶርድ ”የኢትዮጵያ መንግስት ኦኬሎን እንደከሰሰው በሽብር ወንጀል ጦር ሲመለምልና ሲያደራጅ ኣግኝቶት ከሆነ፣ የሞት ቅጣት ይበይኑበታል የሚለው ስጋቴ ነው።የፍርድ ሂደቱን እንደምናየው የሞት ቅጣቱ በፍርድ ቤቱ ይለወጣል የሚል ዋስትና የለንም።” ኣያይዘውም ባለፈው ዓመት 8 ጋምቤላ ውስጥ ያሉ የተቃዋሚ ድርጅት ኣባላቶች በሽብርተኝነት ከሰዋቸውና የሞት ፍርድ በይነውባቸው ሞታቸውን በመጠባበቅ ላይ ናቸው።”
 ጭፍጨፋ
ኦቻላ ከሽብርተኛ ጋር ግንኙነት እንዳለው ኣላውቅም። ነገር ግን በጋምቤላ ውስጥ መንግስትን የሚቃወም ጠንካራ ተቃዋሚ ድርጅት የለም። መንግስትን ለመቃወም የሚነሱትንም ሽብርተኛ የሚል ስም በክልሉ መንግስት ይለጠፍባቸዋል።
 ኦቻላ የጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንት የነበረ ጊዜ፣ massakre 13. desember 2003. የ 1000 በላይ  የኣባወራዎች መኖሪያ ቤቶች በገዥው ስርዓት ወታደሮች ሲቃጠልና ከ400 የኣኙዋክ ንጹሃን ተወላጆች በጥይትና በስለት ሲታረዱ በስፍራው  ነበር። ይሄንንም ተከትሎ ወደ ደቡብ ሱዳን ስልጣኑን በመተው መሰደዱንና ከዚያም ከቤተሰቡ ጋር  በኖርዌይ ”ትሮንዳሄም” በተባለ ቦታ  በስደተኝነት በመግባትና ፈቃድ ጠይቆ በ2009 ዓ.ም የኖርዌጂያን ዜግነት ተሰጥቶት ነበር።
  ቢሆንም  ከ 2012 ጀምሮ በጋምቤላ ውስጥ በሚከናወነው ሁኔታዎች ይረበሽ ነበር። በዚህም የተነሳ ወደዚያው ኣቅንቶኣል።ማድረግ ግን ኣልነበረበትም።በኣንድ ወቅት በክረምት ወራት የሱዳን የመረጃና ደህንነት ሰራተኞች በሱዳን ጁባ ውስጥ ያለን ኣንድ ሆቴል በድንገት ከበቡት። ከዚያም በውስጡ የነበሩትን የሱን ጓደኞች  ኣስረዋቸው ወደ ኢትዮጵያ  ልከዋቸዋል በማለት ድረ- ገጹ ኣትቶኣል።
ቶርቸር 
በኣሁኑ ሰዓት ኦኬሎ በእስር ቤት ውስጥ ባልተረጋገጠ መረጃ ውስጥ ይገኛል። ይህ ኖርዌጂያን በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ማወቅ ኣይቻልም።በኢትዮጵያ ውስጥ በሽብርተኝነት በእስር ቤት ውስጥ ሆኖ  የእናትነት እንክብካቤን ማግኘት ህልም ነው።እስረኞች ለቶርቸርና ስቃይ የተጋለጡ  መሆናቸውን ፈሊክስ ሆርነ  ለድረ-ገጹ ኣስረድተዋል።
የኦኬሎን የፍርድ ሁኔታ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኘው ሪፖርተር የተሰኘው  ጋዜጣ ችሎቱ  ጁላይ 1 ይውላል ብሎ ቢገልጽም፣ የእኛ Dagbaldet በሲዊድን ያለውን የኢትዮጵያ ኣምባሳደር ለማግኘት ሞክረን ያልተሳካልን ሲሆን፤ ዓለም ኣቀፉን የሰብ ኣዊ መብት ተሟጋች ድርጅትንም ሆነ በኣዲስ ኣበባ ካለውም የኖርዌይ ኤምባሲ ትክክለኛ የችሎት ጊዜውን ማረጋገጥ ኣልተቻለም።
የኖርዌይ የውጭ ጉዳይም ለኣንድ ኣዲስ ኖርዌጂያን በኣደጋ ውስጥ በሚሆንበት ጊዜ፣ ወይም ኣደጋ በገጠመው ወቅት እንዴት መከላከል  እንዳለበት ከድረ- ገጹ ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ መስጠት ኣልፈለጉም።ድረ- ገጹ   ምላሽ በማጣቱም ይመስላል በኮንጎ ውስጥ ኖርዌጂያዊው Joshua French  በሞት ሲቀጣና፣  Shahid Azim  በኣስገድዶ መድፈር ወንጀል ፖኪስታን ውስጥ ተይዞ ሞት ሲፈረድበትም ኣላስጣሉትም በሚል ኣጣቅሰው ያለፉት። ቢሆንም ይላሉ የውጭ ጉዳይ ቃል ኣቀባይ ፍሮደ ኣንደርሰን፥ እስከኣሁን ከተከሳሹ ስለ ፍርድ ውሳኔውንም  ሆነ  ስለ ችሎቱ ቀን የምናውቀው የለም በማለት ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ ያለው የኖርዌይ ኣምባሳደር  ኦኬሎ ኦካይ ኦቻላን በተመለከተ ተደጋጋሚ  ጥያቄዎችን ለኢትዮጵያ መንግስት ኣቅርቦኣል። ኦኬሎ ያለበትን ሁኔታ፣ የፍርድ ሂደቱን ለመከታተልና በእስር ቤት ለመጎብኘት፣ ቢሆንም  ከኢትዮጵያ መንግስት ምንም  ምላሽ  ኣልተገኘም። የኖርዌይ የውጭ ጉዳይ ቢሮ ሁኔታውን በኣደገኛነት እንደሚያዩትም ሳይገልጹ ኣላለፉም።
ባለፈው ሳምንት  የኦኬሎ ባለቤት ኦባ ኦድዋ ኦመት kona Obo Adwo Omot fram i Dagbladet  ”… ባለቤቴ ሽብርተኛ ሳይሆን የፖለቲካ እስረኛ ነው” በማለት ገልጻ ነበር። ይህችው የ ኣራት ልጆች እናት የሆነችው ባለቤቱ ባለፈው ሳምንት እንደገለጸችው፣ ”…በኣሁኑ ሰዓት በዚህ ጠባብ ክፍል ከኣራት ልጆቼ ጋር እገኛለሁ። ምንም የማውቀው ነገር የለም። ባለቤቴም የሚያውቀው ነገር የለም። የኖርዌይ መንግስት የተቻለውን ሁሉ ኣድርጎ ባለቤቴን ከእስር እንዲያስወጡልኝ እማጸናለሁ በማለት ነበር የገለጸችው።

Saturday, June 28, 2014

የመቐለ የተቃውሞ ሰለማዊ ሰልፍ ተከለከለ! – አብርሃ ደስታ

June 28/2014
ህወሓቶች የመቐለ ህዝብ ዓፈናውን በሰለማዊ ሰልፍ እንዳያሰማ ለማፈን ያህል የነገው የመቐለ የተቃውሞ ሰለማዊ ሰልፍ ከልክሏል። በደብዳቤ እንዲያሳውቁን በጠየቅነው መሰረት የደብዳቤው ይዘት ምን መሆን እንዳለበት ለስድስት ሰዓት ያህል ከተወያዩ በኋላ እነሆ ቀኑና ይዘቱ አዛብተው ሰጥተውናል። ስህተት አለው ስንላቸው፤ ዝም ብላቹ ያዙ እሱም በስንት መከራ ነው ብለውናል። ባጭሩ የተቀመጠው ምክንያት ክልላዊና ከተማዊ ዝግጅት ስላለን አይመችም፤ በቂ የፀጥታ ኃይልም የለንም የሚል ነው። ግን ነገ ምንም ዝግጅት እንደሌለ አረጋግጠናል። በቂ የፖሊስ ኃይል እንዳለም የታወቀ ነው። ንፁሃን ዜጎች ለመደብደብና ለማሳሰር ፖሊስ ያላጡ ለሰለማዊ ሰልፍ ኃይል የለንም እያሉን ነው። ደሞኮ ለሚፈጠር ችግር ሓላፊነት ትወስዳላቹ ብለው አስፈርመውናል። ሌላ ደግሞ የፎርም ችግር እንዳለ ፅሑፉ ያትታል። የምን ፎርም መሆኑ አይታወቅም። ለማንኛውም ሰልፉ ለመከልከል ፈልገው በደብዳቤው የሚፃፍ ምክንያት ማጣታቸው ነው የሚያሳየው። ደብዳቤው ለህዝብ እንበትነዋለን ስላልናቸው ‘ሌላ ግዜ የምንፈቅድ መሆኑን እናሳውቃለን’ ይላል ደብዳቤው። ባጠቃላይ ግን ህወሓት የመቐለ ህዝብ ድጋፍ እንደሌለው እንዲጋለጥ አልፈገምና ከልክሎታል። ጨቋኝ ስርዓት የህዝብ ድጋፍ የለውም። የህዝብ ድጋፍ እንደሌለው እንዲታወቅ ግን አይፈልግም። ሰልፉ ሌላ ግዜም ቢሆን ይደረጋል። ለነገ ግን የመቐለ ህዝብ ሰለማዊ ሰልፍ የመውጣት መብቱ መነፈጉ ግልፅ ሆኗል።

በአ.አ ዩኒቨርሲቲ 52 ተማሪዎች በ”ዲሲፕሊን” ሰበብ ፖለቲካዊ ክስ ተመሰረተባቸው (ዝርዝራቸውን ይዘናል)

June 28/2014
ዘ-ሐበሻ
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመብት ጥያቄ አንስተው በሃገራዊ ጉዳይ ነቃ ያለ ተሳትፎ የሚያደርጉ 52 ተማሪዎች ላይ የዲሲፕሊን ክስ መመስረቱ ተሰማ። የዲሲፕሊን ክስ የተመሰረተባቸውን ተማሪዎች ስም ዝርዝር የያዘውን ወረቀት በማህበራዊድረገጾች ላይ የለቀቁት የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች ክሱ የተመሰረተባቸው ሰኔ 21 ቀን 2006 ዓ.ም ከጠዋቱ በ2 ሰዓት በተማሪዎች ጽ/ቤት እንዲገኙ ት ዕዛዝ ተሰጥቷል።

ምናልባትም እነዚህ በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ትኩረት አድርገው የሚ ንቀሳቀሱት ተማሪዎች ላይ በዲሲፕሊን ሰበብ ፖለቲካዊ እርምጃ ሊወሰድባቸው እንደሚችል የቅርብ ምንጮች ለዘ-ሐበሻ ያስታወቁ ሲሆን ዩኒቨርሲቲው ይህን እርምጃ ከወሰደ ሌላ የተማሪዎች አመጽ እንዲነሳ ምክንያት ሊሆን እንደሚችል ታዛቢዎች ይናገራሉ። በዲሲፕሊንክ ክስ ሰበብ የፖለቲካ እርምጃ ሊወሰድባቸው የተዘጋጁት ተማሪዎች ስምዝርዝር የሚከተለው ነው፦




ጥቂት ነጥቦች በፍትህ ጉዳይ ላይ

June 28/2014

ጥቂት ነጥቦች በፍትህ ጉዳይ ላይ

ጥቂት ነጥቦች በፍትህ ጉዳይ ላይ

ታደሰ ብሩ

1.     መግቢያ

ህወሓት በሥልጣን ላይ በከረመ መጠን የኢትዮጵያ ሕዝብ በፍትህ እጦት የሚደርስበት መከራ እየጨመረና እየመረረ በመምጣቱ “ፍትህ አጣን፤ የፍትህ ያለህ” የሚሉ እሮሮዎች ከቀድሞው በበለጠ መልኩ እየጎሉ መጥተዋል። በከተማውም በገጠሩም፣ ከእድሜ ባለፀጋውም ከወጣቱም፣ ከወንዱም ከሴቱ፣ ከክርስቲያኑም ከሙስሊሙም ወገኖቻችን የሚሰማው ጩከት “የፍትህ ያለህ” የሚል ነው። የፍትህ እጦት ነው ወገኖቻችንን በገዛ አገራቸው ተፈናቃይ ያደረጋቸው፤ የፍትህ እጦት ነው ገበሬዎች ማሳቸው ለባዕዳን ሲሰጥ አንጀታቸው እያረረ ዝም እንዲሉ የሚያደርጋቸው፤ የፍትህ እጦት ነው ነጋዴዎች ሱቆቻቸው በእሳት ሲጋዩ “ጉዳዩ  ይጣራልን”  ማለት እንኳን ያላስቻላቸው፤ የፍትህ እጦት ነው የእምነት ነፃነታችንን እንኳን ማስከበር ያላስቻለን።
ፍትህ ሰዎች በግልም በቡድንም ተሳስበው እና ተጋግዘው እንዲኖሩ የሚያደርግ የበጎ ሥነ-ምግባር መርሆች ስብስብ ነው። ፍትህ ነው ማኅበረ-ሰብን ከማኅበረ-አራዊት የሚለየው። ማኅበራዊ ኑሯቸውን በሥርዓት አደራጅተው የሚኖሩ እንስሳት መኖራቸው ቢታወቅም (ለምሳሌ የጉንዳን ሠራዊት፤ የንብ መንጋ) በእውቅ (Consciously) የተገነባ የፍትህ ሥርዓት ያለው የሰው ልጅ ብቻ  ነው። ፍትህ ሰውኛ እሴት ነው።
ምንም ዓይነት ፍትህ የሌለበት ማኅበረሰብን ለማሰብ ብንሞክር በአዕምሮዓችን ሊመጣልን የሚችለው እያንዳንዱ ግለሰብ፣ ከፍ ካለ ቤተሰብ፤ ከዚህ በላይ ከፍ ካለ ደግሞ የተዛመዱ ቤተሰቦች የፈጠሩት ስብስብ ነው። እያንዳንዱ ግለሰብ ወይም በዝምድና የተሳሰረ ስብስብ የገዛ ራሱን ወይም ቡድኑን ለማኖርና ከጥቃት ለማዳን የሚጥርበት ሥርዓት እናገኛለን። በዚህ ሥርዓት ውስጥ “የሥጋ” ዝምድና (ለምሳሌ እናትና ልጅ) ብቸኛው ማስተሳሠሪያ ይሆናል። በሌላ አነጋገር ዘር ብቸኛ የስብስቡ ማስተሳሠሪያ ይሆናል። በማኅበረ-እንስሳት ውስጥ መንጋን የሚያስተሳስረው በዘር መነሻነት የተፈጠረ አብሮ ውሎ ማደር ነው። ፍትህ በሌለበት ማኅበረሰብም ውስጥ የሚዛመዱ ቤተሰቦች ራሳቸው በተለያየ ስያሜ ወደሚጠሩ ስብስቦች ማደግ ይችላሉ። ትልቅም ይሁኑ ትንሽ፣ ስብስቦቹን የሚያገናኛቸው ዝርያቸው ነው። በማኅበረ-እንስሳት ውስጥ በመንጋዎች መካከል የማያቋርጥ ትንንቅ ይኖራል። በማኅበረ-እንስሳት ደካማው ብቻ ሳይሆን ጠንካራውም ቢሆን ሕይወቱን በሰቀቀን ማሳለፉ የግድ ነው። ጠንካራው መንጋ ከሱ የባሰ ጠንካራ መንጋ  እንዳይመጣበት እንደሰጋ ይኖራል። ፍትህ የሌለበት ማኅበረሰብም እንደዚያው ነው። ፍትህ በሌለበት፣ ሰዎች በዘር መደራጀታቸው ተፈጥሮዓዊ የመሆኑን ያህል እርስ በርሳቸው መጣላታቸውም እንደዝያው የማይቀር ተፈጥሮዊ ነው። በቡድኖች መካከል ያለው ጦርነት በአንዱ ቡድን ጊዜዓዊ አሸናፊነት ጋብ ሲል በቡድኑ ውስጥ ባሉ ቤተሰቦች መካከል ጦርነት ይነሳል፤  ያ ጋብ ሲል ደግሞ በእያንዳንዱ ግለሰብ መካከል ይጀመራል። ሲከፋ ወገንና ጠላት ያልለየ ሁሉም ከሁሉም ጋር (all against all) ጦርነት ውስጥ ይገባል። ይህ ዓይነቱ ሁኔታ ነው ህገ-አራዊት የሚባለው። ፍትህ በሌለበት የሰው ልጆች ሕይወት ወደ ህገ-አራዊት ያሽቆለቁላል።
ወያኔ አገራችንን እንዲህ ወደ አለ አስቀያሚና አስፈሪ ሁኔታ እየገፋት ነው። ፍትህ ድራሿ ጠፍቶ፣ ዘር ብቻውን የኑሮ መሠረት ሲሆን የቁልቁለት ጉዟችን የሚያደርሰን ወደ ህገ-አራዊት መሆኑ የማይቀር ነው።

2.   ህግ፣ ፍትህ እና የህግ የበላይነት

ህግ እና ፍትህ በጥብቅ የተቆራኙ ቢሆንም የተለያዩ ጽንሰ-ሀሳቦች ናቸው። ህግ “ይህንን አድርግ፤ ያንን አታድርግ” የሚል ድንጋጌ ነው። አቅም ያለው ሁሉ የፈለገውን ህግ አውጥቶ ሊያስፈጽም ይችላል። ፍትህ፣ ሰዎች ተሳስበው እና ተጋግዘው እንዲኖሩ የሚያደርግ፤ አድዎንና ጥቃትን የሚከላከል፤ በዳይን የሚቀጣ፣ ተጠቂን የሚክስ በጎነት ነው። ፍትህ የማኅበራዊ ተቋማት ቀዳሚ በጎ ውጤት ነው። ህግ መሣሪያ ሲሆን ፍትህ ህጉ በተግባር ላይ ሲውል የሚገኘው ውጤት ነው። ጥሩ ህግ በሥራ ላይ ከዋለ ፍትህን ያስገኛል። ጥሩ ህግ ኖሮ ሥራ ላይ ካልዋለ ህጉ መኖሩ ብቻውን ፍትህን አያስገኝም። መጥፎ ህግ ደግሞ ፍትህን ያጓድላል፤ ኢፍትሃዊነትን ያነግሳል። “የህግ የበላይነት” ሲባል በሁሉም ላይ ተፈፃሚ የሚሆን ህግ አለ ማለት ነው።
የህግ የበላይነት እንዲከበር ቢያንስ ሁለት ነገሮች መሟላት ይኖርባቸዋል።
justice
2.1.  ህግ፣ ፍትሃዊ ይሁንም አይሁን፣ ያለ አድልዎ በሥራ ላይ መዋል አለበት
መጥፎም ይሁን ጥሩ፣ አንድ ህግ በሁሉም ላይ እኩል ሥራ ላይ ከዋለ የህግ የበላይነትን አንድ መሠረታዊ መሥፈርት አሟላ ማለት ይቻላል።  በተለይም ህግ አስፈፃሚው በህጎቹ ራሱ የሚገዛባቸው መሆን አለመሆኑ ቁልፍ ጉዳይ ነው። ህግ አውጭው የሚያወጣቸውን ህጎች ህግ አስፈፃሚው ሲፈልግ በሥራ ላይ የሚያውላቸው፣ ሳይፈልግ ደግሞ የሚተዋቸው ከሆነ፣ የህጎቹ መኖር ለህግ የበላይነት መከበር የሚሰጠው ፋይዳ የለም።
በሀገራችን ወያኔ የሚያወጣቸው ከልካይ ህጎች ተቀናቃኞቹን እንጂ ራሱን ወያኔን አይከለክሉትም። ለምሳሌ በፀረ-ሽብር ህጉ፣ የወያኔ አሻንጉሊት ፓርላማ በሽብርትነት ከፈረጃቸው ድርጅቶች ጋር መነጋገር ያስቀጣል። ይህ ክልከላ ግን በራሱ በወያኔ ላይ አይሠራም፤ ከአብነግ ጋር ይፋ ለሆነ ድርድር ላይ መቀመጡ በራሱ ሚዲያ በይፋ ገልጿል።  “ግንቦት 7 ከኤርትራ መንግሥት ጋር ተባብሮ  ይሠራል” ሲል በከሀዲነት ይወነጅላል፤ ወያኔ እራሱ ግን ከሰባ ጊዜ በላይ  ከኤርትራ ጋር አብሮ ለመሥራት ሙከራ አድርጎ እንዳልተሳካለት በመግለጽ ያማርራል።
ወያኔ የሚያወጣቸው ህጎች ፍትሃዊነት የጎደላቸው ቢሆንም እንኳን በትክክል ሥራ ላይ ውለው ቢሆን ኖሮ የተሻለ ነበር። ወ/ት ርዕዮተ ዓለሙ ላይ በመጀመሪያ 14 ዓመት ከዚያ ደግሞ በይግባኝ 5 ዓመት የተፈረደባት የፀረ-ሽብር ህጉ መጥፎ ስለሆነ ብቻ አይደለም። ዳኝነትና ዳኛ ቢኖር ኖሮ በዚሁ ህግ ተከራክራ ነፃ መውጣት ትችል ነበር። ዳኝነት ኖሮ ቢሆን ኖሮ እስክንድር ነጋ በተከሰበት ኢፍትሃዊ ህግም ቢሆን ተከራክሮ ነፃ ይወጣ ነበር። የአንዱዓለም፣ የሙስሊም ማኅበረሰብ መሪዎች እና ሌሎች በርካታ ወገኖቻችን ጉዳይም እንደዚሁ ነው፤ ዳኝነት ቢኖር ኖሮ በተከሰሱበት ህግ ተከራክረው ነፃ መውጣት ይችሉ ነበር። ዳኝነት ኖሮ ቢሆን ኖሮ ብዙዎቹ ተከሳሾች መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ ይሰናበቱ ነበር።
ዛሬ አገራችን ውስጥ ያለው የህግ ችግር የመጥፎ (የኢፍትሃዊ) ህጎች መብዛት ብቻ አይደለም። ችግራችን ከዚያም ያልፋል። ባጠቃላይ የሚሠራ ህግ የለም፤ ዳኝነት የለም። ህገ-አልባነት ህግ ሆኗል።
2.2.  የህጎች ፍትሃዊ መሆን አስፈላጊነት
ህግ ሁሉ ግን ወደ ፍትህ አያደርስም። ፍትህን የሚያሰፍኑ ህጎች አሉ፤ ኢፍትሃዊነትን የሚያሰፍኑ ህጎችም ሊኖሩ ይችላሉ። የወንድና ሴት መሳሳም የሚያስቀጣበት አገር አለ። እንደኛ አገር ደግሞ መንግሥት ያልወደደውን ጋዜጣ ማንበብ የሚያስቀጣበት አገር አለ። የህግና የፍትህ ግኑኝነት ውስብስብ ነው። ለምሳሌ፣ “ሰዎች ሁሉ እኩል መስተናገድ አለባቸው” የሚል ህግ ቢወጣ በግልቡ ሲታይ ችግር ያለው ባይመስልም በሥራ ላይ በሚውልበት ጊዜ ግን ፍትሃዊ ላይሆን ይችላል። አንድ የጤና ጣቢያ ለአንድ ጤነኛ ባለጉዳይ እና የአካል ጉዳት ላለበት ሌላ ባለጉዳይ እኩል መስተንግዶ መስጠት አለብኝ ቢል ኢፍትሃዊ ነው። ከሚሰጠው አገልግሎት እኩል ተጠቃሚ እንዲሆኑ የአካል ጉዳተኛው የተለየ መስተንግዶ ሊሰጠው ይገባል። ከላይ በምሳሌነት የተጠቀሰው ዓይነት በደምሳሳው ሲታይ ችግር ያለበት የማይመስል ቀና ህግ እንኳን በሥራ ላይ በሚውልበት በፍትህ ሚዛን መታየት ይኖርበታል።
ህግ ተብለው በሥራ የሚውሉ ድንጋጌዎች ገና ከመነሻው በማያሻማ ሁኔታ ከፍትህ ጋር የተጣሉ ሲሆኑ ምን ይደረጋል? ለምሳሌ፣ መነጋገርንና ማሰብን የሚከለክል ህግን እንዴት መቀበል ይቻላል? ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግን የሚከለክል ህግን እንዴት መቀበል ይቻላል? መደራጀትን የሚከለክል ህግ እንደምን መቀበል ይቻላል? ለፍትህ ግድ ያለው ሰው ወይም ቡድን እንዲህ ዓይነት ህጎችን በማክበር ሳይሆን በመጣስ ነው ለፍትህ ዘብ መቆም የሚችለው። በህግ የበላይነት ሰበብ ለኢፍትሃዊ ህጎች መገዛት ከተጠያቂነት የማያድነውም ከህጎች ሁሉ በላይ የሆነው የፍትህ ስሜት በውስጣችን ሊኖር ስለሚገባው ነው። ዛሬ በወገኖቻችን ላይ ሰቆቃ እየፈፀሙ (ቶርቸር እያደረጉ) ያሉ አረመኔዎች ዛሬ ያለው ህግ ይህን እንዲፈጽሙ ቢያዛቸው እንኳ ነገ ሲጠየቁ “እኔ ህጉ ያዘዘኝን የፈፀምኩት፤ የሥራ ግዴታዬን ነው የተወጣሁት” ማለት የማያድናቸው ኢፍትሃዊ ትዕዛዝን፣ ደንብንም ሆና አዋጅን የመቃወሚያ ህሊና የተሰጣቸው በመሆኑ ነው።
ሰው ሆነን ተፈጥረን በሰዎች ማኅበር ውስጥ በማደጋችን ብቻ የተወሰነ የፍትህ ስሜት በውስጣችን አለ።  በዚህ የፍትህ ስሜት (በተለምዶ አነጋገር በህሊና ዳኝነት) የሚገዛ ማንኛውም ሰው በራሱ ላይ እንዲደርስ የማይፈልገውን ነገር በሌሎች ላይ አያደርስም፤ ሌሎች በሌሎች ላይ ጥቃት ሲያደርሱም አይቶ ዝም አይልም። ህሊናችን ኢፍትሃዊ ህጎችን ይፀየፋል

3.   ኢትዮጵያ፣ ህግና ፍትህ

justice 02
ኢትዮጵያ አገራችን የብዙ ወለፈንዲዎች (Paradoxes) አገር ናት። ከእነዚህ ወለፈንዲዎችም አንዱ ፍትህና ህግ በኢትዮጵያ ያላቸው ቦታ ነው። የኢትዮጵያ ሕዝብ በአንድ በኩል ህግ አክባሪ ነው፤ በሌላ በኩል ደግሞ ፍትህ የተነፈገ ሕዝብ ነው። እንዴት ፍትህ የተነፈገ ሕዝብ ህግ አክባሪ ይሆናል? ይህ ለመረዳት የሚቸግር ወለፈንዲ ነው
ለኢትዮጵያዊያን “በህግ አምላክ” ትልቅ ትርጉም ያለው ሀረግ ነው። ድሮ (ከወያኔ በፊት) ተበዳይ በዳያን አግኝቶ “በህግ አምላክ ቁም ብዬሃለሁ” ካለው ፓሊስ እንኳን ባይኖር ምስክር ወይም ገላጋይ እስኪመጣ ድረስ “ቁም” የተባለው ሰው ባለበት ይቆም ነበር። “የህግ አምላክን” ማክበር አምላክን ከማክበር ጋር እኩል ነበር። “የህግ አምላክ” መኖሩ ተገዢዎች በህጉ ተፈፃሚነት ላይ እምነት እንዲኖራቸው አድርጓል። ገዢዎችም ቢሆኑ ለዳኝነት ክብር እንዲሰጡ “የህግ አምላክ” በተወሰነ መጠንም ቢሆን አገልግሏል። ከፍትህ አንፃር የቀደሙት ሥርዓቶች ብዙ ጉድለቶች የነበሩባቸው ቢሆንም ችሎትን እንደ አሁን መዘባበቻ ያላደረጉበት አንዱ ምክንያት ፍትህን ከመለኮታዊ ሥልጣን ጋር ማያያዛቸው ነው። ይህ እውነታ የኢትዮጵያ ሕዝብ በፍትህ ሥርዓቱ ላይ ከፍተኛ እምነት እንዲያድርበት አድርጓል። አንድ ባለጉዳይ በአንድ ዳኛ ቢፈረድበት “የህግ አምላክ” ስላለ በሚቀጥለው እርከን ላይ ያለው ዳኛ ዘንድ ፍትህን አገኛለሁ በሚል ለአቤቱታ ይጓዛል፤ እዚያም ባይሳካለት ወደሚቀጥለው እርከን አቤት ይላል። እንዲህ እያለ አንዳንዱ እንጉሥ ችሎት ዘንድ ይቀርባል። የኢትዮጵያ ሕዝብ እንዲህ ፍትህ እየተነፈገውም “በህግ አምላክ” ላይ ተስፋ የማይቆርጥ ህገ አክባሪ ሕዝብ ነው። የኢትዮጵያን ሕዝብ ህግ አክባሪነት በችሎቶች ደጃፎች ብቻ ሳይሆን በዘወትር ሕይወቱም የሚታይ ነው። በከተሞች ውስጥ የወርቅ ቤቶችን ግድዳዎች ተደግፈው የሚያድሩ ድሆች ያሉት ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ሳይሆን አይቀርም። ጠመንጃ ይዞ “አገሬ መግቢያ መሳፈሪያ ሙሉልኝ” ወይም “ራበኝ፣ ለምሳ ተዘከሩኝ” የሚል ወታደር የነበረው ኢትዮጵያ ውስጥ ነው። ይህ ሁሉ መልካም ባህል አሁን በዘመነ ወያኔ በዓይኖቻችን ሥር እየተንኮታኮተ ነው። ይህ በቀላሉ የማይገነባ ክቡር ባህል እያጣን ነው።
አሳዛኙ ነገር በዚህ ህግ አክባሪ ሕዝብ ጫንቃ ላይ የተጫኑ ገዢዎች የሕዝቡን ህግ አክባሪነት በሚመጥን መጠን ህግን አክብረው የሚያስከብሩ አለመሆናቸው ነው። በህግ አጠባበቅ ረገድ ኢትዮጵያ እየተጓዘችበት ያለው የቁልቁለት ጉዞ አስፈሪ ነው። ኢትዮጵያ ከአንድ ገዢ መዳፍ ወደ ሌላው በተወረወረች ቁጥር ፍትህ ከቀድሞው በባሰ እየተረገጠች መጥታለች። የቅርቡን ዓመታት እንኳን በምሳሌነት ብንጠቅስ የአጼ ኃይለሥላሴ አገዛዝ ኢፍትሃዊነት ያስመረራቸው ወገኖች ሥርዓቱን ታገሉት፤ በትግሉ አሸንፎ የወጣው ግን ከቀድሞው የባሰው ደርግ ሆነ። የደርግ ሥርዓት ያስመረራቸው ታገሉት፤ በትግሉ አሸንፎ  የወጣው ግን ከደርግ የባሰው ወያኔ ሆነ።  ይህ የቁልቁለት ጉዞ ካልተሰበረ  አደጋው በዚሁ ዓይነት ሊቀጥል ይችላል።
ሌላው አሳሳቢ ጉዳይ የፍትህ እሳቤያችን ራሱ እያሽቆለቆለ መምጣቱ ነው። ቀድሞ፣ ከላይ እንደተገለፀው፣ ፍትህ መለኮታዊ ፀጋ ተደርጋ ትወሰድ ነበር፤ መቀመጫዋም ከአማልክት ጎን ነበር። “በህግ አምላክ” ሲባልም የአማልክት መቀመጫ ነው ተብሎ ወደሚታሰበው ሰማይ እየታየ ነበር። ከማርክሳዊ ሌሊናዊ ርዕዮተዓለም መምጣት ጋር ፍትህ ከሰማየ ሰማያት ወርዳ መሬት ላይ ተፈጠፈጠች። ፍትህ ሰዎችን ሁሉ በእኩል ማየቷ ቀረናመደባዊ ሆነች። በዚህ አዲሱ ዕይታ መሠረት የላብአደሩ ፍትህ እና የቡርዣው ፍትህ ለየቅል ብቻ ሳይሆን ተቃራኒ ሆነው ተገኙ። ለአንዱ ፍትሃዊ የሆነ ነገር ሁሉ ለሌላው ኢፍትሃዊ ነው። ከወያኔ መምጣት ጋር ደግሞ ፍትህ መሬት ላይ መንደባለሏም በዝቶ ጉድጓድ ተቆፍሮ እጉድጓጉ ውስጥ ተጣለች። በአዲሱ ወያኔ አመጣሽ ዕይታ እያንዳንዱ ዘር (ብሔር፣ ብሔረሰብ፣ ሕዝብ) በየራሱ ጉድጓድ ውስጥ የቀበራት የራሱ ፍትህ አለው። የትግሬ ፍትህ እና የአማራው ፍትህ አይተዋወቁም። አሮሞው፣ አደሬው፣ ሶማሌው፣ አፋሩ፣ ሲዳማው፣ ጉራጌው …. እያንዳንዳቸው የየራሳቸው ፍትህ አላቸው። አንዱ ዘንድ ፍትሃዊ የሆነ ሌላው ጋር ፍትሃዊም ሊሆንም ላይሆንም ይችላል። እንደመደብ ትንተናው እርግጠኛ ሆኖ መናገር አይቻልም። በዚህም ምክንያት ነው ማኅበረሰባችን ብዥታ በበዛበት ሁኔታ ላይ የሚገኘው። ለምሳሌ አንዱ ዘር በገነባው ሀውልት በሀሴት ሲጨፍር፤ ሌላው በንዴት ይበግናል፤ ሶስተኛው ደግሞ ምንም ስሜት አይሰጠውም። በአንድ ቋንቋ እየተነጋገርን መሰማማት የቸገረንም በዚህ የፍትህ እሳቤ መዛባት ጭምርም ነው።

4.   ምልከታ ወደፊት

ይህ ሁሉ የሚያመለክተው (1) አገራችን የምትገኝበት አሳሳቢ ደረጃ፣ እና (2) እኛ (ማለትም በዚህ ዘመን ያለነው ኢትዮጵያዊያን) ላይ የወደቀውን የኃላፊነት ክብደት ነው። ዜጎች ፍትህ የማግኘት ተስፋቸው ሲሟጠጥ በሚኖሩበት ማኅበረሰብ ላይ የነበራቸው ተስፋ ይጨልማል። “ታግለን ሥርዓቱን ወደ መልካምነት ልንቀይረው እንችላለን” የሚለው እምነት ካልዳበረ ለሀገር፣ ለወገን፣ ለመጪው ትውልድ መጨነቅ ያቆሙና እያንዳንዱ ሰው “እኔ ምን አቀበጠኝ” እያለ  ሁሉም ጭቆናን ችለው ለመኖር ሊመርጡ ይችላሉ። ይህ እንዳይመጣ መወሰን ያለብን በየግላችን ነው።
ይህን ወሳኝ የግል ውሳኔ የሰጠን ሰዎች ደግሞ መሰባሰብና ተግባሮቻችን ማቀናጀት ይኖርብናል። እንዲህ ካደረግን በአገራችን የተንሰራፋውን ኢፍትሃዊነትን መዋጋት የሚቻለው በፓለቲካ ሥርዓቱ ላይ ለውጥ ሲመጣ መሆኑን ለማመን ጊዜ አይወስድብንም።  ከዚህ ቀጥሎ  የሚመጣው አቢይ ጥያቄ “ለውጥ እንዴት?” የሚለው ይሆናል።  ከዚያ በፊት ግን በለውጡ አስፈላጊነት እና ይህ ለውጥ ካልመጣ  ሰዎች ሆነን የመቀጠላችን ጉዳይ እንኳን አጠራጣሪ መሆኑ በትክክል ልንረዳ ይገባል።  ይህ ቁርጠኝነት ሥር እንዲሰድ ስለ ፍትህ ያለን ግንዛቤ በየጊዜው መዳበር ይኖርበታል።
በፍትህ እጦት ሳቢያ በየእስር ቤቶች እየተሰቃዩ ላሉ ወንድሞቻችንና እህቶቻችን፤ ከማሳዎቻቸው ተፈናቅለው ለተበተኑ ወገኖቻችን፤ አደገኛ የበረሃና የባህር ጉዞ በማድረግ ለተሰደዱ ወገኖቻችን፣ ለራሳችን እና ለመጪው ትውልድ ልንደርስለት ይገባል። ፍትህን ከተቀበረችበት ጉድጓድ በቶሎ ካላወጣናት አገር አይኖረንም፤ እኛም ሰዎች ሆነን አንቀጥልም። በዚህ የኃላፊነት እና የአጣዳፊነት ስሜት ነው የፍትህ ግንዛቤዓችን መገንባት የሚኖርበት።

    ፀሐፊውን በ tkersmo@gmail.com ማግኘት ይቻላል

    የሙስሊሙን ትግል ለማኮላሸት የታቀደ ስብሰባ በሽመልስ ከማል ቢሮ ተካሄደ።

    June 27/2014
    ምንሊክ ሳልሳዊ
    የቀድሞዋ አልቁድስ አዘጋጆችም ከአቶ ሽመልስ ከማል ጋር መፈራረማቸውን ለማወቅ ተችልዋል፡፡
    የሙስሊሙን ትግል አስመልክቶ በኮሚኒኬሽን ሚኒስትሩ አቶ ሽመልስ ከማል ቢሮ በትላንትናው እለት ደህንነቶች የመጅሊስ ሰዎች : የሱመያ ጋዜጣ አዘጋጆች የተመለመሉ ወጣቶች ስብሰባ አድረገው እንደነበር ምንጮቻችን ለቢቢኤን ገለጹ፡፡ በዛሬው የጁምአ ተቃውሞ ለማሰር አቅደውት የነበረውም ዝናብ በመጣሉ ምክኒያት እንደተኮላሸባቸው ታወቀ፡፡
    በትናንትናው እለት ምሽት በአቶ ሽመልስ ከማል ቢሮ ውስጥ በነበረው ስብሰባ በሙስሊሙ ማህበረሰብ ትግል ላይ ውዥንበር ለመፍጠር ታቅዶ በቀድሞው አልቁድስ ጋዜጣ አዘጋጆች የተዘጋጀችው በድር ጋዜጣ ተብሎ ታትሞ አጀንዳው ስለታወቀ ስምዋን የቀየረችውን አሁን ሱመያ በሚል መታተሙዋ ተገልጸዋል፡፡ የሙስሊሙ ትግል ደጋፊ በመምሰል ክፍተት ለመፍጠር ከመንግስት በጀት የተመደበላቸው የቀድሞዋ አልቁድስ አዘጋጆችም ከአቶ ሽመልስ ከማል ጋር መፈራረማቸውን ለማወቅ ተችልዋል፡፡
    በአዲስ አበባ ያለው ሙስሊም ማህበረሰብ በድር ጋዜጣም ሆነ ሱመያ ጋዜጣ ትግሉ ለማዳከም የተዘጋጀ መሆኑን ስላወቀ ተቀባይነት እንደሌለው የተረዱት የመንግስት ባለስልጣናትና አዘጋጆቹ ጋዜጣዋን ወደ ክፍለ ሀገራት ለመበተን እንዳቀዱም በዚሁ ስብሰባ ላይ አውሰተዋል፡፡ ጋዜጣዋን ክፍለ ሀገር ሂዶ ለማከፋፈል ለሚፈልጉ ወጣቶችም ስልጠና እንደሚሰጣቸውና ዳጎስ ያለ አበልም እንደሚተሳብላቸው በዚሁ ስብሰባ ላይ ተግልጽዋል
    ተቃውሞው በምንም ተአምር መቀጠል የለበትም ለዚህ ሁላችንም ርብርብ ማድረግ አለብን ሲሉ አሳስበዋል አቶ ሽመልስ ከማል፡፡ ስልጠና ከወሰዱ በሁላ ጥለው የወጡት ወጣቶች እንደገና ተጠርተው ሰዎችን በማሳሰር በደህንነት መሰማራት እንዳለባቸውም ተገልጽዋል፡፡

    ቢቢኤን የናንተው ድምፅ ሌሎችንም የዚህን ስብሰባ ተጨማሪ መረጃ ለመስማት ቀጣዩን ሊንክ ይክፈቱ -http://goo.gl/VwQJzy
    http://goo.gl/VwQJzy

    የአማራን ህዝብ በማጥፋት ወያኔና ተቃዋሚው በጋራ እየሰሩ ነው

    June28/2014



    አቶ አዲሱ አበበ አርብ ጁን 20 2014 በአሜሪካ ድምጽ ራዲዮ ያስተላለፉትን ቃለ መጠይቅ ቃል በቃል በጽሁፍ ገልብጨ ከአውዲዮው ጋር እንድልክላችሁ ያነሳሳኝ ሆን ተብሎ በአማራው ህዝብ ላይ የሚፈጸመው ዘር ማጥፋት፣ ድርጊቱን ቀጥታ በሚፈጽሙት አካላት ብቻ ሳይሆን የወያኔ ትግሬዎችን የጎሳ ፖለቲካ እንቃወማለን የሚሉ ሳይቀሩ ሆን ብለው የተሰሳተ መረጃ በመስጠት በአማራው ህዝብ ላይ የክህደት ስራ እየሰሩ ለመሆኑ ለመጠቆም እና አንባቢም ቃለ መጠየቁን በማንበብም ሆነ ቃለ መጠየቁን ከተለያዩ ድህረገጾች በመስማት ያራሱን ፍርድ እንዲሰጥ ነው። በአማራው ህዝብ ላይ የሚፈጸመው የዘር ማጥፋትና የዘር ማጽዳት ዘመቻ በወያኔና የሱ ተናካሽ ውሾች በሆኑ የብሄር ድርጅቶች ብቻ ሳይሆን፤ በኢትዮጵያ ስም የተደራጁ ፓርቲዎች፣ ድርጅቶች፣ ሬዲዮ ጣቢያዎች፣ ድህረገጾች ወዘተ ጭምር በጋራ የሚተባበሩበት ለመሆኑ የሚጠይቅ አይምሮ ያለው ያስተውለው።
    ተፈናቃዮች አማራ ናችሁ ተብለን ከወለጋ ተፈናቀልን እያሉ፤ አቶ አዲሱ አበበ አማረኛ ተናጋሪዎች ተፈናቀሉ ይላሉ። በአማረኛ ተናጋሪነት ከሆነ ከወለጋ የተጠየቁ አፈናቃዮችኮ በአማረኛ ነው ከአቶ አዲሱ አበበ ጋር የሚነጋገሩት፤ አቶ አዲሱ አበበ የአሜሪካ ድምጽ ራዲዮ ጋዜጠኛ ስለሆኑ፣ እንዲሁም የአሜሪካ መንግስት ከምንም ጊዜ ይበልጥና ከማንም በላይ የወያኔ ትግሬዎችን መንግስት በገንዘብና በሰው ሀይል ስለሚረዳ አቶ አዲስ አበበ ከቀጣሪያቸው አቋም ውጭ ሊሆኑ አይችሉም ብንል፡ ከአማራው ኪስ በሚወጣ መዋጮ የሚንቀሳቀሱ እንደ ኢሳትና ሌሎችም በየሀገሩና በየከተማው የተቋቋሙ ሬዲዮ ጣቢያዎችና ድህረገጾች፣ የአማራው ህዝብ አማራ በመሆናችን ብቻ ተነጥለን፤ ሀብትና ንብረታችን ተዘርፎ፣ ተደብድበን፣ ከፊሎችም ተገለው ከሞት አምልጠን እዚህ ደረሰን ሲሉ፣ ”ከባለቤቱ ይበልጥ ያወቀ ቡዳ ነው” እንደሚባለው፤ አማራ ስለሆኑ አይደለም፤ አማረኛ ተናጋሪ ስለሆኑ ነው ብለው በአማራው ህዝብ ላይ አማራ በመሆኑ ብቻ ወንጀል እንደላልተፈጸመበት አድርገው የተዛባ ማስተባበያ ለህዝብ ጀሮ ያቀርበዋል።  ከዚህ ተጨማሪ ስለዚህ መፈናቀል የዘገቡ ኢትዮጽያዊ የሚባሉ ድህረገጾችና ሬዲዮ ጣቢያዎች ብዙም ባይሆኑ፣ ለይስሙላ የዘገቡም ዘግበውም በነጋታው ከድህረገጻቸው ያነሱ ድህረገጾችንም ታዝቤአለሁ።
    ብአዴን ማን ነው ሲሉ አቶ ገብረመድህን አርአያ ሰፋ ያለ መረጃ ሰጠውናል። ብአድኖች ከመጀመሪያው ”አማራ ህዝብ ጠላት አይደለም” ያሉትን የገደሉና ከዚያም በአማራው ህዝብ ላይ በየክፈለሀገሩ እየዞሩ የአማራውን ህዝብ ነጥለው በመሪነት ያስገደሉና ያሰደዱ ለመሆኑ መረጃዎች አሉ። አሁንም ከዚህ ቃለ መጠየቅ እንደምንረዳው የኦሮሞና የአማራው ክልል ባለስልጣኖች ይሄን ያህል አፈናቅሉ፤ ይሄን ያህል ግደሉ፤ ይሄን ያህል ደግሞ ለፖለቲካ መልሱ እየተበሉ በእቅድ የሚፈጽሙት የዘር ማጥፋትና የዘር ማጽዳት ወንጀል መሆኑን ቃለ መጠይቁ ይጠቁማል።
    በአቶ አዲሱ አበበና በሬዲዮ ጣቢያቸው ላይ እንዲያውም ስለመፈናቀሉ በመዘገባቸው ባለውለታ እንጂ ቅሬታ የለኝም። ሌሎች በተቃዋሚነት ተሰልፈናል የሚሉ ግን አሁንም ቢሆን ለይስሙላ የሚጠይቁት ”ወደ ቀያቼው እንዲመለሱ” የሚል ነው። አንድ ሰው አማራ በመሆኑ ብቻ ሀብት ንብረቱ ተዘርፎ፤ አቅመ ደካማ የሆኑ ሚስት ልጆቹ፣ በእድሜ የገፉ እናት አባት ተገለው፤ ቤቱ ተቃጥሎ ”ወደ ቀያቸው ይመሰለሱ” የሚለው ፍርድ በአማራው ህዝብ ላይ ለሚፈጸመው የዘር ማጥፋትና ማጥዳት ወንጀል ተባባሪነት ካልሆነ በቀር ትክክለኛ ፍርድ አለመሆኑን ህሌናችሁ ፍርድ ይስጥ።
    አንድ ሰው አማራ በመሆኑ ብቻ ሀብት ንብረቱን ተቀምቶ፣ የተገደለው ተገሎ የሚፈናቀል ከሆነ፤ አንድ ከአማራ ወላጆች የተወለደ ኢትዮጵያዊ መብቱ ተከብሮ ለመኖሩ የጊዜና የቦታ አለመገጣጠም ካልሆነ በቀር ዛሬ ወለጋ በሚኖሩ አማሮች ላይ የደረሰው መገደልና መፈናቀል በሱ ወይም በሷ ላይ እንደማይደርስ ምንም አይነት መተማመኛ የለም። ብሄረተኝነት የግለሰቡን ብሄር አንጂ የግለሰቡን ሰብአዊ ባህሪ አይቶ ይህ ደግ ነው ተወው፣ ያ ክፉ ነው በለው አይልም። ስለዚህ ማንም ከአማራ ወላጆች የተወለደ ሁሉ በወያኔ ትግሬዎችና የነሱም ተናካሽ ውሾች በሆኑ የብሄር ድርጅቶቹ አንዲሁም ከሀገር ውጭ መረጃ በማጣመም፣ በአማራው ህዝብ ላይ የሚፈጸመውን ወንጀል በማስተባበልና ማእቀብ በማድረግ ከወያኔ ትግሬዎች ጋር በአጋርነት የተሰለፉ ሬዲዮ ጣቢያዎችና ድህረገጾች የአማራን ህዝብ በማጥፋት ወንጀል እየተባበሩ ለመሆኑ ከኔ ጽሁፍ ይልቅ ትንሽ ማሰብ የሚችል ጭንቅላት ያለው ሰሞኑን በወለጋ በአማራው ህዝብ ላይ በተፈጸመው ግድያና መፈናቀል ድህረገጾችን አይቶ፣ ሬዲዮ ጣቢያዎችን አዳምጦ ይፍረድ።
    ከግለሰብ የተወረወረ ትዝብት
    ቃለ መጠይቁን ለማዳመጽ ይሄንን ይጫኑ፣ በጽሁፍ ለማንበብ ከታች ያለውን ይመልከቱ
    የአሜሪካ ራዲዮ ጣቢያ ከተፈናቃዮች ጋር ያደረገው ቃለ መጠይቅ፣
    ጁን 20 2014
    ከወለጋ በተለይም ከግንቢና ከቄለም ከግንፍሌ ወረዳ ተባረርን ደግሞ ቤት ንብረታችን ተቃጠለ ያሉ የአማረኛ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያን በአሁኑ ወቅት ባህር ዳር እንደሚገኙ ይናገራሉ። ቁጥራቸው እስከ 3000 ይደርሳል የሚሉ እነዚህ ተፈናቃዮች የአማራው ክልል አስተዳደር መፍትሔ እንዲፈልግላቸው በመጠባበቅ ላይ መሆኑንም ተመልክቷል። የኦሮሚያ ክልል የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጽህፈት ቤት በበኩሉ የተፈናቀሉ ሰዎች ቁጥር ከ100 በታች ነው ይላል። አዲሱ አበበ ተፈናቃዮችንና ጉዳዩ የሚመለከታቸውን የመንግስት አካላት አነጋግሮ ተከታዩን አጠናቅሯል።
    አቶ ጋሻው ፈቃደ የተባሉና ሌላ አንድ ስሜ አንዳይገለጽ ያሉ ተፈናቃይ ጨምረን አወያየን፣ ስማቸው እንዲገለጽ ያልፈለጉት የምእራብ ወለጋ ዞን ተፈናቃዩ ከወር በላይ ሆኖናል ብለው ይጀምራሉ።
    አሁን 1 ወር ከምናምን እየሆነው ነው ምክንያቱ የድሮ ታሪክ ነው የሚያነሱት፤ ሚኒሊክ እንደዚህ አድርጎን፣ እንዲህ አድርጎን ነው የሚሉት፤ በጣም አሳደዱነ፤ የከተማው ህዝብ እንዳለ ወጥቷል እንደገና ባለስልጣኖች ደግሞ አሉበት፡ ፖሊሶች እነዚህ አድማ በታኝ የሚባሉት አብረው ነው ሲዘርፉና ሲደበድቡን የዋሉ ማለት ነው። አማራ የተባለውን።
    እኮ ምክንያቱ ምንድነው አሉዋችሁ፤ በትክክል?
    ምክንያቱ የድሮ ታሪክ ነው፣ እነሱ እንገነጠላለን ምናምን ነው የሚሉት፤ እራሳችን ነጻ እናወጣለን፤ አማራን አንፈልግም፣ አማራ ይውጣልነ ነው። እና ህይወታችን የተረፈው በስንት ነገር ነው። ኮርኒስ እየገባን ጫካ እየገባን በስንት ነገር ነው። ብዙ ሰው ሞቷል።
    ስንት ጊዜ ሆኖት እርሶ ወለጋ ሲኖሩ?
    እኔ 11 ዓመቴ ነው፣ ወደ 5 ቤተሰብ አስተዳድራለሁ፣ ሱቅም ነበረኝ፣ ጣቃ አከፋፍል ነበር፣ ጣቃውን እንዳለ ዘርፈውኛል።
    ስንት ሰው ከዚያ ተሰደደ? ከወለጋ ከግንቢ በተለይ? እርሶ ካሉበት
    ቢያንስ ከ8000 የማያንስ ህዝብ ነው።
    ባህርዳር የአማራው አስተዳደር አለ እዚያ ደግሞ ሄዳችሁ አላመለከታችሁም? ምን አሉዋችሁ?
    ወደ ቤታችሁ ተመለሱ ነው የተባልነው፣
    ወዴት ወደቤታችሁ?
    ወደነበራችሁበት ተመለሱና እናረጋጋለን ምናምን ነው ያሉን፤ እነሱ ደግሞ አሁን እራሱ አልተውም
    ሌላው አቶ ጋሻው ፈቃደ ይባላል፤ የመፈናቀላችንን ምክንያት በውል አልተረዳነውም፤ ይሉና ይቀጥላሉ።
    ምክንያቱ ምን  እንደሆነ እኛ ያወቅነው ጉዳይ የለም፣ ለኛ በኳስ ነው ምናምን ነው የሚሉት
    ኳስ ማለት
    በባህርዳር ከተማ ላይ ኳስ ጨዋታ ተካሂዶ ነበር፣ የአማራ ክልል ህዝብ ኦሮሞዎችን ጋላ! ጋላ! አሉን፣ እና የኛ ሰው ደግሞ የተደበደበ ሰው አለ። እያሉ ነው ለኛ ሲናገሩት የነበረው።
    እናንተ እዚያ አልሄዳችሁም? ለምን እናንተን ውጡ አሉዋችሁ ብዬ ነው?
    እኛም ግራ የገባን እኮ እሱ ነው፣ ከዚያ ወደዚያ ሰው ተይዞ መመከር እያለበት ለምን በስመ አማራ ለምን እኛ ይሄን ያክል መበደል አለብን የሚለውንኮ አቤቱታ ስናቀርብ አቤቱታችንን እዚህ ደግሞ አልቀበልም ያሉ።
    ስንት ሰው ነው በጠቅላላ የተፈናቀለ ወይም እንዲወጣ የተደረገው?
    ቢያንስ ከግንቢ ከተማ ብቻ አንድ 3000 ሰው ይሆናል። ያልወጣም እዚያ የቀረም ህዝብ አለ፤ በቃ ህይወታችን እስከሚያልፍ መጠበቅ ነው እንጂ ያለብን እንዴት እናደርጋለን?
    ሌላ ሰው ሳናግር እንዲሁ ከ2000 ሰው በላይ ነው የሚሉኝ፤ ይሄን ያህል ሰው ሲፈናቀል እዚያ አካባቢ አስተዳደሩ፤ የፖሊስ ጣቢያው፤ የመንግስት ባለስልጣናት የሉም? ወይም እናንተ ሄዳችሁ አቤት ለማለት አልሞከራችሁም? አቶ ጋሻው።
    ሄደን አቤት ብለናል፤ ግን ሊቀበሉን አልቻሉም፣ ሄደንም አመልክተናል አቤቱታችንን እያቀረብን ነው እኛ ያለነው አሁን ለነሱ
    ለማን ነው አቅርበን እንቢ አሉን የሚሉኝ?
    ርእሰ መስተዳደር ሄደን ነበር እኛ፣ ርእሰ መስተዳደሩ
    ለማን ነው አቅርበን ነበር የሚሉኝ፣ ለባህርዳር?
    አዎ ባህርዳር ከተማ ላይ፣
    እና ምን ተባል…?
    ከ5 ሰዓት እስከ 8 ሰዓት ተቀጠርን፣ 8 ሰዓት ደግሞ ውጡ አሉን።
    ሰው ምረጡ ተብሎ ሰው መርጣችሁ ከላካችሁ እንዴት እንደገና ውጡ ይላሉ ብዬ ነው። ማ ቢሮ ነበር ልትገቡ የፈለጋችሁ?
    እዚያ እርሰ መስተዳደሩ ላይ፤ በቃ አስተዳደሩ፤ እሱን ፈልገን ነበር እኛ ርእሰ መስተዳደሩን
    ፕሬዜዳንቱ ቢሮ ነው ወይስ ምክትላችው ወይስ ጸሀፊ ጋ ወይም
    አዎ፣ ርእሰ መስተዳደሩ ቢሮ ነው እንጂ
    ለመሆኑ የአካባቢው ባለስልጣናት ምን አሉ? እናንተስ አቤት ብላችሗል? ላልሁት ጥያቄ የጸጽታ ሀላፊ ናቸው፤ እርሳቸው ሁሉንም ያውቃሉ፤ በማለት የአንድ ሰው ስምና ቁጥር ሰጠውኝ ደወልሁ
    አቤት፤ አቤት
    እንደምን ዋሉ? አቶ አወቀ
    አቤት፤ ማን ልበል?
    አዲሱ እባላለሁ፤ ከዋሽንግቶን ነው የምደውለው፤ ከአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ
    ይሄን ስልክ አላውቀውም፤ ከየት ነው?
    እንዳልሁት ከአሜሪካ ነው የምደውለው፤ ከአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ፣ ከዋሽንግቶን፣ ከቪኦኤ
    ከዚያ አካባቢ ተፈናቀልን የሚሉ ሰዎች ኢንተርቪው አድርጌ ነበር፤ እና እርሶ የሚያውቁትን ነገር ቢነግሩኝ?
    ከየት?
    ከቄለም አካባቢ፤ ከግንቢም አማረኛ ተናጋሪዎች
    የት ሄድን? ወዴት ተፈናቀልን አሉ?
    ተባረው ባህር ዳር ጎጃም ውስጥ ነው  ያሉት፤ ሰፈራ ጣቢያ አግኝተው?
    ማን ነው ያባረረው?
    እርሶ የሚያውቁትን እንዲነግሩኝ ነው አቶ አወቀ፤ አሁን የምደውለው ነዋሪዎችም ባለስልጣናት ናቸው ያባረሩን ይላሉ፤ ሁለቱንም
    እነማን ናቸው እነሱ መጀመሪያ?
    የሰዎቹን ስማቸውን ነው የሚፈልጉት?
    አዎ
    በሺዎች የሚቆጠሩ ናቸው፤ ነገረ ግን ጥያቄዬ ከቄለምና ከግንቢ አካባቢ እንዲባረሩ ሆኖዋል ወይ? እንዲወጡ ተደርጓል ወይ? የጸጽታ ክፍሉ የሚያውቀው ነገር አለ ወይ? እምሎት።
    እኔ የጸጽታ ክፍል አይደለሁምና ከህዝብ ነኝ፤ እና ማን ነው ያለ? መጀመሪያ ንገረኝ፣
    እርሶ ……
    ከዚያ በሗላ ነው የማውቀውን የምስጥህ እንጂ የሆነም ያልሆነም ነገር ልሰጥህ አልችልም ማነው ያለህ?
    አቶ አወቀ የጸጽታ ሀላፊ ናቸው ተብሎ ነው ስልኩ የተሰጠኝ ልክ አይደለም?
    ውሸት ነው፤ የጸጽታ ሀላፊ አይደለሁም። እኔ ሌላ ስራ ነው ይዤ ያለሁ፤ የጸጽታ ሀላፊውን ልትጠይቅ ትችላለህ።
    እርሶ በምን ውስጥ ነው ያሉት? ስለዚህ ጉዳይስ የሚያውቁት ጉዳይ የለም።
    እኔ የድርጅት ጽህፈት ቤት ነኝ
    የተባረሩ አማረኛ ተናጋሪዎች ስለመኖራቸው አያውቁም?
    የተባረሩ የሉም። ያባረረም የለም።
    የእርሶ ቢሮ ሀላፊነቱ ምንድን ነው? አቶ አወቀ፤ የድርጅት ጉዳይ ሲሉ ምንድን ነው የምትሰሩት?
    የኦህዲድ የድርጅት ጉዳይ ነው
    እና የኦህዲድ ጽህፈት ቤት ይሄን አያውቅም?
    የተባረረ ሰው የለም እያልሁህ እኮ ነው፣ በራሳቸው ፍላጎት ሊሄዱ ይችላሉ እንጂ ያባረረ ሰው የልም፡ እያልሁህ እኮ ነው፤ ቄለብ ወለጋ ስትል ከቄለብ ወለጋ የተባረረ ሰው የለም። እንደዞኑ የምናውቀው ነገር የለንም።
    ከትናት በስቲያ ማክሰኞ ወደ ኦሮሚያ የመንግስት ኮሚኒኬሽንስ ጉዳዮች ቢሮ ደወልሁና የቢሮ ሀላፊዋን ወይዘሮ ራዲያ ኢሳን አገኘሁ። ምንም የምናውቀው ነገር የለም አሉኝ። ዛሬስ ያውቁ እንደሆን ብዬ እንደገና ወደ ወይዘሮ ራዲያ ቢሮ ደወልሁ፣ በቁጥሩ ላይ ነው ያልተስማማነው እንጂ ማወቁን ያውቃሉ።
    ሁለት ሺ ሶስት ሺ ተፈናቀለ የምትለው አይደለም
    ከነሱ የሰማሁትን ነው
    መቶ የማይሞሉ ሰዎች ናቸው
    ከሁለት ቦታ ነው የሰማሁት ከግንቢና ከቄለም
    አዎ ቄለም ወለጋ አሼ ቀበሌ ነች አይደለ፤
    አዎ አሼ ቀበሌ ነው ያሉኝ
    የሆነ ወንጀል ተፈጽሞ ነበረ
    ማን ነው የፈጸመው?
    እንድ ሰው ሞቶ ነበር፤ የኦሮሞ ብሄር ተወላጅ የሆነ ቀጥሎ ደግሞ ሁለት ሰዎች ባልታወቁ ሰዎች ተገለዋል፤ ከፍርሀት ተነስተው ነው እነዚህ ሰዎች ክልል ሶስት የሄዱት፤ መንግስት ..
    ከፍርሃት ማልት?
    መንግስት፤ ፖሊስ፤ እዚያ ያለው አስተዳደር የሚባለው ስህተት ነው። አሁን እንዲያውም ወደ ቄያቸው እንዲመለሱ እየተደረገ ነው ያለው
    ቁጥሩ አይደለም ወሳኙ፤ ነገር ግን ሰዎቹ ሁለት ሺ ሶስት ሺ ይላሉ፤ እርሶ 100 አይሞላም ይላሉ። ግን በፍርሀት ነው የወጡት የሚሉኝ ለምን ነው የፈሩት?
    ነገርሁህ እኮ፤ በዚያ ቀበሌ አካባቢ ወንጀሎች ተፈጽመዋል፡ እንደነገርሁህ ወንጀሉን ይፈጽማሉ ተብሎ የሚገመተው ያው እየተፈለገ ነው።
    ሁለት ሰው ወይም ሶስት ሰው ወንጀል ተፈጸመበት ሞተ ብለውኝል፤ መቶ የማይሞሉ ሰዎች ደግሞ ፈርተው ወጡና፣ እነዚህ ሁሉ የሚፈሩበት ምክንያት በመጠርጠር ስማቸው ተነስቶ ነው? ነገሩ ትንሽ የሚየያዝ አልሆነልኝም።
    የተጠረጠሩ አይደለም። እኔ እስከማውቀው ድረስ ፍርሀት በቃ፤ አሁን ነገርሁህ እኮ ወደ ቀያቸው እንዲመለሱ አስተዳደሩም እየሰራ ነው፤ ወደ ንብረታቸው እንዲመለሱ ማድረግ ነው።
    እነዚህ ከመቶ የማይሞሉ እርሶ እንዳሉት ሲሰደዱ ወይም መፈናቀላቸውን መቼ ነው የእርሶ ቢሮ ያወቀው?
    እንደ መንግስት ይሔን ሁለቱም የክልሉ መንግስታት ያውቁታል፤ የምናስተዳድረው ያው አንድ ሀገር ነው፤ ያው ክልሎች እራሳቸውን ያስተዳድሩ እንጂ መናበቡ ነገር አለ።
    ይሄ ከሆነ መናበቡ አለ፣ ትናት ስደውል ምንም የምናውቀው የለም ብለውኛል። እና መቼ ነው ያወቁት? የእርሶ ቢሮ ያወቀው
    አሁንም አሁንም አንተ የምትለው ከ2000 እስከ 3000 የምትለው አንተ ያነሳህልኝ ቁጥርና እኔ የማውቀው ቁጥር በጣም ስለሚለያይ
    ቁጥሩ አይደለም ወሳኙ፤ አንድም ሰው ቢሆን ብዙ አመት ከኖረበት መፈናቀሉ ሊያሳስበን ይገባል ማለቴ ነው። ቁጥሩ አይደለም ወሳኙ፤ አሁን ደግሞ ፌደራል እዚያ ሄዶ እንዲያረጋጋ ተብሏል ተባለ፤ ነገር ግን ፌደራል አልሄደም። እንዲያውም እዚያ ያሉት ሰዎች እንዲወጡ እየተደረገ ነው የሚሉኝ ሰዎቹ።
    እንግዲህ እኔ አሁን ያለኝን ትክክለኛ መረጃ ነው እየሰጠሁህ ያለሁት
    እሺ
    መንግስት እዚያ ያለው አስተዳደር የማረጋጋቱ ስራ ሌሎችም እንዳይፈናቀሉ ማለት የወጡትም ደግሞ እንዲመለሱ አማራ ክልል መንግስት ጋርም እየተናበቡ እየተሰራ ነው።
    በጣም አመሰግናለሁ ሰላም ይዋሉ
    እሺ
    ለመሆኑ የአማራው ክልል ርእሰ መስተዳድር ምን እያደረገ ነው? ወደ አማራው ብሄራዊ ክልል መንግስታዊ ጽህፈት ቤት ደውዬ ፕሬዜዳንቱ የሉም ስለተባለ ወደ ሌላው ከፍተኛ ባለስልጣን ወደ አቶ ሰማ ቢሮ ተመራሁ፤ ከባለጉዳይ ጋር መሆናቸውን የገለጹልኝ ጸሀፊያቸው ወይዘሮ አዝመራ ከ 5 ደቂቃ በሗላ እንድደውል ነገሩኝ፣ ደወልሁ፤ አሁንም ከባለጉዳዩ ጋር እንዳሉ ናቸው ተባለ፤ ከ15 ደቂቃ በሗላ ደውል ተባልሁ፤ ደወልሁ፣ አስቼኳይ ስራ ገጥሟቸው አሁን ከቢሮ ወጡ ተባለ፤ በዚሁ አበቃሁ። በሌላ ጊዜ እንሞክራቸዋለን፤ የተፈናቃዮችን ሁኔታም እንከታተላለን፤ ላሁኑ በዚሁ ላብቃ፣ ሰላም።