Thursday, April 10, 2014

“ንብረት የማፍራት መብት መገለፅ ያለበት በብሔረሰብ ደረጃ ሳይሆን በግለሰብ ነው” – አቶ ተክሌ በቀለ (የአንድነት ፓርቲ ም/ፕሬዝዳንት)

April 10/2014
በዘሪሁን ሙሉጌታ

የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ሁለተኛውን የሕዝብ ንቅናቄ መጀመሩ የሚታወስ ነው። ፓርቲው ከዚህ ቀደመ “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” በሚል መሪ ቃል የሕዝባዊ ንቅናቄ መድረኮች አዘጋጅቷል። አሁን ደግሞ “የሚሊዮኖች ድምፅ ለመሬት ባለቤትነት” በሚል መሪ ቃል ፕሮግራሙን ይፋ አድርጓል። ባለፈው እሁድ መጋቢት 28 ቀን 2006 ዓ.ም በደሴ ከተማ ፕሮግራሙን በሰላማዊ ሰልፍ አከናውኗል።
በደሴ ስለተካሄደው ሰላማዊ ሰልፍና “የሚሊዮኖች ድምፅ ለመሬት ባለቤትነት” በሚለው ርዕሰ ጉዳይ ላይ የፓርቲውን ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ተክሌ በቀለ፣ የፓርቲው የውጪ ግንኙነት ኃላፊ ኢንጂነር ዘለቀ ረዲ እና የፖርቲው ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሀብታሙ አያሌው ሰልፉን መርተውታል። ከመሬት ባለቤትነትና ከሰልፉ ጋር በተያያዘ የፓርቲውን ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ተክሌ በቀለን አነጋግረናቸዋል።
ሰንደቅ፡- በደሴ ያካሄዳችሁት ሰላማዊ ሰልፍ ምን ያህል የተሳካ ነበር?
አቶ ተክሌ፡- መጀመሪያ ፕሮግራሙን ያሰብነው በሐዋሳ፣ በአዲስ አበባና በደሴ ከተሞች ነበር። እንደአጋጣሚ ሆኖ የደሴው በመሳካቱ ቅስቀሳ ስናደርግ ቆይተን ሰልፉን ለማካሄድ በቅተናል። የአዲስ አበባውና የሐዋሳው ለሌላ ጊዜ ተዛውሯል። የሐዋሳውን በራሳችን ምክንያት ያራዘምነው ሲሆን፤ የአዲስ አበባው ግን በአስተዳደሩ ችግር ምክንያት ነው።
የደሴው ሰላማዊ ሰልፍ እንደጠበቅነው በከፍተኛ ሞቅታ ነው ፕሮግራሙ የተጀመረው። በርካታ ሕዝብ ተገኝቶልናል። የሰልፉ አካል ሆኖ በመሐል መንገድ ላይ መፈክር እያሰማ ሲሄድ የነበረው የሕዝብ ብዛት ከ50 እስከ 60 ሺህ ገምተነዋል። ከሰልፉ ጎን ለጎን ዳርና ዳር የሚሄደው ሕዝብ በግምት መቶሺህ ይሆናል። በእኛ እምነት ሕዝቡ በመሬት ጉዳይ ብቻ ሳይሆን የመሬት ጉዳይ የሚያስከፍላቸውን ማኅበራዊ ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን በመገንዘብ ከፍተኛ የሆነ መነሳሳት አሳይቷል። በተደረገው የሁለት ቀን ቅስቀሳ ያን ያክል ሕዝብ መውጣቱ የሕዝቡም ስሜት ከፍተኛ እንደነበር ያሳያል። በዚህ ወቅት እኔን ያስታወሰኝ በ2002ቱ መርጫ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ “ደሴም ሳይቀር አሸንፈናል” ብለው ነበር። አሁን ሳየው ግን የኢህአዴግ የምርጫ ኮንትራት ሳያበቃ ይሄን ያክል ሕዝብ ወጥቶ “በቃኝ” የማለቱ ሁኔታ ሲታየ ምርጫውን እንዴት ነበር ያሸነፉት ብዬ እንዳስብ አድርጎኛል።
ሰንደቅ፡- መሬት የፖሊሲ ጉዳይ እንደመሆኑ መጠን ከሰላማዊ ሰልፍ ይልቅ በሕዝባዊ ውይይት ማካሄዱ ይሻላል፤ አለበለዚያ በትንሹም በትልቁም ሰላማዊ ሰልፍ መጥራት የፓርቲውን ደጋፊዎች ያሰለቻል የሚል ነገር እየተነሳ ነው። ለዚህ ኀሳብ ያለዎት ምላሽ ምንድነው?
አቶ ተክሌ፡-ፕሮግራሙ ሲጀመር የመረጥናቸው ከተሞች ነበሩ። አዲስ አበባን ጨምሮ በርካታ የሀገሪቱ ምሁራን የሚገኙበት የአዳራሽ ውስጥ ስብሰባ አቅደን ነበር። ወደ አደባባይ እየገፋን ያለው ኢህአዴግ ነው። መሬትና ከመሬት ጋር ተያይዞ ለሚፈጠሩ ማኅበራዊ ኢኮኖሚያዊና የፍትህ ችግሮች በተመለከተ በሰላማዊ ሰልፍና በሕዝባዊ የአዳራሽ ስብሰባ ለይተን ነበር። ነገር ግን ገና ከመጀመሪያው አዲስ አበባ ላይ አዳራሽ ማግኘት ተቸግረናል። የመንግስት አዳራሾች ብቻም ሳይሆን በገንዘባችን ከፍለን የሆቴሎችን አዳራሽ ማግኘት አልቻልንም። ወደ ጎዳና እየገፋን ያለው ገዢው መደብ ነው።
ሰንደቅ፡- የመሬት ችግር በከተማና በገጠርም የተለያየ ነው። በሀገሪቱም የችግሩ አይነትና መጠንም የተለያየ ነው። በቀላሉ የሕዝብ ድጋፍ አላችሁ ተብሎ በሚገመተው ደሴ ከተማ ከማካሄድ ይልቅ በደቡብና ኦሮምያ ክልሎች ለምን እንቅስቃሴውን አልጀመራችሁም?
አቶ ተክሌ፡- በአጠቃላይ በመሬት ላይ ያለን እይታ ሦስት አይነት ነው። መሬት በግል፣ በወል ወይም በመንግስት ስር መሆን አለበት የሚል የመሬት ስሪት አቋም አለን። ኢህአዴግ ደግሞ መሬትን በተመለከተ የሚያስቀምጠው ከእኛ ፍፁም የተለየ ነው። በሕገ-መንግስቱ አንቀጽ 40 ንዑስ ቁጥር ስድስት ላይ መሬት የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች እንደሆነ አድርጎ ነው የሚያስቀምጠው። ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በቋንቋ፣ በሃይማኖት፣ በባህል፣ ወዘተ እንጂ ንብረት በማፍራት መብታቸው ሊገለፅ አይችልም። ንብረት የማፍራት መሠረታዊ መብት መገለፅ ያለበት በብሔረሰብ ደረጃ ሳይሆን በግለሰብ ነው። ኢህአዴግ ብሔር ብሔረሰቦች የሚያቋቁሙት መንግስት ነው ብሎ ስለሚያምን በተዘዋዋሪ መሬት የመንግስት እንደሆነ መረዳት ይቻላል። ይህ ማለት ደግሞ በብሔር ብሔረሰቦች ስም መሬትን ወይም የሕዝብን ንብረት ጠቅልሎ ኢህአዴግ ወስዶታል ማለት እንችላለን። በሌላ አነጋገር ግለሰቦች ከመሬት ባለቤትነት ውጪ ሆነዋል ማለት ነው። በእኛ እምነት የከተማ መሬት የግለሰቦች መሆን አለበት ብለን እናምናለን። የገጠሩ ደግሞ አስቀድሜ እንደነገርኩህ በግል፣ በወል ወይም በጋራ እና በመንግስት መያዝ አለበት።
ወደ ጥያቄህ ስመጣ አጠቃላይ የኢህአዴግ የመሬት ፖሊሲ በብሔር ብሔረሰቦች ሽፋን ከመውሰዱ አንፃር ችግሩ የመላ ሀገሪቱ ነው። ስለዚህ በደሴም ጀመርከው በደቡብ ችግሩ አንድና ተመሳሳይ ነው። በእርግጥ በደሴ የጀመርነው የተሻለ ተቀባይነት አለን በሚል መነሻ ብቻ አይደለም። አንድነት አጠቃላይ ሕዝቡ ከተቃዋሚው ጎራ ጋር እንደወገነ እንረዳለን። ኢህአዴግ የሚዘጋብን ሕዝቡ እንደሚደግፈን ስለሚያውቅ ነው። በእርግጥ አንድነት ያልደረሰባቸው፣ ሌሎች ተቃዋሚዎች ጠንካራ ስራ የሚሰሩባቸው ቦታዎች ይኖራሉ። ያም ሆኖ ስንጀምረው አዲስ አበባና ሐዋሳ ነበር። ደሴ አልነበረም።
ሰንደቅ፡- ገዢው ፓርቲ ተቃዋሚዎች በመሬትም ሆነ በሌሎች ጉዳዮች ላይ የጠራ ፖሊሲ የላቸውም እያለ ነው። በእናንተ እምነት በአሁኑ ወቅት የጠራ ፖሊሲ አለን ብላችሁ ታስባላችሁ?
አቶ ተክሌ፡- በመሬት ላይ ብቻ አይደለም። በአጠቃላይ ከመሬት ጋር ተያይዞ ያሉ ችግሮች በርካታ ናቸው። የሀገሪቱ አንጡራ ሀብት መሬት እንደሆነ አንረዳለን። ዋነኛ ትኩረታችንም የመሬት ምርታማነት፣ ባለቤትነትና ልማት ነው። ከገዢው ፓርቲ ጋር ካሉን የሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብት የአከባበር ልዩነቶች ባሻገርም አንዱና ዋነኛው መሬት ነው። ከሀገሪቱ የችግር ምንጮች ውስጥ አንዱ የመሬት ባለቤትነት ነው። ስለዚህ በዚህ ዙርያ ያሉ ችግሮችን ተረድተናል። ችግሮቹን በመረዳታችንም የጠራ ፖሊሲ ቀርፀናል። ከመሬት ባሻገርም በፋይናንስም በለው፣ በግብርናም ሆነ በውጪ ጉዳይ በማኅበራዊ ጉዳዮች ሀገሪቷዋን ከድህነትና ኋላቀርነት ያወጣል ብለን እናምናለን። ችግራችን የቀረፅናቸውን አማራጭ ፖሊሲዎች ለሕዝብ ማድረስ የምንችልበት የሚዲያ እና ወደ ሕዝቡ የምንቀርብበት መድረክ መዘጋቱ ነው። እና ኢህአዴግ “ተቃዋሚዎች አማራጭ የላቸውም” የሚለው አባባል ድሮ የቀረ ተረት ተረት ነው።
ሰንደቅ፡- በተቃዋሚዎች በኩል ወጥ የሆነ የመሬት ፖሊሲ አይስተዋልም። በተለይ በኦሮሞ ብሔር የተደራጁ ተቃዋሚ ፓርቲዎች መሬት የመንግስት ይሁን የሚል ዝንባሌ አላቸው። ሌሎቻችሁ ደግሞ “መሬት ይሸጥ ይለወጥ” እስከማለት ትደርሳላችሁ ይህ ደግሞ በምርጫ ወቅት አያስቸግርም?
አቶ ተክሌ፡- ተመሳሳይ ፕሮግራም ያላቸው ፓርቲዎች ውህደት ፈጥረው በአንድ ላይ ቢንቀሳቀሱ ችግሩ ሊፈታ ይችላል። የግል ስልጣንና የቡድናዊ ጥቅምን አስወግደው ወደ ውህደት ቢመጡ መልካም ነው። አሁን ፓርቲዎች ሚዛን በማይደፉ ጉዳዮች ላይ የተለያዩ ቢሆንም፤ ያነገቡት ፕሮግራም የተለያየ አይደለም፤ በመሆኑም ሕዝቡ የተለያዩ ፓርቲዎችን ቢመርጥም የሚመረጠው ፕሮግራም ግን ተቀራራቢና በአመዛኙ አንድ አይነት ነው ለማለት ያስደፍራል። በእርግጥ ከመድረክ ጋር በተያያዘ አንዱ ልዩነት የመሬት ባለቤትነት ጉዳይ ነው። ሆኖም ግን በመለስተኛ ፕሮግራማችን ላይ መሬትና ያልተፈቱ ሌሎች ጥያቄዎችን ሕዝቡ እንዲፈታቸው ተስማምተናል። ነገር ግን ሕዝቡ ደግሞ ደሞክራሲያዊና ሰብአዊ መብቶቹን ሙሉ በሙሉ አልተጎናፀፈም። መሠረታዊ ዴሞክራሲያዊ መብቶቹን ያልተጎናፀፈ፣ ሕዝብ ዋነኛ በሆኑ የሕዝብ ችግሮች ላይ መፍትሄ ለማምጣት መጀመሪያ የተነፈገውን መብት ማግኘት አለበት የሚል መረዳት አለ። በመሠረቱ የተጠቀሱት የኦሮሞ ድርጅቶችም መሬት የመንግስት ይሁን ሳይሆን፤ ሕዝቡ ይወስን እያሉ ነው። አረናን ብትወስደው መሬት የግል ቢሆንም፤ መሸጥ መለወጥ የለበትም ይል እና ጉዳዩ የሕገ-መንግስት ማሻሻያን የሚጠይቅ እንደመሆኑ ሕዝቡን ቀጥተኛ ተሳትፎ የሚጠይቅ ነው። በድምሩ ስታየው መሬትን በተመለከተ በተቃዋሚዎች ካምፕ ያለው መረዳት የሚያራራቅ ሳይሆን ሊታረቅ የሚችል ጉዳይ ነው።
ሰንደቅ፡- ፓርቲያችሁ በአሁኑ ወቅት የመሬትን ጉዳይ ያነሳው ለምንድን ነው?
አቶ ተክሌ፡- ኢትዮጵያ ውስጥ የስልጣን መባለግን ጨምሮ ከፍተኛ የሙስና ምንጭ የሆነው መሬት ነው። የመሬት ጉዳይ የፍትህ እጦትና የመልካም አስተዳደር ችግር መገለጫዎች አንዱና ዋነኛው ነው። ለሀገሪቱ ኢኮኖሚ አዝጋሚነትና ለማኅበራዊ ችግሮች ምንጩ የመሬት ባለቤትነትና የይዞታ አስተዳደር ችግር ነው። ይህንን እኛ ብቻ ሳንሆን እራሱ ገዢው ፓርቲ የሚያምንበት ጉዳይ ነው። በዚህ ወቅትም ጉዳዩን ልናነሳው የቻልነው ከመሬት ጋር ተያይዞ የሚነሱ ችግሮች ላይ ግንዛቤ ለመጨበጥ፣ ባለን ፖሊሲም ላይ እንደ ግብአት የሚያስፈልግ ነገር ካለም ለማካተት ነው። በዋናነት ግን የሀገሪቱ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ቀውሶች መገለጫ መሆኑን፣ የኢህአዴግ የመሬት ፖሊሲ የተሳሳተና ያስከተለውንም በሙስና የመጨማለቅ ሁኔታን ለማሳየት ነው።
በአሁኑ ወቅት መሬት በኢንቨስትመንት ስም የሙስና መንጭ ሆኗል። ግለሰብ በግለሰብነቱ ከመሬት ባለቤትነት ከራቀ በፖለቲካ ዓይን ስታየው የካድሬዎች መጫወቻ ይሆናል። ይህንን ማረጋገጥ የሚቻለው በተለያዩ ጊዜአት መንግስት የሚያስራቸው ባለስልጣናቱን እያየን ነው።
ሰንደቅ፡- በቀጣይ የምታካሂዱት እንቅስቃሴስ ምን ይመስላል?
አቶ ተክሌ፡- በትላልቅ ከተሞች በተለይም ምሁራንን በቀላሉ በምናገኝበት ቦታ የአዳራሽ ስብሰባዎች እያደረግን፣ ጉዳዩ በቀጥታ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ውይይት ይደረጋል። በገጠር ደግሞ በወረዳ ደረጃ የሚሰሩ ስራዎች አሉ። ሰላማዊ ሰልፎቹም በተመረጡ ከተሞች ይቀጥላሉ። እንደነገርኩህ መሬትን በተመለከተ ሕዝቡ በቂ ግንዛቤ እንዲያገኝ ዋነኛ ዓላማችን ነው። በገጠሩም በከተማም ሰፊ እንቅስቃሴ እናደርጋለን ብለን አቅደናል።
ሰንደቅ፡- ይህ መሬትን ማዕከል ያደረገ እንቅስቃሴ በቀጥታ ከ2007ቱ ምርጫ ጋር የሚያያይዘው ነገር አለ?
አቶ ተክሌ፡- ከምርጫ ጋር አይያያዝም። ምርጫ እንገባለን ወይስ አንገባም የሚለው የብሔራዊ ምክር ቤቱ ውሳኔ ነው የሚሆነው። በአጠቃላይ ያሉትን ሁኔታዎች እያየን የምንወስነው ጉዳይ ነው። አሁን ግን የመሬት ጉዳይ ያለንን ፖሊሲ ከማዳበርና ኅብረተሰቡም በመሬት ላይ የጠራ ግንዛቤ እንዲኖረው ማድረግ ነው።

1497470_617770758307862_5102468884195852277_n

No comments: