Thursday, April 24, 2014

የወታደራዊ መኮነኖች ቅነሳ?! ህወሓት እየተዳከመ መሆኑ የሚያሳይ ሌላ ማስረጃ ደግሞ በተለያዩ ክልሎች ይሰሩ የነበሩ የህወሓት የደህንነት ሰዎች ከያንዳንዱ ክልል መባረራቸው ነው!

April 24/2014
አብርሃ ደስታ

ህወሓቶች ከትግራይ የሚቀነሱ ወታደራዊ መኮነኖች ሲኖሩ ከኦሮምያ፣ ደቡብና አማራ ክልሎች ደግሞ ይጨመራሉ የሚል መረጃ ያስደነገጣቸው ይመስላል። በዚህ መረጃ የደነገጠ የህወሓት ካድሬ ካለ በትክክል ስለ ህወሓት መረጃ የለውም ማለት ነው።
በወታደራዊ መኮነኖች ቁጥር መቀነስና መጨመር ጉዳይ ሙያዊ ትንታኔ መስጠት አስፈላጊ ይመስለኛል። ምክንያቱም ወታደራዊ መኮነንነት ማዓርግ እንጂ ሹመት አይደለም። የራሱ የሆነ ወታደራዊ ዲሲፕሊንና ሳይንስ አለው። ስለዚህ በዚህ ጉዳይ አስተያየት ለመስጠት የተሟላ ሙያዊ መረጃ ሊኖረኝ ይገባል። አሁን የምችለው ሙያዊ አስተያየት ሳይሆን ፖለቲካዊ አስተያየት መስጠት ብቻ ነው። በዚሁ መሰረት የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት የብሄር (ወይ የክልል) ተዋፅዖ መሰረት ያደረገ ሳይሆን የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ተዋፅዖ መሰረት ያደረገ ነው።

(ወታደራዊ ማዓርግ የብሄር ተዋፅዖ መሰረት ያደረገ መሆን አለበት ብዬ አላምንም። ልምድና ብቃት ያለው፣ ለደረጃ መኮነንነት የሚመጥን ስብእናና ዕውቀት ያለው እንዲሁም ለሀገሩ ለመስራት ፍቃደኛ የሆነ፣ አካላዊና አእምሮአዊ ብቃት ያለው፣ ሁሉ ወታደራዊ ማዓርጉ ማግኘት አለበት፣ ሀይማኖቱ፣ ብሄሩና የፖለቲካ እምነቱ ግምት ዉስጥ ሳይገባ።) መከላከያ ሰራዊታችን (በተለይ ወታደራዊ መኮነኖች) የብሄር ወይ ክልል ተዋፅዖ የለውም። የፓርቲ ተዋፅዖ ነው ያለው።

መኮነናዊ ማዓርግ የሚሰጠው በብሄር ሳይሆን በፖለቲካ ነው (የህወሓት፣ የብአዴን፣ ኦህዴድ፣ ደኢህዴን ምናምን እየተባለ)። ማንኛውም ትግርኛ ተናጋሪ ወታደራዊ ማዓርግ የሚሰጠው ይመስላችኋል? የህወሓት ደጋፊ (በውስጥ አባል) ካልሆነ በቀር? ወታደራዊ ማዓርግ የሚሰጠው በፖለቲካ አመለካከቱ ነው። እንኳን መኮነኖች የጉምሩክና ገቢዎች ሰራተኞችም በፓርቲ ተዋፅዖ የተዋቀሩ ናቸው። በዚሁ መሰረት የህወሓት ወታደራዊ መኮነኖች ሲቀነሱ፣ የብአዴን፣ ኦህዴድና ደኢህዴን መኮነኖች ሲጨምሩ ከመለስ ዜናዊ ሞት በኋላ የህወሓትን ዓቅም በሌሎች የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች እየተዋጠ መሄዱ የሚያሳይ ነው። የህወሓት የበላይነት እያበቃ መሆኑ ምስክር ነው። ህወሓት እየተዳከመ መሆኑ የሚያሳይ ሌላ ማስረጃ ደግሞ በተለያዩ ክልሎች ይሰሩ የነበሩ የህወሓት የደህንነት ሰዎች ከያንዳንዱ ክልል መባረራቸው ነው። አሁን በሌሎች ክልሎች ይሰልሉ የነብሩ ህወሓቶች ተባረው በትግራይ መቐለ ከተማ ተሰባስበዋል። ይህን ሁሉ የሚያሳየው የህወሓትን መዳከም ነው።

መከላከያ ሰራዊታችን ከአንድ ፓርቲ አገልጋይነት ወደ ሀገር አገልጋይነት (ሀገራዊ ሰራዊት) እናሸጋግረዋለን። ሰራዊቱ አይፈርስም ግን የፓርቲ ሳይሆን የሀገር (የመንግስት) ይሆናል።

No comments: