Saturday, July 27, 2013

ሰበር ዜና፣ የአንድነት ፓርቲ አመራሮች ቤት በፖሊሶች እየተበረበረ ነው

July 27, 2013

ብርበራው ቀኑን ሙሉ እንደሚደረግ ታውቋል

በደቡብ ወሎ ዞን በሀይቅ ከተማ የሚገኙ የአንድነት ፓርቲ አመራሮችና አባላት ቤት ላይ ዛሬ ከማለዳው 12 ሰዓት ጀምሮ ብርበራ እንደተጀመረ የዞኑ የአንድነት ፓርቲ አመራሮች ለፍኖተ ነፃነት አስታወቁ፡፡

የአንድነት ፓርቲ የወረባቡ ወረዳ ሰብሳቢ አቶ እድሪስ ሰኢድ ለፍኖተ ነፃነት እንዳስታወቁት ዛሬ ከማለዳው 12 ሰዓት ጀምሮ “የጦር መሳሪያ ሰውራችኋል” በሚል ፖሊሶችና ሚኒሻዎች በሀይቅ ከተማ ባሉ ከ16 በላይ በሚሆኑ የአንድነት ፓርቲ አመራሮችና አባላት መኖሪያ ቤት ውስጥ ብርበራ አካሂደዋል፡፡ ብርበራው ከተካሄደባቸው አመራሮች መሀከል አንዱ የሆኑት የወረዳው የአንድነት ፓርቲ የፋይናንስ ኃላፊ አቶ አራጌ ሑሴን ለሪፖርተራችን እንደገለፁት 5 ፖሊሶችና 1 ሚሊሻ ከማለዳው 12 ሰዓት ጀምረው መኖሪያ ቤታቸውን ፈትሸዋል፡፡ አቶ አራጌ ሁሴን አክለውም “እኔ ሰላማዊ ሰው ነኝ ምንም አታገኙም አልኳቸው፤እንዳልኩትም 2 ሰዓት የፈጀ ብርበራ አድርገውም አንዳች ሳያገኙ ወጥተዋል” በማለት ገልፀዋል፡፡

“ብርበራው መንግስት በአንድነት አባላት ቤት ውስጥ የጦር መሳሪያ አገኘሁ በሚል የተለመደ ድራማ ለመስራት እንደተዘጋጀ የሚያስረዳ ነው” ያሉት የአንድነት ፓርቲ የደቡብ ወሎ ዞን ሰብሳቢ አቶ ብስራት አቢ ኢህአዴግ የደቡብ ወሎ ህዝብ በግዳጅ አንድነት ፓርቲን እንዲያወግዝ በተለያዩ ከተሞች ስብሰባና ሰላማዊ ሰልፎችን እንደጠራ አስረድተዋል፡፡ በአንድነት አባላት ቤት የሚደረገው ብርበራ እስከ ምሽት ሊቀጥል እንደሚችልም ለፍኖተ ነፃነት የደረሱ መረጃዎች አመላክተዋል፡፡

No comments: