Wednesday, July 10, 2013

24 ሚሊየን ዶላር በመመዝበር የተጠረጠሩ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ኮርፖሬሽን የስራ ሃላፊዎች ተከሰሱ

አዲስ አበባ ፣ሃምሌ 3፣ 2005 (ኤፍ ቢ ሲ) 24 ሚሊየን ዶላር መዘበሩ ባላቸው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ኮርፖሬሽን ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች የፌደራሉ የስነ ምግባርና  ፀረ ሙስና ኮሚሽን ክስ መሰረተ።

በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር የዋሉት የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ኮርፖሬሽን ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎችን ጨምሮ ዘጠኝ ተጠርጣሪዎች ዛሬ ፍርድ ቤት ቀርበዋል።

የኮሚሽኑ የምርመራ ቡድን በእነ አቶ መስፍን ብርሃኔ የኮርፖሬሽኑ የዲስትሪቢዩሽን ስራ አስፈጻሚ ላይ ያቀረበው ክስ ከአራት አመት በፊት ትራንስፎርመር ለመግዛት ኮርፖሬሽኑ ያወጣውን ጨረታ ይመለከታል።

በዚህ ጨረታ ላይ ኮርፖሬሽኑ 3 ሺህ 520 የተለያዩ መጠን ያላቸውን ትራንስፎርመሮች ለመግዛት ጨረታ ያወጣል። 

 የመርማሪ ቡድኑ ክስ ጉድ ላክ ስቲል የተባለው ኩባንያ ጨረታውን ካሸነፈ በኋላ ሪዘርቭ ባንክ ኦፍ ኢንዲያ ለተባለ ባንክ አቶ መስፍን ከኮርፖሬኝኑ እውቅና ውጭ ለጨረታው ውል ለመፈፀም ገንዘብ ለማግኘት ደብዳቤ ፅፈዋል ይላል።

በጨረታው 3 ሺህ 520 ትራንስፎርመሮችን ለመግዛት ቢታቀድም አሮጌና ያገለገሉ ትራንስፎርመሮች ቀርበዋል ፤ ግዥውም ያልተገባ አካሄድ የተከተለ ነው ሲል የኮሚሽኑ የምርመራ ቡድን ክሱን መስርቷል።

በዚህ መዝግብ የዲስትሪቢውሽንና ቴክኒክ ቡድን ክፍል መሪ አቶ መኮንን ብርሃኔ እንደ ዋነኛ ድርሻቸው ትራንስፎርመሮችን መርምረው መረከብ ሲገባቸው በቀጥታ ከአቶ መስፍን የመጣውን የግዥ ውል ተቀብለዋል በመባል ተጠርጥረዋል።

የምርመራ ቡድኑ ክስ በዚህም መነሻነት በመንግሰት ላይ 17 ሚሊዮን ዶላር ጉዳት ደርሷል ይላል።

ሁለተኛው የክስ መዝገብ በኮርፖሬሽኑ የሃገር አቀፍ የኤሌትሪክ ሃይል አቅርቦት ፕሮግራም ስራ አስፈፃሚ በሆኑት በአቶ ሽፈራው ተሊላ የተሰየመ ነው።
አቶ ሽፈራው የስልጣን ውክልና ሳይኖራቸውና የኮርፖሬሽኑን ይሁንታ ሳያገኙ ለሪዘርቭ ባንክ ኦፍ ኢንዲያ የውሉን ተቀባይነት ማረጋገጫ ደብዳቤ ፅፈዋል ሲባሉ ተጠርጥራው ክስ ተመስርቶባቸዋል።

በዚህ መዝገብ የኢንጅነሪንግ ክፍል ሃላፊው አቶ ሚሊዮን ማቱሳላ ደረጃውን ያልጠበቁና አሮጌ ትራንስፎሮቹን መርምረው ውድቅ ማድረግ ሲገባቸው ስራ ላይ አውለዋል ተብለው ተከሰዋል።

7 ሚሊየን ዶላር መንግስትን ባከሰረው በዚህ መዝገብ የሰፕላይ ቼን ሃላፊ አቶ ዳንዔል ገብረ ስላሴ ፣ የኢንግነሪንግ ፕሮሰስ የስራ ተወካይ አቶ ሠመረ አሳቤና የጨረታ ኮሚቴዎቹ አቶ ፋሪስ አደም ፣ አቶ ብሩክ ተገኝና ጌታቸው አዳነ በክስ መዝገቡ ተካተዋል።
በሁለቱ መዝገብ በአጠቃላይ ከ24 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር በላይ በትራንስፎርመር ግዥ ጨረታ መንግስትን ያለ አግባብ እንዲመዘበር አድርገዋል ሲል የክስ መዝገቡ ያስረዳል።

ማክሰኞ ዕለት በቁጥጥር ስር የዋሉት ዘጠኝ የኮርፕሬሽኑ ሃላፊዎች ላይ የምስክር ቃል መቀበል ፣ የተጠርሪዎቹን ቃል ለመቀበልና ቀሪ ማስረጃ ለማሰባሰብ የኮሚሽኑ የምርመራ ቡድን ተጨማሪ የ14 ቀን የግዜ ቀጠሮ ጠይቋል።

ፍርድ ቤቱም ተከሳሾቹ ያቀረቡትን የዋስትና ጥያቄውን አሳማኝ ሆኖ ባለማግኘቱ ቀሪ ማስረጃን ለመስማት ለሐምሌ 17 ቀን 2005 ዓ ም ቀጠሮ ይዟል።

ምንጭ ፋና

No comments: