Friday, July 19, 2013

የኢትዮጵያ ወታደሮች የሞርሲና ቦዲ ሴቶችን የደፍራሉ ሲል አንድ የምርምር ተቋም አስታወቀ

ሐምሌ ፲፩(አስራ አንድ)ቀን ፳፻፭ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ኦክላንድ ኢንስቲቲዩት ባወጣው መግለጫ በኦሞ ሸለቆ የሚገኙ የሙርሲና የቦዲ ነዋሪዎች አካባቢያቸው ለሸንኮራ ገዳ ምርት ይፈለጋል በሚል በሀይል ቀያቸውን እንዲለቁ ከመደረጉ ጋር ተያይዞ ከፍተኛ የሆነ የሰብአዊ መብቶች ጥሰት መፈጸሙን ገልጿል። ድርጊቱ በአሜሪካ እና በእንግሊዝ መንግስት እርዳታና  እውቅና እየተካሄደ መሆኑም ገልጿል፡፡
የእንግሊዝ መንግስት የልማት ተራድኦ የውጭ ግንኙነት ክፍል ቃል አቀባይ ፣ ” የእኛ ድጋፍ ለዘመናት በጦርነትና በረሀብ ስትሰቃይ ለኖረችዋ ኢትዮጵያ ረድቷል” ብለዋል።
ኦክላንድ ተቋም በበኩሉ የልማት አጋር አገራት ከሰብአዊ መብቶች ጥሰት ጎን ለጎን የሚካሄደውን ልማት መደገፋቸው አሳሳቢ ነው ብሎአል።  አንድ የሙርሲን አባወራ ” ወታደሮች በየአካባቢያችን ተሰማርተው የቦዲን ሴቶች ወስደው ደጋግመው ደጋግመው ደፈሩዋቸው፣ ከዛም የእኛን ሚስቶች ደፈሩዋቸው” በማለት ለተቋሙ መናገራቸው ተገልጿል።
የእንግሊዝ የልማት ተራድኦ ሰብአዊ መብቶችን በሚጥስ መንግስት የሚገኙ ህዝቦችን አትርዱ ማለት፣ ለተረጅዎች ሁለተኛ ጉዳት ነው በማለት የተቋሙን ሪፖርት ሳይቀበሉት ቀርተዋል።
ኢትዮጵያ በየአመቱ ከለጋሽ አገራት  ከ50 እስከ 60 ቢሊዮን ብር የሚደርስ ገቢ እርዳታ ታገኛለች።
ኢትዮጵያ መንግስት በጉዳዩ ዙሪያ የሰጠው አስተያየት የለም።

No comments: