Friday, July 19, 2013

ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ የምናደርገው ትግል በስም ማጥፋትና በፍረጃ አይገታም!!!!

Submitted by Admin on Fri, 07/19/2013 - 12:30

ከሰማያዊ ፓርቲ የተሰጠ መግለጫ


 ሰማያዊ ፓርቲ በሃገራችን የሚፈፀሙ የሰብአዊ መብት ጥሰትና የአስተዳደር ብልሹነት እንዲስተካከል የመንግሥት አካላት አስፈላጊውን እርምጃ እንዲወስዱ በተደጋጋሚ ሲጠይቅ መቆየቱ ይታወሳል፡፡ ነገርግን እነዚህ ጥያቄዎቻችን በመንግሥት በኩል ምላሽ ስለተነፈጋቸው ጥያቄዎቹ ከፍ ባለደረጃ ትኩረት እንዲያገኙ ሆነው መቅረብ እንዳለባቸው ተገንዝበናል፡፡ በዚህም መሰረት ጥያቄዎቹን በሰላማዊ ሰልፍ መጠየቅ እንዳለበት ወስኖ ግንቦት 25 ቀን 2ዐዐ5 ዓ.ም በአዲስ አበባ ባካሔደው ታላቅ ሠላማዊ ሠልፍ ጥያቄዎቹ እንዲመለሱ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡

 በተጨማሪም ጥያቄዎቻችን ከመንግሥት በኩል በሦስት ወር ጊዜ ምላሽ የማያገኙ ከሆነ ሌላ የተቃውሞ ሠልፍ ከፍ ባለ ደረጃ የሚጠራ ስለመሆኑ ፓርቲው አቋሙን በሰልፉ ዕለት አሳውቋል፡፡

 ይሁንእንጂ ሰልፉ ከተጠናቀቀበት ዕለት ጀምሮ በገዥው ፓርቲና በመንግሥት ተወካዮች የተሠጡ መግለጫዎች ያስገነዘቡን መፍትሔ እንዲሠጣቸው ለቀረቡ ጥያቄዎች መንግስት ተገቢውን መልስ ለመስጠት ምንም ዓይነት ፍላጐት እንደሌለው ነው፡፡ ከዚህም አልፎ መንግስት ጥያቄዎቹ የቀረቡበትን መንፈስ እንኳ በቀናነት ለመቀበል ያልፈለገ መሆኑን ያሳያል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ፓርቲያችንን ለመጫንና ስሙን ለማጉደፍ በፕሮግራሙም ሆነ በሥራ እንቅስቃሴው የሌለበትን በአክራሪነትና በአሸባሪነት ለመወንጀል ተደጋጋሚ ጥረት እያደረገ መሆኑን ከሚሠጣቸው መግለጫዎች ተረድተናል፡፡

 ይህ የመንግስት አካሔድ የጥያቄዎቻችንን አቅጣጫ ለማስቀየር ከሚደረግ ሙከራ ውጭ የትግሉን እንቅስቃሴ ሊገታው እንደማይችል ዛሬ ሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎች እያደረጉ ያሉት የሰላማዊ ትግል እንቅስቃሴ አብይ ማስረጃ ነው፡፡ በተጨማሪም መንግስት የሚያደርጋቸውን ፍረጃና ስም ማጉደፍን በመፍራት የኢትዮጵያ ህዝብ የሚደርስበትን የሰብአዊ መብት ጥሰትና የአስተዳደር ብልሹነት ከዚህ በላይ ተሸክሞ ለመኖር የማይችልበት ደረጃ ላይ መድረሱን ያሳያል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በአሁኑ ወቅት ለነፃነትና ለፍትህ መገኘት እያደረጉ ያለውን እንቅስቃሴ ፓርቲያችን እያደነቀ ትግላቸንን አጠናክረን እንድንቀጥል መልዕክቱን ያስተላልፋል፡፡

 ሰማያዊ ፓርቲ ግንቦት 25 ቀን 2ዐዐ5 ዓ/ም. ካካሄደው ታላቅ ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ዕለት ጀምሮ በገዥው ፓርቲና በመንግሥት የተወሰዱ አቋሞችን በመገምገም ፓርቲው ላቀረባቸው ጥያቄዎች የተሠጠ ምላሽ አለመኖሩንና አንዳንዶቹም ችግሮች እየተባባሱ መሔዳቸውን ተገንዝቧል፡፡

ስለሆነም ፓርቲያችን ለሕዝብ በገባው ቃል መሠረት ነሀሴ 26 ቀን 2ዐዐ5 ዓ.ም ከፍ ያለ የተቃውሞ ሰልፍ በማካሄድ አሁንም በሃገራችን የሚካሄዱ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችና የአስተዳደር ብልሹነቶች እንዲስተካከሉ፣ በተለይም የፖለቲካና የህሊና እስረኞች እንዲፈቱ፣ የመንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ ገብነት እንዲቆም፣ የተፈናቀሉ ዜጐች ወደመኖሪያቸው እንዲመለሱና አፈናቃዮችም ለፍርድ እንዲቀርቡ፣ ሙስናና የተበላሹ አሰራሮች እንዲወገዱ ላቀረባቸው ጥያቄዎች ምላሽ እስኪያገኙ ድረስ ትግሉን አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡

 በዚሁም መሰረት መንግስት በፓርቲዎች ላይ ከሚነዛው ስም ማጥፋትና ፍረጃ እንዲቆጠብና ፓርቲያችን ላነሳቸው ጥያቄዎች ተገቢውን ምላሽ እንዲሰጥ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ፣ የፓለቲካ ፓርቲዎችና የሲቪክ ማሕበራት ነሀሴ 26 ቀን 2ዐዐ5 ዓ.ም በምናደርገው ታላቅ የተቃውሞ ሰልፍ በመሳተፍ የየበኩላቸውን አስተዋፅዖ እንዲያደርጉ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡
ሐምሌ 12 ቀን 2005 ዓ.ም

 አዲስ አበባ
 

No comments: