Wednesday, July 10, 2013

በቁጫ ወረዳ የተነሳውን ተቃውሞ ተከትሎ የታሰሩ ሰዎች ቁጥር ከ450 በላይ መድረሱ ታወቀ

ሐምሌ ፪( ሁለት )ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና :-የኢሳት ምንጮች እንደገለጡት ካለፈው አርብ ጀምሮ ከማንነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ በተፈጠረው ተቃውሞ ከ470 ያላናሱ ሰዎች እስከ ትናንት ድረስ ተይዘው የታሰሩ ሲሆን፣ ተቃውሞውን አስተባብረዋል ከተባሉት መካከል በዋና ከተማዋ ሰላም በር የሚኖሩ ከ13 በላይ የአገር ሽማግሌዎችና ታዋቂ ሰዎች ተመርጠው ወደ አርባ ምንጭ እስር ቤት መወሰዳቸው ታውቋል።

ወደ  አርባምንጭ እስር ቤት ከተላኩት መካከል አቶ አማኑኤል ጎቶሮ ፣ ደፋሩ ዶሬ ፣  እዮብ ጦና፣  ሻምበል ሻዋ፣ አልመሳ አርባ፣ አቶ ባንቲርጉ ሄባና፣ ወ/ሮ ጊፍታነህ ፈርአ፣ ባሻ ፋንታሁን ታደሰ፣ አቶ አበራ ገ/መስቀል፣ መ/ር ዶለቦ ቦንጃ ፣ መምህር መሸሻ ማላ፣ አቶ ጴጥሮስ ሀላላ እና አቶ ቲንኮ አሻንጎ ይገኙበታል።

የወረዳው ፖሊስ በዛሬው እለት 15 የሚሆኑ ወጣቶችን ከእስር ለመልቀቅ መፈለጉን ቢያስታውቅም፣ “እስረኞቹ ግን መጀመሪያውኑ ለምን አሰራችሁን አሁንስ በምን ምክንያት ትለቁናላችሁ” የሚል ጥያቄ በማቅረባቸው እስካሁን እንዳልተለቀቁ ታውቋል።

በጉዳዩ ዙሪያ አስተያየታቸውን የጠየቅናቸው በከተማዋ የሚገኙት የአንድነት ፓርቲ የደቡብ ተወካይ አቶ ዳንኤል ሺበሺ እንደተናገሩት ፖሊስ ምግብ ከሚያቀብሉ ሴቶች እና ልጆች  በስተቀር ሌሎች ነዋሪዎች ወደ አካባቢው እንዳይጠጉ በመከልከሉ የእስረኞችን ቁጥር በትክክል ለማወቅ እንዳልተቻለ ተናግረዋል። ይሁን እንጅ ከ470 በላይ ሰዎች መታሰራቸውን መረጃ እንደደረሳቸው ገልጸዋል።

ኢሳት ከ86  በላይ የታሰሩ ሰዎች ስም ዝርዝር ደርሶታል።  ከእስረኞች መካከል የመጀመሪያ ዲግሪ ያላቸው በሙያቸው ረዥም ዓመታትን ያገለገሉ  ከ22 የማያንሱት ደግሞ የኢህአዴግ አመራር አባላት የነበሩ ሲሆን፤ ቀሪዎቹ ደግሞ ነጋዴዎች፣ ተማሪዎች፣ ሥራ አጦች፣ የዩንቨርሲቲና የኮሌጅ ሌክቼሬሮች፣ የመንግሥት ሠራተኞች፤ የከተማ ነዋሪዎች ናቸው፡፡

አካባቢው ዛሬም በመከላከያ እና በልዩ ፖሊስ አባላት እየተጠበቀ መሆኑን ለማወቅ ተችሎአል
እሁድ ሰኔ 30፣ 2005 ዓም በደቡብ ክልል በጋሞ ጎፋ ዞን በቁጫ ወረዳ በሰላም በር ከተማና አካባቢዋ የሚኖሩ ከ7 ሺ በላይ ነዋሪዎች፣ የማንነት ጥያቄ በማንሳታቸው የታሰሩ መሪዎቻችን ይፈቱትልን የሚል ጥያቄያቸውን በወረዳ ጽህፈት ቤት ተገኝተው ለማቅረብ በተጓዙበት ወቅት የዞንና የወረዳ ፖሊሶች በነዋሪዎቹ ላይ ድበደባ መፈጸማቸውን እና በመቶዎች የሚቆጠሩትን ማሰራቸውን መዘገባችን ይታወሳል።

No comments: