Friday, July 26, 2013

በኢትዮጵያ የሚታየው የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ተባብሷል

ሐምሌ ፲፰(አስራ ስምንት)ቀን ፳፻፭ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን ኃይል በፈረቃ የማዳረስ ተግባር በሚስጢር ማከናወኑን አጠናክሮ መቀጠሉን ምንጮች ጠቆሙ፡፡ በተለይ በአዲስአበባ ከሰኔ ወር 2005 አጋማሽ ጀምሮ በተከታታይ የኤሌክትሪክ ኃይል በመቋረጥ ላይ የሚገኝ ሲሆን በአንዳንድ የከተማዋ አካባቢዎች የኃይል መቋረጡ በተከታታይ እስከሶስት ቀናት የሚወስድ ጭምር መሆኑ ነዋሪውን ሕዝብ ግራ የሚያጋባ ሆኗል፡፡

የኃይል መቆራረጡ እንደባንክ፣ አየር መንገድ ያሉ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት የኢንተርኔት ኔትወርክ በማስተጓጎል ሥራዎቻቸውን እያስቆመ ከመሆኑም በላይ ተጠባባቂ ጄኔሬተር የሌላቸው በተለይ አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎችን ማምረት ወደማይችሉበት ደረጃ ላይ አድርሷቸዋል፡፡

በተደጋጋሚ እያጋጠመ ያለውን የኃይል መቆራረጥ ከተራ የቴክኒክ ችግሮች ጋር ለማያያዝ ቢሞከርም የኮርፖሬሽኑ ምንጮች ግን በየጊዜው እያደገ የሚሄደውን የሃይል ፍላጎት ጋር አቅርቦቱ ተመጣጣኝ ባለመሆኑ ችግሩ መከሰቱን በመጠቆም በውስጠ ታዋቂ ኃይል በፈረቃ የማዳረሱ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ክልሎችን ጨምሮ በአዲስአበባም አካባቢዎች እየተለዩ ኃይል በፈረቃ የማዳረሱ ሥራ እየተሠራበት ነው ብለዋል፡፡

 ኮርፖሬሽኑ የፈረቃ የኃይል ዕደላውን በሚስጢር ለመያዝ የተገደደው ምናልባትም ለጎረቤት አገራት የኤሌክትሪክ ኃይል ከመሸጡ ጋር ተያይዞ እየተሰነዘረበት ያለውን ትችት ለማለዘብ ሊሆን ይችላል።

በኤሌክትሪክ ኃይል መቋረጥ ቀውስ ውስጥ የምትገኘው ኢትዮጵያ በአሁኑ ሰዓት ከ35 እስከ 40 ሜጋዋት የኤሌክትሪክ ኃይል ለጅቡቲ በመሸጥ በወር ከ 2 ነጥብ 1 ሚሊየን ዶላር በላይ ገቢ እያገኘች እንደሆነም ለኢሳት የደረሰው መረጃ የመለክታል።
በተጨማሪም በተመሳሳይ ሁኔታ ለኬንያ ኃይል ለመሸጥ እ.ኤ.አ በ2006 ኢትዮጵያና ኬንያ ስምምነት መፈራረማቸው ይታወቃል።

በኢትዮጵያ አቆጣጠር በ2004 አጋማሽ የሶማሌላንድና የኬንያ ሞያሌ ከተሞች ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኔትወርክ
ጋር እንዲገናኙ መደረጉና በዚህም ገቢ እየተገኘ መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ።

የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት የአገር ውስጥ ፍላጎት ባልተሟላበት ሁኔታ ለጎረቤት አገራት ኤክስፖርት የማድረግ ፋይዳ ምን እንደሆነ የኮርፖሬሽኑ የስራ ሃላፊዎች በተደጋጋሚ ከመገናኛ ብዙሃን ለሚቀርብላቸው ጥያቄዎች ” አንድ ጊዜ የምንሸጠው የሚተርፈንን ኃይል ብቻ ነው፣ሌላ ጊዜ ደግሞ ኃይል ካነሰን መልሰን መውሰድ እንችላለን” በማለት እርስ በእርሱ የሚጋጭ መግለጫ ሲሰጡ መቆየታቸው የሚታወስ ነው::

በተለይ ካለፈው አንድ ወር ጀምሮ በተከታታይ የኀይል መቋረጥ ማጋጠሙ ለኤክስፖርት የሚያመርቱ ኢንዱስትሪዎችን ጭምር እየጎዳ መሆኑን በመጠቆም ጥናት ቢሰራ አገሪቷ ኃይል ሸጣ ከምታገኘው ይልቅ በዚህ መንገድ እያጣች ያለችው ከፍተኛ ሊሆን እንደሚችል ዘጋቢያችን አስተያየቱን አስፍራል። በመላ አገሪቱ በርካታ ፋብሪካዎች ተገንብተው በሀይል እጥረት ስራ አልጀመሩም። ስራ የጀመሩትም ቢሆኑ ብዙዎች በኪሳራ ሰራተኞቻቸውን እየቀነሱ ነው።

No comments: