Monday, September 8, 2014

ህዝባዊ እንቢተኝነት ለነፃነት እና ለፍትህ ! (በይድነቃቸው ከበደ)

Sep8,2014
በአገራችን የፖሊቲካ ሥርዓት ሄደት ውስጥ ስልጣን በሰላማዊ መንገድ ከአንዱ ወደሌላው የተሸጋገረበት አጋጣሚ እጅግ በጣም አናሳነው፡፡ አብዛኛው የስልጣን ሽግግር ጉልበትና ብረትን መሰረት ያደረገ ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱ የስልጣን ሽግግር ጉልበተኞች ሁሌም አሸናፊ የሚሆኑበት ጉልበቱ አናሳ የሆነ ከስልጣን የሚርቅበት ዓይነተኛ መንገድ ነው፡፡ይህም በመሆኑ በህዝብ ፍቃድ እና ምርጫ ወይም በህዝባዊ እንቢተኝነት የመንግስት የአስተዳደር የስርዓት ለውጥ ወይም ጥገናዊ ማስተካከያ ለውጥ ከዚህ ቀደም እንዲሁም ባሁን ወቅት በአገራችን ስለ መደረጉ ምስክርነት ለመስጠት የሚያስችል አጋጣሚ ስለመኖሩ ያጠራጥራል፡፡ ለዚህም ነው ሰላማዊ ትግል በአገራችን ተስፋ አስቆራጭ እና የማይሞከር መስሎ የሚታየው፡፡
ይድነቃቸው ከበደ
ይድነቃቸው ከበደ

እርግጥነው በሰላማዊ ትግል ሂደት ውስጥ ውጣ ውረዶ የበዛ ነው፡፡ በዓለማችን ላይ የተካሄዱት ሠላማዊ ትግሎች ውጤት ያስመዘገብት መተኪያ የሌለውን የሰውልጅ ሕይወትን እስከመንጠቅ በመድረሰ ነው፡፡ ይበልጥ ደግሞ ትግሉ አስቸጋሪ የሚያስመስለው ውጤቱ የሚፈጀው ጊዜ ነው፡፡ ሠላማዊ ትግል ማለት ታጋዩ የሚታገልለትን ውጤት ሣይመለከት በትግሉ ሂደት የሚሰዋበት ነገር ነው እስከመባል ይደርሳል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ደረጃ ለመድረስ ከሌላ ጋር ሣይሆን ከእራስ አስተሳሰብ ጋር ይህ ቀረሽ የማይባል ትግልን ማካሄድ ይጠይቃል፡፡ ይሁን እንጂ እንዲህ-አይነቱ የአስተሳሰብ ልዕልና ለመድረስ ገፊ ምክንያቶች ካሉ፣ ምክንያቶችሁ በስትራቴጂ ከተነደፉ፣ የገዥው ስርዓት ደካማ ጎኖ በሚገባ ከታወቀና ከተለየ፣ ተምሳሌታዊ እንዲሁም ደረጃ በደረጃ የሚያድግ ሰላማዊት ግሉን የሚመራ ጠንካራ ተቋም ካለ የሰላማዊ ትግል የአስተሳሰብ ደረጃ ማሳያ የሚሆን በአመርቂ ውጤት የተደገፈ ተግባር እውን ሆኖ ማያት የማይቻልበት ምንም ምክንያት የለም ፡፡ በመሆኑም የሠላዊ ትግል መገለጫዎች ከሆኑት ውስጥህ ዝባዊ እንቢተኝነት ከአምባገነን አገዛዝ ወደ ዲሞክራሳዊ ስርዓት ለመሸጋገር አይነተኛ መንገድ ነው፡፡ ስለዚህም ህዝባዊ እንቢተኝነት ወንጀልም አጢያትም አይደለም! ህዝባዊ እንቢተኝነት በተለያዩ አገሮች በተለያየ ወቅት የተተገበር እና ውጤት የታየበት ከአምባገነናዊ ስርዓት የመላቀቂያ ቀጥተኛ መንገድ ነው ብሎ መደምደም ባይቻልም ተመራጭ የሰላማዊ ትግል ስትራቴጂ ነው፡፡ ሁላችንም ሊያስማማን የሚችለው ጨቋኝ የመንግስት ሥርዓት ባለበት ህዝባዊ እንቢተኝነት የቅንጦት ጉዳይ ሣይሆን የህልውናምርጫ ይሆናል፡፡ በዚህም ምክንያት ህዝባዊ እንቢተኝነት የትኛውም አይነት ስም ቢሰጠው ተጨቋኝ እና ጨቋኝ እስካለ ድረስ አይቀሬነቱ እርግጥ ነው፡፡

ጨቋኝነት እራስን በክፉ ልቦና እና በጥላቻ በማስገዛት ከሰውነት በታች በራስ ፍቃድ የሰው መጥፎ መሆንን ወዶ መቀበል ነው፡፡ መጮቀን ግን ማንም የትም ፈልጎ የማይቀበለው ጉልበተኛ ጉልበት በሌለው ላይ የሚያሸክመው የግፍ ክምር ነው፡፡መጨቋን በግለሰብ ደረጃ ሲሆን እዳው ገብስ ነው ተብሎ ቀሎ ባይታይም፣ በአገር እና በመንግስት ሲሆን ግን ልብ ይስብራል የማንነትም ክብር ያሳጣል፡፡ ጭቋና በሃይማኖት፣ በጎሣ፣ በአስተሳሰብ እና በፖለቲካ አመለካከት ምክንያት ሲፈፀም የጭቆና ቀንበር መሸከም ይከብዳል፡፡

በመሆኑም በስልጣን ላይ የሚገኝ የህዝብ ፍቃድ ጨርሶ ያላየው በሃይል እየገዛ የሚገኘ መንግስት፡፡በሃይማኖት፣ በጎሣ፣ በአስተሳሰብ እና በፖለቲካ አመለካከት በዜጎቹ ላይ እያደረሰ ያለው ጭቆና መጠኑ እና አይነቱ እየበዛ ከሄደ ለዜጎች እንቢተኝነት ምላሹ የሥርዓት ለውጥ ብቻ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በጭንጋፍ አምባገነናዊ የመንግስት አስተዳደር ውስጥህ ዝባዊ እንቢተኝነት ያለው ምልክታ እንደሌሎች ፓለቲካዊ እንቅስቃሴ እና ተቃውሞ የተሸዋረር እይታ አይደለም፡፡
ይሁን እንጂ የአገራችን ወቅታዊ ሁኔታ መነሻ በማድረግ እኛ ኢትዮጵያዊያን ስለ እዝባዊ እንቢተኝነት ለመነጋገር ሳይሆን ተግባራዊ ለማድረግ በቂ ምክንያቶች አሉን፡፡ የመጀመሪያው እና ወሳኙ በህዝብ መልካም ፍቃድ እና ምርጫ ይሁንታ ባላገኘው ጉልበተኛ መንግስት አማካኝነት ነፃነት እና ፍህት በአደባባይ መነጠቃችን እና በተነጠቅነው ምትክ እየደረሰብን ያለው መንግስታዊ ጭቆና ከልክ በላይ መሆኑ ነው፡፡ የህዝብ ስልጣን ባለቤት ቀማኞች ኢትዮጵያዊ ማንነት እና ክብር በማሳጣት ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነት ንእንዲጠፋ ለማድረግ እና እነሱ እንደሚፈልጉት አይነት ሃገር ሆና ማየት የቀን የለሊት ምኞታቸው እንዲሁም ጥረታቸውም ጭምር ነው፡፡ ማንነትን ከማሰናከል እና ከማጥፋት የሚጀምረው መንግስታዊ ውንብድና እጅ ሳይሰጡ ለምን ብሎ መጠየቅ ትልቁ እና የመጀመሪያው የነፃነት ጥያቄ ነው፡፡ የጥያቂው ምላሽ ምንም ይሁን ምን በጀግኖች አባቶቻችን እና እናቶቻችን ተከብራና ታፍራ የኖረችው በፈጣሪ ቃልኪዳን እና እገዛ ሁሌም በክብር ትኖራላች፡፡

በአገራችን ሞልቶ በፈሰሰው የግፍ ፅዋ ያልተነካው ማነው ? 23 ዓመት ሙሉ ነፃነት እና ፍትህ በመነጠቅ የቁም እስረኛ በመሆኑ የተጨነቀው ስንቱ ነው? ጭንቀቱ አላስችል ሲለው አገር ጥሎ በሰው አገር የሚኳትነው ምን-ያህል ነው? በአገዛዙ ስርዓት ምክንያት የስንት ሰው ህይወት ተሰዋ ? የታሰረው እና የቆሰለው ቤት ይቁጠረው፡፡ የኑሮ ውድነቱ ትከሻን ከማስጎበጥ አልፍ የስንቱን ህይወት ቀጠፈ? እኛ ኢትዮጵያዊያን ደሰታችን እና ሀዘናችን ከፈጣሪ ጋር የተቆራኘ ነው፤ ይህን እንጂ የአገዛዙ ሥርዓት የለየለት አምባገነን መሆኑ የሚያመላክተው በሃይማኖት ላይ የሚያደርገው ቀጥተኛ ጣልቃ ገብነት እና ያስከተለው ቀውስ ጭምር ነው፡፡ ለሃይማኖት እና ለታሪክ ግድ የማይሰጠው ገዥው መንግስት በዜጎች መካከል ማህበራዊ ቀውስ በመፍጠር ያለተረጋጋ ማህበረሰብ እንዲኖር ያልተደረገ ነገር ምን አለ ? መሬት ቆርሶ መሸጥ የዕለት ገቢ ያደረገው መንግሰት በተለያየ የአገራችን ክፍል ምትክ መሬት ወይም ተገቢውን ካሳ ሳይሰጣቸው የተፈናቀሉ እና ለከፋ ችግር የተጋለጡ ቤት ይቁጠራቸው፡፡ በመሆኑም እነዚህ እና መሰል በደሎች በመንግሰት አማካኝነት ያልተፈፀመበት ማነው ?፡፡ ከተገፉ እና ከተበደሉ ጎን ላለመቆም መወሰን ምንም አልተነካውም የሚለው ነገ ላለመነካቱ ምን ማረጋገጫ አለው ፡፡እርግጥነው የስርዓቱ ቀጥተኛ ተጠቃሚ የሆኑ ጥቂት ግለሰቦች እና ሆድ አደሮች ለህዝባዊ ህንቢተኝነት የወንዝ ዳር ሙጃ ሣራ መሆናቸው አይቀርም ፡፡

በመሆኑም ጥገናዊ ለውጥ የሚያመጣ የመንግሰት አስተዳደር ሳይሆን የስርአት ለውጥ ለመፍጠር የሚያስችል ሁሉን አቀፍህ ዝባዊ እንቢተኝነት በሠላማዊ መንገድ ተግባራዊ ማድረግ እንደ-ዜጋ የመኖር ወይም ያለመኖር ምርጫም ጭምር ነው፡፡ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ከግዴለሽነት እና ምን-ያገባኛል ስሜት ተላቆ በገዥው መንግሰት ላይ “ስልጣን የህዝብ ነው!” ከማለት ባለፍ የስልጣን ባለቤት ለመሆን የሚያስችል ቁጭት አዘል ዝግጅት ስለመኖሩ ብዙ አመላካች ነገሮች አሉ፡፡ ስለሆነም ዓለም አቀፍ ተሞክሮ ያለው የአገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ግምት ውስጥ በማስገባት ፣ እጅግ በጣም ሰላማዊ የሆነ መሪ እና ተመሪ ያለው ጠንካራ ስትራቴጂ በመንደፍ ህዝባዊ ህንቢተኝነት ለነፃነት እና ለፍትህ ተግባራዊ ማድረግ ይቻላል፡፡

እንዲህ አይነቱ ህዝባዊ እንቢተኝነት በሁለት መንገድ የሚፈፀም ነው፡፡ የመጀመሪያው ዜጎች በራሳቻው ፍቃድ ተነሳሽነት በሚፈጥሩት ተቋማት የሚመራ ሲሆን፡፡ በአገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ነፃ ማህበራዊ ተቋም ስለመኖሩ እና ይህን ስለማስፈፀማቸው እርግጠኛ ለመሆን አይቻልም፡፡ ሌላው ደግሞ በፖለቲካ ፓርቲዎች አማካኝነት ነው፡፡ ይህ ደግሞ አሁን ባለው የተቃዋሚ ፓርቲዎች ከተለመደው እና ውጤቱ በግልፅ ካልታወቀበትና ካልተመዘነበት የቅርብ ጊዜ የተቃውሞ ሰልፍ ልምድ ጋር ሲነፃፀር አዲስ ምዕራፍ ነው፡፡ ሆኖም ግን ለ8 ዓመታት የተዘጋው የተቃውሞ ሰልፍ በሰማያዊ ፓርቲ ፈር-ቀዳጅነት አደባባይ ወጥተን ድምፃችን ለማሰማት መቻላችን ለፓርቲው አድናቆት የሚያሰጥ ነው፡፡ በተጨማሪ የዚህ ፁሁፍ አቅራቢ በመኢአድ እና በአንድነት እንዲሁም በመድረክ አማካኝነት የተካሄዱትን የተለያዩ የተቃውሞ ሰልፎች ያለው አድናቆት እንደተጠበቀ ነው፡፡ ስለሆነም አገር አቀፍ ህዝባዊ እንቢተኝነት በሰላማዊ መንገድ ተግባሪዊ እንዲሆን የፓርቲዎች ፊት አውራሪነት እና አዝማችነት የግድ አስፈላጊ ነው፡፡ በህዝብ የተጣለበትን ሃላፊነት የሚወጣ እና የተለያ የሰላማዊ የትግል ዜዴዎችን ተግባሪዊ የሚያደርግ ጠንካራ የተቃዋሚ ፓርቲ የምናይበት ወቅት እርቁ እንደማይሆን ተስፋ አደርጋለው ፡፡
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር !!!

No comments: