Saturday, September 13, 2014

በቦረና ዞን ነዋሪ የሆኑት አቶ ጎንፋ አበራ ከፖሊስ በተተኮሰ 4 ጥይት ሕይወታቸው አለፈ

September 13,2014
አስከሬኑ ሽኝት ላይ የነበሩ የአባያ ገላና ወረዳ ሰብሳቢ አቶ በድሉ መንግሥቱ በፖሊስ ተደብድው በእስር ላይ ናቸው
(ፍኖተ ነፃነት) በቦረና ዞን ገላና ወረዳ ቶሬ ከተማ ነዋሪ የሆኑት አቶ ጎንፋ አበራ ጳጉሜ 4 ቀን 2006 ዓ.ም በግምት ከምሽቱ 3፡00 ሰዓት ላይ ወታደር ዋቆ ሁቃ በተባለ ፖሊስ በተተኮሰ 4 ጥይት ህይወታቸው ማለፉን የቦረና ዞን የአንድነት አስተባባሪ አቶ ጌታቸው በቀለ ለፍኖተ ነፃነት ገለጹ፡፡ የአቶ ጎንፋ አስከሬን ወደ ቶሬ ከተማ ጤና ጣቢያ ተወስዶ ሐሙስ መስከረም 1 ቀን 2007 ዓ.ም ከቀኑ 6፡00 ሰዓት ቤተሰባቸው ወደሚገኝበት አምቦ ከተማ ሲሸኝ የቶሬ ከተማ ነዋሪዎች አሸኛኘት ያደረጉ ሲሆን የአባያ ገላና ወረዳ ሰብሳቢ የሆኑት አቶ በድሉ መንግሥቱ ከሽኝቱ ሲመለሱ በፖሊስ ተይዘው ድብደባ ከተፈጸመባቸው በኋላ በእስር ላይ መሆናቸውን አስተባባሪው ገልጸዋል፡፡ አቶ በድሉ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል በመሆናቸው ብቻ በተደጋጋሚ በገዢው ፓርቲ ካድሬዎች ድብደባና እስር ይፈጸምባቸው የነበረና ባሳለፍነው ዓመትም ይሰሩበት የነበረ የግል ታክሲያቸውን በድንጋይ የሰባበሩባቸው ሲሆን አቶ በድሉና በአካባቢው ያሉ የፓርቲው አባሎች ግን እየደረሰባቸው ያለው ዛቻ፣ ማስፈራሪያና እስር ከትግሉ ፈቀቅ እንደማያደርጋቸው ሰላማዊ ትግሉንም አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል፡፡ ወደ ቶሬ ወረዳ ፖሊስ ደውለን ሁኔታውን ለማጣራት ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም፡፡
Car ethiopiaCar ethiopia1

No comments: