Sunday, September 7, 2014

የብኣዴን ካድሬዎች ራሳቸውን ከሕወሓት የበላይነት ማላቀቅ አለብን የሚል ዘመቻ ጀመሩ።

Sep 6/2014
ዘላለማችንን የፖለቲካ የበታችነት የተጠናወተን ጥገኞች ሆነናል::


ምንሊክ ሳልሳዊ እንደዘገበው በባህር ዳር ካለፈው ሳምንት ጀምሮ እየተካሄደ ያለው የብአዴን ካድሬዎች እና የለውጥ ሃዋርያ ብሎ ራሱን የሚጠራው የወጣት አባላት ቡድን በድርጅቱ ውስጥ ያገረሸውን የለውጥ ጥያቄ ተከትሎ በብኣዴን ውስጥ እየተነሳ ስላለው የፖለቲካ መብት ጥያቄ በሰፊው ውይይት የተደረገበት ሲሆን ብአዴን የኢሕኣዴግን መርሆ እንደጠበቀ ከሌሎች ድርጅቶች የበላይነት እና ጥገኝነት መላቀቅ አለበት በሚሉ እና ወደ አመራር የመጡ በትግሉ ያልተሳተፉ ግለሰቦችን አደርባይነት አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን አጽንኦት ሰጥተው ተወያይተውበታል::

የባህር ዳሩ ስብሰባ እንዲሁም ያዝ ለቀቅ እየተደረገ ያለው የክልል ከተሞች የብአዴን ካድሬዎች ስብሰባ በድርጅቱ መካከል መከፋፈልን ለመፍጠር እና አለመተማመንን ለማንገስ እንዲሁም ጥላቻን ለማስፋፋት የታቀደ ነው ሲሉ ካድሬዎቹ ይናገራሉ፤ የብአዴኖች በቡድን እየተከፋፈሉ በተለያዩ አጋጣሚዎች መገናኘት እና መሰብሰብ ለሕወሓት ድንጋጤን የፈጠረ መሆኑን ውስጥ አዋቂ ምንጮች ተናግረዋል:: በፖለቲካ ጥቃት ከድርጅቱ የተገለሉ የቀድሞ አባላት ከድርጅቱ ካድሬዎች ጋር መገናኘታቸው እና ወዳጅ መሆናቸው ለሕወሓት እንዳልተዋጠለት ታውቋል።

ብኣዴን ከፍተኛ የስልጣን እርከኖች ላይ ለምን አይቀመጥም? የጦር ሰራዊቱ በአንድ ብሄር ተወላጆች የበላይነት ተቀፍድዶ ተይዟል በትግሉ ትንሽ እና ትልቅ ሳይባል ብኣዴን መስእዋትነት ከፍሏል ;; ብኣዴን ስሙ የተቀየረው የኢሕዴንን ታሪክ ለማኮላሸት እና ኢሕዴን የሚለውን ስም ከገበሬው እና ከክልሉ ለማጥፋት የተሸረበ ሴራ ነው እንጂ ለአማራው የታዘነ ጉዳይ አይደለም የሚሉ አስተያየቶች የተደመጡ ሲሆን ዘላለማችንን የፖለቲካ የበታችነት የተጠናወተን ጥገኞች ሆነናል እንዳሉ ተጠቁሟል::

የብአዴን ውይይት ያተኮረበት የፖለቲካ የበላይነት በዝርዝር የቀረበ ሲሆን የትግል አቅጣጫዎችን ለምን በራሳችን አንቀይስም የሚል ጥያቄ ሳይቀር እንደተካተተበት ሲታወቅ የስልጣን ክፍፍል የክልልሎች የልማት ስኬት እና ከጀርባ የፖለቲካ ውኪሎች ሙስና እና ጫና ለክልል ልማቶች እንቅፋት እንደሆነ በዝርዝር ተቀምጧል::እንዲሁም በሙስና ስም ስለሚታፈኑ የድርጅቱ አባላቶች የተነሳ ሲሆን እነማን ናቸው በከፍተኛ ደረጃ በሙስና የተዘፈቁት የሚሉ ጥያቄዎችም እንደተነሱ ታውቋል::እንደዚህ አይነት ነጥቦች ካሁን በፊትም ተነስተው ተድበስብሰው እንዲታለፉ የተደረገ እንደነበር ተሰብሳቢዎች የተናገሩ ሲሆን አሁን ግን መልስ ሊሰጥባቸው ይገባል ሲሉ በአንክሮ ተናግረዋል።

No comments: