Wednesday, September 3, 2014

የሸዋስ፣ ሃብታሙ እና ዳንኤል ተጨማሪ 28 ቀን ተቀጠረባቸው

Sep3,2014
• ‹‹2 ጊዜ 28 ቀን ሲቀጠርባቸው ምንም ሳትሰሩ ነው የመጣችሁት›› ጠበቃ ተማም
Habtamu abrhayeshiwas daniel






የሸዋስ አሰፋ፣ ሀብታሙ አያሌውና ዳንኤል ሺበሽ ተጨማሪ 28 ቀን ተቀጠረባቸው፡፡ ታሳሪዎቹ ዛሬ ጠዋት 3፡30 ላይ በአራዳ ምድብ ችሎት እንደሚቀርቡ ተነግሮ የነበር ቢሆንም ቀጠሮው ተቀይሮ 8፡30 ላይ በቀረበው ችሎት ‹‹ተጨማሪ መረጃ ለማሰባሰብ›› በሚል ተመሳሳይ ምክንያት 28 ቀን ተቀጥሮባቸዋል፡፡ መስከረም 22/2007 ዓ.ም ይቀርባሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም ጠበቃ ተማም አባ ቡልጉ ገልጸዋል፡፡
ችሎቱ ወደ ከሰዓት የተዛወረበት ምክንያት ‹‹ዳኛ ስላልነበረ ነው›› የተባለ ሲሆን ችሎቱን ለመከታተል የአውሮፓ ህብረትና ሌሎች ተወካዮችን ጨምሮ በርከት ያለ ህዝብ ቢገኝም ቤተሰብም ጭምር ችሎቱን መከታተል ሳይችል ቀርቷል፡፡ ለዚህም የተሰጠው ምክንያት ‹‹ችሎቱ በጽ/ቤት የተካሄደ በመሆኑ ተመልካች አይይዝም›› የሚል መሆኑን ጠበቃ ተማም ገልጸዋል፡፡
ጠበቃ ተማም አባ ቡልጉ ቀጠሮውን አስመልክቶ ‹‹እስካሁን የምታቀርቧቸው ምክንያቶች ተመሳሳይ ናቸው፡፡ 2 ጊዜ 28 ቀን ሲቀጠርባቸው ምንም ሳትሰሩ ነው የመጣችሁት፡፡ አሁንም ተጨማሪ 28 ቀን ተቀጥሮባቸዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ደንበኞቼ እየተጉላሉ ነው፡፡›› በሚል ውሳኔውን መቃወማቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተጨማሪም ጠበቃው ታሳሪዎቹን ከቤተሰብ ውጭ ማንም እንዳይጠይቃቸው እየተደረገ መሆኑን በመግለጽ ቅሬታቸውን ያቀረቡ ሲሆን ዳኞቹ እንደተለመደው ‹‹በሌሎች ዘንድም ሊጠየቁ ይገባል›› የሚል ትዕዛዝ እንደሰጡ ታውቋል፡፡ ጠበቃ ተማምም በበኩላቸው ‹‹ፍርድ ቤት ሁል ጊዜም ትዕዛዝ ይሰጣል፡፡ ግን ተግባራዊ ሲሆን አይታይም፡፡›› ሲሉ ፍርድ ቤቱ የሚሰጠው ትዕዛዝ ተግባራዊ እንዲሆን ጠይቀዋል፡፡
ምንጭ ነገረ ኢትዮጵያ

No comments: