Sunday, September 21, 2014

የወያኔውን የከፋፍለህ ግዛ ስርዓት ለመጣል በአንድነት እንነሳ!!!

Septenber21,2014
ዛሬም እንደ ትናንቱ ምንም የማያውቁ ህጻናት ዋይታ!!! የሴቶችና አረጋዊያን ሌላ ዙር መፈናቀል! ሌላ ዙር የጅምላ ስደት መራር መርዶ ከወደ ጋምቤላ
የግጭቱ ስረ መሰረት እንዲህ ነው። የህወሓት አገዛዝየአካባቢውን ማኅበረሰብ በማፈናቀልና ለም መሬታቸውን ቀምቶ በኢንቨስትመንት ስም ባብዛኛው ካንድ አካባቢ ለመጡ የወያኔ አባላት ቀደም ሲል ለሰሩት ወንጀል ማካካሻ እንዲሆን ታስቦ ካቅማቸው በላይ ቸራቸው። እነሱም ያለምንም ይሉኝታና ያካባቢውን ማኅበረስብ ያኗኗር ሁኔታ በጭራሽ ከግምት ሳያስገቡ ጌታዋን እንደተማመነች በግ ያካባቢው ማኅበረሰብ ለዘመናት ሲወርድና ሲዋረድ ጠብቆ ያቆየውን ጥብቅ ደን እየመነጠሩ የጣውላና የከሰል ንግድ ላይ ተሰማሩ።
የአካባቢው ማኅበረሰብ ግን የበይ ተመልካች ሆነ፣ ቅሬታውን ለባለስልጣናት አቤት ቢልም ሰሚ አላገኘም። ጭራሽ ይባስ ብለው በቀየው የተገኘውን ሴት ወንድ ሳይመርጡ በፌደራል ፖሊስ በመቀጥቀጥ ብዙዎችን ለሞት ሲዳርጓቸው ሌሎችን ደግሞ ቁስለኛ አድርገዋል። ከሞትና ከመቁለት የተረፉትም ተፈናቅለው ዱር ገደሉን ቤታቸው አድርገዋል። በሌላም በኩል የግጭቱ ሰለባ የሆኑት ከሌላ ክልል መጥተው ለረዝም ጊዜ ባካባቢው ኑዋሪ የሆኑ ኢትዮጵያዊን ዜጎችም የግጭቱ ሰለባ ከመሆነ አልተረፉም ፣እነሱም ሞትና ቁስለኛ ሆነዋል። ከሞትና ከመቁሰልም የተረፉት በቴፒ ከተማ አውላላ ሜዳ ላይ ተበትነው ምንም የማያውቁ ሴቶችና ህጻናት ቀን በጸሀይ ሌሊት በቁር እየተጠበሱ ይገኛሉ። እጅግ የሚያሳዝነው ግጭቱን የሚባብሱትና በዋና ተዋናይነት የሚተውኑት የወያኔው ቅጥረኞች የሆኑ የአካባቢ ካድሬዎችና መሬቱን ያላግባብ የቀሙ ያንድ አካባቢ ተወላጆችና ያንድ አካባቢ የፌደራል ፖሊስና የመከላከያ የበላይ ሹማምንት መሆናቸው ነው።
እንዲህ ዓይነቱ የወያኔ ሴራ ዛሬ የተጀመረ አዲስ ክስተት አይደለም። ህወሓት ገና ከመጀመሪው ሲፈጠር አብሮት የነበረና ላለፉት ሃያ ሶስት ዓመታት የቀጠለ እዳ ነው። ይህ ህወሓት ኢትዮጵያዊያንን እርስ በራስ በማጋጨት ለዘመናት ለመግዛት አስቦና አልሞ የተነሳበትና ከኢጣሊያን ቅኝ ገዝ የተማረው ስልት ነው፤ ይህ የህወሓት ባንዳነት ውጤት ነው።
ባለፉት አመታት በጉራ ፈርዳና በቤንሻንጉል ክልል የተፈናቀሉትን ኢትዮጵያዊን ለዘመናት ከኖሩበት ስፍራ ሲፈናቀሉ ያየነውም ይህንኑ የፋሽስታዊ ስርዓታቸው መገለጫው የሆነውን ዘር ለይቶ ማፈናቀልና ማሳደድን ነው።
በጋምቤላ ክልል በሜጢ ከተማና አካባቢው የንጹሀን ዋይታና ሰሚ ያጣ ጩኸት ሁላችንንም፤ ማለትም ኢትዮጵያዊያንን ሁሉ በእጅጉ ሊያሳስበንና ይገባል። በቶሎ ባንድነት ተረባርበን ካላስቆምነው መዘዙ የምንወዳት ሀገራችንን እንዳልነበረች ሊያደርግ የሚችል አደገኛ ሁኔታ ነው።
ግንቦት 7 የፍትህ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ይህንን ተገነዝቦ ስርዓቱን በሁለገብ ትግል ለመስወገድ ወሳኝ ምዕራፍ ላይ ይገኛል፣ በመሆኑም የህዝብ ወገኖች በሙሉ ትኩረታችንን ወያኔ ላይ ብቻ እናድርግ። የወያኔን ከፋፍለህ ግዛ እምቢ በማለት ስርዓቱን ከጫንቃችን አውርደን ለመጣል በሚደረገው ትግል ላይ እንድንረባረብ ግንቦት 7 ጥሪውን ያቀርባል።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!

No comments: