Monday, September 22, 2014

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለስራ አጦች በየቤታቸው ለማባበያ ካርድ እያደለ ነው

September 22,2014
• ‹‹ምርጫ ሲደርስ የሚደረግ ነው››
• ‹‹ለኢህአዴግ ጥላቻ አለሽ በሚል አንመዘግብም ብለውኛል››

ነገረ ኢትዮጵያ እንደዘገበው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሴክተር ለስራ አጦች ‹‹ስራ እንሰጣችኋለን›› በሚል በየቤታቸው የስራ ፈላጊዎች መለያ መታወቂያ ካርድ እያደለ መሆኑን የነገረ ኢትዮጵያ ምንጮች ገለጹ፡፡
የስራ ፈላጊዎች መለያ መታወቂያ ካርዱ የሚሰጠው የተማረም ሆነ ያልተማረ እስከ 60 አመት እድሜ ለሚገኝ ማንኛውም ስራ አጥ ነው እንደተባለ ታውቋል፡፡ በሌላ በኩል ከዩኒቨርሲቲ የተመረቁት አዲስ ተማሪዎችና ከአሁን ቀደም ተመርቀው ስራ ያላገኙ ተማሪዎች ‹‹ቀበሌ መጥታችሁ ተመዝገቡ›› እንደተባለ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ካርድ የተሰጣቸው ነዋሪዎች የመዘገቧቸው ሰዎች ‹‹ስራ እንሰጣችኋለን፤ ተከታታይ ስብሰባ ስላለ ስራ ለማግኘት ስብሰባውን መሳተፍ ይጠበቅባችኋል›› እንዳሏቸው ገልጸዋል፡፡ካርዱ ከተሰጣቸው መካከል ያልተማሩም የሚገኙበት ሲሆን በተለያየ መስክ በዲግሪ ተመርቀው ስራ ያጡ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ጨምሮ በርካታ ስራ አጦች እንዳሉ በመጠቆም ስራ የማግኘት ተስፋቸውን እንዲገልጹልን የጠየቅናቸው ነዋሪ ‹‹ስራ እንሰጣችኋለን ብለዋል፤ ከሰጡን ማየት ነው፡፡ ግን ለምርጫ ሳይሆን አይቀርም›› ሲሉ ጥርጣሬያቸውን ገልጸዋል፡፡
በተመሳሳይ ከአሁን ቀደም በቤተሰብ ደረጃ 1ለ5 ተደራጁ ተብለው ሳይደራጁ የቀሩ የቤት እመቤት ‹‹ከአሁን ቀደምም በቤተሰብ ደረጃ 1ለ5 እንድንደራጅ ተጠይቀን ነበር፡፡ አልተደራጀንም፡፡ ምን አልባት ያ አልሰራ ሲል ይሆናል፡፡ ያው ምርጫ ሲመጣ ብዙ ነገር ይመጣል›› ሲሉ የተሰጣቸው ካርድ የምርጫ ማባበያ ሊሆን እንደሚችል ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡በሌላ በኩል ለገዥው ፓርቲ አሉታዊ አመለካከት አላቸው የሚባሉ ዜጎች እንዳይመዘገቡ የተደረገ ሲሆን እንድትመዘገብ በተጠየቀችበት ወቅት ‹‹ካርዱን ተቀብለን ስንሰበሰብ አባል እንድንሆን አትጠይቁንም?›› የሚል ጥያቄ በማንሳቷ ‹‹ለኢህአዴግ ጥላቻ አለሽ፡፡ አንመዘግብሽም›› እንደተባለች ገልጻለች፡፡
ምንም እንኳ መዝጋቢዎቹ ‹‹ሊስትሮም ቢሆን ስራ ካለው እንዳትመዘግቡ›› መባላቸውን የሚገልጹ ቢሆንም ሱቅና በመሳሰሉት የንግድ ስራዎች የተሰማሩ ዜጎች ‹‹ስራ አጥ›› ተብለው እየተመዘገቡ ይገኛሉ፡፡ ይህም ስራ ከመስጠት ይልቅ ለምርጫ ለማባበልና መረጃ ለመሰብሰብ ሊሆን እንደሚችል ካርድ የተሰጣቸው ነዋሪዎች ለነገረ ኢትዮጵያ ተናግረዋል፡፡

No comments: