Monday, June 30, 2014

ጊዜ የማይሠጥ ሀገራዊ ጥሪ አለብን!

June30/2014
እስከመቼ ባለንበት እንረግጣለን?
eskemechie


ራሱን “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” ብሎ የሰየመው ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት (ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት)፤ ሀገራችንን ዕለት ከዕለት ወደ ባሰ አዘቅት እንድትገባ እየጎተታት ነው። የፖለቲካ ፍልስፍናውና የአስተዳደር መመሪያው የሀገራችንን ሕልውና በንጥልጥል ላይ እንዲቀመጥ ሌት ከቀን እየጣረ ነው። በአንፃሩ ደግሞ ለኢትዮጵያዊያንና ለኢትዮጵያ በመቆም፤ በተለያዩ ድርጅቶች ከፍተኛውን መስዋዕትነት በመክፈል፤ ከዚህ ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት ጋር እየተዋደቁ ያሉ ታጋዮች አሉ። ይህ በዚህ ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥትና በኢትዮጵያ ሕዝብ መካከል እየተደረገ ያለው ግብግብ፤ ለረጅም ዘመን እንዳለ ሆኖ፤ ፀረ-ኢትዮጵያዊው መንግሥት የፈለገውን እያደረገ ያለበትና፤ በታጋዩ ወገን ያለው ክፍል ደግሞ ላለፉት ፳ ፫ ዓመታት ባለበት የሚረግጥበት ሁኔታ አልተለወጠም። ከጊዜ ወደ ጊዜ ይህ ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት የሚጠናወተው ክፍል እየበዛ፤ በአሁኑ ሰዓት ሀገሪቱ ይኼው ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት ሊቆጣጠረው በማይችልበት ቀውስ ውስጥ ልትገባ አዝምማለች። ከዚህ እንድታቀና ሁላችን እንፈልጋለን። ይኼን ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት ማስወገድ ሁላችን እንፈልጋለን። እስካሁን የደከምንባቸው መንገዶች ውጤታቸው አመርቂ ስላልሆነ፤ አዲስ መንገድ መቀየስ አለብን። የሀገራችን ችግርና መከራ፣ በምኞት አይቀረፍም። ይህ በትግላችን የሚከናወን ነው። ይኼን ለማሳካት እንዴት እንደምንበቃ ምርጫ የሌለው አንድ መንገድ አለን። ሁላችን እናውቀዋለን፤ ኢትዮጵያዊያን በአንድነት ተነስተው ሀገራችን እያሉ እንደሆነ ሁሉ፤ እኛም በያለንበት ለኢትዮጵያዊያን ከጎናቸው ቆመን፤ ሀገራችንን አስቀድመን፣ በአንድ ተሰልፈን መነሳት ነው። የዚህ መንገድ ጠቃሚነቱ፤ ፀረ-ኢትዮጵያዊውን መንግሥት ማስወገዱ ላይ ብቻ ሳይሆን፤ ቀጥሎ ለምትመሠረተው ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ አስተማማኝ መሆኑ ነው። በዚህ ሂደት ሁሉም ድርጅቶች ባለቤቶች ናቸው። በዚህ ሂደት እያንዳንዷ ኢትዮጵያዊት ባለቤት ናት። በዚህ ሂደት እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ባለቤት ነው። ትኩረቱ፤ በሚሰቃየው ወገናችን፣ የጋራችን በሆነችው ሀገራችን፣ እና በጠላታችን ፀረ-ኢትዮጵያዊው መንግሥት ላይ ነው። ይህ የጋራችን ፈተና ነው። ማናችንም ከዚህ ውጭ አይደለንም። ከሀገር መለስ ብዙ የምንለያይባቸው ጉዳዮች አሉ። ነገር ግን ክብደታቸው ከሀገር ነፃነት ጋር ሲነፃፀር፤ ሁለተኛ ደረጃን የያዘ ስለሆነ፤ ቅድሚያን ለሀገር እንድርግ። በመካከላችን ያለው ልዩነት የዴሞክራሲያዊ አሠራርን የሚጠይቅና በዚያው መንገድ የሚፈታ ነው። የዚህ ጽሑፍ ዓላማ፤ ከተለያየ ቦታና የተለያየ ተመክሮ ያለን ግለሰብ ኢትዮጵያዊያን፤ ከድርጅት አባል መሆን አለመሆን ይልቅ፤ የወገናችንን ብሶት ማስወገድና የሀገራችንን ሕልውና ማስጠበቅን በማስቀደም፤ በአንድነት በመቆም፤ የትግሉን ሂደትና መደረግ ያለበትን ተረድተን፤ በሀገራዊ ጥሪው ሁላችንም ኢትዮጵያዊያን እንድንሰባሰብ ነው። ይህ ብዙዎቻችንን ያሰባስባል። ይህ በአንድነት ለተግባር ያሰልፈናል። ይህ፤ የምናደርገው ጥረት ለሀገራችን መሆኑን ያረጋግጣል። ይህ በፍጥነትና በተጠናከረ ጉልበት ለወገናችን እንድንደርስ ያደርገናል።
ውድ አንባቢ፤
በሀገራችን ላለው የፖለቲካ ውጥንቅጥ፤ ላንዴና ለመቼውም መፍትሔ ለማስገኘት የመጨረሻው ደወል ተደውሏል። ሀገራችን ስላለችበት የፖለቲካ ሀቅ እርስዎም ሆነ እኔ ነጋሪ አያስፈልገንም። ኢትዮጵያዊያንን ለረጅም ዘመን አቆራኝቶ የያዘንን የኢትዮጵያዊነት ትስስር ለመበጣጠስ የተነሳን ድርጅት፤ በምንም መመዘኛ ብንለካው ፀረ-ኢትዮጵያዊ ከመሆኑ ሌላ፤ ምንም ገላጭ ቃል አይገኝለትም። በመካከላችን ያለውን አንድነት ሰብሮ፤ እርስ በርሳችን በጥርጣሬ እንድንተያይ ያደረገን፤ ይኼው ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት ነው። ሀገራችንን እየገዛ ያለው ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት፤ ሀገራችንን እየወሰዳት ያለበት አዘቅት፤ አደገኛና መመለሻ የሌለው ነው። ዴሞክራሲያዊነት፣ ፍትኅን አክባሪነት፣ ለሕዝብ ተቆርቋሪነት፣ ለድሃ ቋሚነት፣ ሀገር ወዳድነትና ለሕግ ተገዥነትን የወደደ፤ የትውልድ ቆጠራን ከውሉ አያስገባም። እኒህ፤ ተግባራዊ ለማድረግ ፍላጎት ባላቸው ግለሰብ ኢትዮጵያዊያን እጅ ያሉ ጥበቦች ናቸው። ከተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች የተገኘን ወገኖች፤ በምን መንገድ ተለያይተን ልንተያይ ነው? ኢትዮጵያዊ ብለን በእኩልነት ካልተቀባበልን፤ መበታተኑ ማንን ነው የሚጠቅመው? የየተንገንጣዩ ልሂቃን ሥልጣን ይዘው የገነጣጠሉንን ወገናቸውን ለመግዛትና ኪሳቸውን ለማሳበጥ ከመሯሯጥ ውጪ፤ ለኛ ለተራ ግለሰቦች ምን ሊያስገኙልን ይችላሉ? ዴሞክራሲ ለየብቻ ስንሆን ብቻ ነው የሚሠራው ያለው ማነው? ትናንት በኤርትራ የደረሰውን ለምን እንረሳለን? አሁንም የተያዘው ጉዞ፤ ሀገሪቱ አንድነት አጥታ መገዛት የማትችልበት ሁኔታ እንዲፈጠርና፤ ስግብግብ የሥልጣን ጥመኞች ተጠቃሚ የሚሆኑበትን ሁኔታ ለመፍጠር ነው። በሀገራችን ያለውን የጨቋኝና የተጨቋኝ ጉዳይ “የብሔር ጥያቄ ዋነኛው የሀገራችን ቅራኔ ነው” ብሎ የተነሳው ይሄ ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት፤ ይህ ቅኝቱ አሁን ሀገራችን እንደ አንድ ሀገር እንዳትቆምና ሕዝቧም እንደ ኢትዮጵያዊነቱ ሕልውናውን እንዲያጣ ቀን በመቁጠር ላይ ነው። ለሥልጣን መወጣጫና በሥልጣኑ መስንበቻ የቀመረው ጉዳይ፤ አድሮ በራሱ ላይ ተጠምጥሞ መታነቂያው ሆኗል። በየክልሉ ያሉ የተለያዩ ኢትዮጵያዊያን እንዲፈጠሩ ያሰላውና የየክልሉ ነዋሪዎች፤ ሌሎችን “መጤዎች” በማለት እንዲያባርሩ ያፋፋመው ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት፤ ኢትዮጵያን ወደ ማጥፋቱ አምርቷል። በአንፃሩ ግን፤ ኢትዮጵያዊያን ከሰሜን እስከ ደቡብ፤ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ ሀገራችን አንድ ናት ብሎ ተነስተዋል።
በኢትዮጵያ ውስጥ የሚካሄደው የፖለቲካ ጉዳይ፤ ከጀርባው ኢትዮጵያን ለማጥፋት በደንብ የተቀመረ እርምጃና አራማጅ አለው። ይህ በፀረ-ኢትዮጵያዊው መንግሥት የሚተገበረው ጥፋት፤ ከጀርባው የውጭ ሀገር እጅ ያለበት ለመሆኑ ማናችንም ጥርጥር ሊኖረን አይችልም። በፖለቲካ ምንም ነገር ለብቻው የሚሄድ የለም። በምንም መንገድ የውጭ ሀገር መንግሥታት ለኢትዮጵያዊያን ጥቅምና ለዴሞክራሲ ይቆማሉ ብለን ማሰብ የለብንም። እነሱ የቆሙት ለሀገራቸው ጥቅምና ከኛ የሚያገኙትን ጥቅም ለማብዛት ነው። ከአሜሪካ አንስቶ እስከ ኤርትራ ድረስ፤ ለዴሞክራሲ ወይንም ጠንካራ ኢትዮጵያን ለመመሥረት የቆመ የለም። ባለቤቶችም ሆን ባለዕዳዎቹ፤ ታጋዮችም ሆን አሳልፎ ሠጪዎቹ፤ እኛው ነን። የኢትዮጵያን መንግሥታዊ ሥልጣን በውጭ መንግሥታት ፈቃድና ቡራኬ ለመቀበል የተዘጋጁ የድርጅቶች መሪዎች፤ ምን ያህል ሀገር ወዳድ ናቸው? የውጪ ሀገሮች አደግዳጊ የሆነ ቡድን በሀገራችን የሥልጣን ወንበር ከተቀመጠ፤ አሁንም ፖለቲካችን እንቧለሌ ዙሪያ ነው የሚሆነው፤ ወጣቶቻችንን ለጦርነት፣ የሀገራችንን ሀብት ለጥቂት ግለሰቦች፣ ድህነትና ረሃብን ለወገናችን ማውረስ ነው። የአክራሪዎች (ቴረሪስት) ተግባር የኢትዮጵያዊያን የፖለቲካ ችግር አይደለም። የአሜሪካ ችግር ነው። የኛ ችግር ፀረ ኢትዮጵያ መንግሥት በላያችን ላይ መጫኑ ነው።
የምንታገለው ለሚከተሉት የትግል ዕሴቶቻችን ነው፤
ሀ) የኢትዮጵያ ሕዝብ ሉዓላዊነቱ ተከብሮ፤ ሕዝቡ የኢትዮጵያ መንግሥት ባለቤትነቱ እንዲረጋገጥ፤
ለ) ሀገራችን ኢትዮጵያ አንድነቷ ተጠብቆ፤ ለሙ መሬቷና ዳር ድንበሯ ለኢትዮጵያዊያን እንዲሆን፤
ሐ) በሀገራችን ኢትዮጵያ፤ በሕዝቡ የጸደቀ ሕግ-መንግሥት ኖሮ የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን፤
መ) የእያንዳንዷ ኢትዮጵያዊትና የእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ የግለሰብ መብት በሕግ እንዲደነገግና በተግባር እንዲገለጥ፤
እነዚህ ናቸው የምንታገልላቸው። እኒህ ደግሞ በማንኛውም ታጋይ ደርጅት ዘንድ ተቀባይነት አላቸው። በተግባር ላይ እንዲውሉ ደግሞ እያንዳንዱ ግለሰብ ኢትዮጵያዊና ኢትዮጵያዊ ድርጅት የኔ ብሎ መነሳት አለበት። ሀገራችንን ከዚህ ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት ለማስለቀቅ በሚደረገው ትግል፤ በዚህ መለስተኛ በሆነው ሀገራዊ ጥሪ ለመሰባሰብ፤ የተለያዩ ድርጅቶች መኖራቸው ወይም አዳዲስ መፈጠራቸው አስፈላጊ አይደለም። ይልቁንስ የሚያስፈልገው ሁላችንም ወደ አንድ የምንመጣበት መንገድ ነው። አሁን በታጋዮች ወገን ያለው ሀቅ አያኮራም። ከአንደኛው የፖለቲካ ዝማሜ እስከሌላው ጫፍ ድረስ ተዘርግቶ ያለው የፖለቲካ ድርጅቶች ስምሪት፤ የፖለቲካ ማኅደሩን ከማጨናነቅ ያለፈ፤ አመርቂ ውጤት አላሳየም። እናም ሊቀጥል አይገባውም። ከዚህ መውጣት አለብን። ለሥልጣን በመሰለፍ ላይ እግራቸውን የተከሉ ሁሉ፤ የኢትዮጵያን ዘለቄታ ጥቅም ስላላዘሉ፤ ውጤታማ ቢሆኑም፤ ለኢትዮጵያዊያ መልሶ እምቦጭ ነው።
ነገ እንድትመጣ የምንፈልገዋን ኢትዮጵያ፤ በአንድነት ልናረጋግጥበት የምንችለው በዚህ መንገድ ነው። ከሺ ዘጠኝ መቶ ሃምሳ ሶስቱ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራና ከሺ ዘጠኝ መቶ ስድሳዎቹ የተማሪዎች እንቅስቃሴ ጀምሮ እስካሁን ድረስ ያለው ትግል፤ ይኼንኑ የዴሞክራሲ ጥያቄ ነው አንግቦ የዘመተው። ሕዝባዊ ያልሆነ ሥልጣን ያባልጋል። በቀላሉ አይለቀቅም። መንገዱን ሁሉ በማጥበብ ዘለቄታን ይሻል። እናም አምባገነን ነው። መንግሥቱ ኃይለማርያምን ማጥናቱ የበለጠ ያረጋግጣል። ኢሳያስ አፈወርቂን ያየ ሌላ አይሻም። መለስ ዜናዊን ያየ ሌላ መረጃ አይጠይቅም። የሀገራችን ምጣኔ ሀብት ሥምሪት ዘግናኝ ነው። ጥቂቶች ከመጠን በላይ ባለሀብቶችና፤ እጅግ በጣም ብዙዎች መንገድ አዳሪዎች ያሉበት ሀቅ ነው። ሥራ ፈላጊው ቁጥሩ እየጨመረ ነው።
ኢትዮጵያ ውስጥ የሚታገሉ ወገኖቻችን ስንመለከት፤ በየጊዜው በሚለዋወጥ ሕግ እጅና እግራቸው ተፈጥርቆ፤ ይኼን ካደረጋችሁ እንዲህ ትደረጋላችሁ እየተባሉ፤ ከፍተኛውን መስዋዕትነት በመክፈል ይገኛሉ። ሆኖም ግን መሠሪ በሆነው የገዥው ቡድን ተንኮልና የስለላ ድር ተሸብበው እንቅስቃሴያቸው ውስን ሆኗል። ደስ የሚል የትብብር ጅማሬ እየታዬ ነው። ይበርታ እንበል። ሆኖም ግን፤ አሁንም አንድ የሆነ ማዕከል ኖሮ፤ ሁሉም በአንድነት የሚሰለፉበት መንገድ ካልተፈጠረ፤ ከሚገኘው ድል ይልቅ መስዋዕትነቱ እየበለጠ፤ የታጋዩን ቁጥር ለጊዜውም ቢሆን እንዳያሳሳው ያሰጋል። እናም የአንድነት ጥሪው አሁንም መጠንከር አለበት።
በውጭ ሀገር ያለን ኢትዮጵያዊያን ለረጅም ጊዜ በያለንበት ስንታገል ብዙ ዓመታት አሳልፈናል። በአንድነት ሕብረትን ፈጥረን፤ አንድ ሀገር፤ አንድ ራዕይ፤ አንድ ትግል ብለን ካልተነሳን፤ አሁንም ዓመታትን ከመቁጠር ሌላ የረባ ልንሠራ አንችልም። ትግል ሥነ ሥርዓት አለው። ትግል መስዋዕትነት አለው። ትግል ታታሪነትን ይጠይቃል። ትግል ቀጣይነትን ይጠይቃል። ሲያመቸንና ደስ ሲለን የምንቀላቀለው፤ ደስ ያላለን ጊዜ ደግሞ ንቀን የምንተወው ከሆነ፤ የትም አይደርስም። ቆራጥነትን፣ ታታሪነትን፣ አልቸነፍም ባይነትን ይዘን ነው ወደፊት መሄድ የሚገባን። ለዚህ ደግሞ አሰባሳቢና አነሳሽ ራዕይ ያስፈልጋል። ፀረ ኢትዮጵያ መንግሥት በሀገራችን ቆሞ፣ ሕዝቡ ከዕለት ወደ ዕለት ኑሮው እያሽቆለቆለ፣ ጥቂቶች ሀብታቸውን ሽቅብ አጉነው ባለንበት ሀቅ፤ ሀገርን ከዚህ ፀረ ኢትዮጵያ መንግሥት ነፃ ለማውጣት ከታጋዩ ሕዝብ ጎን አብረን መሰለፉ ይገባናል።
አሁን ምን እየሠራን ነው? እያንዳንዳችን መጠየቅ ያለብን ራሳችንን ነው። ዛሬ፣ ትናንት፣ የዛሬ ሳምንት፣ ያለፈው ወር፣ ባለፈው ዓመት፣ ባለፈው አምስት ዓመት ምን ሠራን ብለን ራሳችንን እንጠይቅ? ከዚህ ተነስተን ሌሎች የሚያደርጉትን መገመትና መገምገም እንችላለን። ታዲያ ወገናችንን ማፍቀራችንን እና ሀገራችንን መውደዳችን የት ላይ ነው? እኛስ ካልታገልን ማን ታግሎ ነፃ እንዲያወጣን እንጠብቃለን? በውጭ ያለን ኢትዮጵያዊያን የተለያዩ መድረኮች አሉን። ሃሳቦቻችንን ልንለዋወጥባቸው የሚያስችሉን፤ ድረገፆች፤ የመወያያ ክፍሎች፣ ሬዲዮ ጣቢያዎች፣ ፌስቡክ፣ ትዊተር፣ እና ሌሎችም አሉን። እኒህን በመጠቀም አንድነትን እያራመድን፤ ትግሉን ማጠናከር እንችላለን። ይህ ፍላጎቴ አይሠራም ወይንም ትክክል አይደለም የምትሉ ካላችሁ፤ የናንተን የሚሠራ አቅርቡና ልከተላችሁ። ዋናው ነገር ተግባራዊ ሆነን መገኘታችን ነው።
አዲሲቷን ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ ለማቋቋም ያለው መንገድ፤ በአንድነት ሁላችን ተሰባስበን የምንመሠርተውና የምንቆምለት ድርጅት እየመራን፤ ይኼን ፀረ-ኢትዮጵያ መንግሥት ከሥሩ ስንመነግለው ነው። ጊዜ ባለፈው የአፄው ዘመነ መንግሥት የታጋዮች ጥያቄ፤ የዴሞክራሲ ጥያቄ ነበር። ለዚህም ከፍተኛውን መስዋዕትነት በመክፈል ትግሉን ወደፊት ገፍተውታል። በሰው በላው የመንግሥቱ ኃይለማርያም አምባገነን መንግሥት ዘመን የታጋዮች ጥያቄ የዴሞክራሲ ጥያቄ ነበር። ያንን አረመኔ መንግሥት በማፋጠጥ፤ ከፍተኛ መስዋዕትነትን ከትንሹ እስከ ትልቁ ከፍለው ትግሉን ወደፊት ገፍተውታል። በፋሽስቱ ጣሊያን ወራሪ መንግሥት የታጋዮች ጥያቄ የሀገራችን ነፃነት ነበር። ለሀገር ነፃነት በአንድነት ሁሉም ሀገሬ ብሎ ተነስቶ፤ ለጦርነት ተጉዘው ያልተመለሱ አርበኞቻችን ሀገራችንን ለኛ አትርፈውልናል። በሀገራችን አሁን ያለው መንግሥት የዴሞክራሲ ጥያቄዎችን የምናቀርብለውት መንግሥት አይደለም። ሕግን የሚያከብር መንግሥት አይደለም። እኩልነትን የሚቀበል መንግሥት አይደለም። የሕዝብን ድምጽ የሚያከብር መንግሥት አይደለም። በኢትዮጵያዊነት እየገዛ አይደለም። ፀረ ኢትዮጵያ መንግሥት ነው። እናም እንደፋሽስቱ የምንታገለው መንግሥት ነው። ለፀረ ኢትዮጵያ መንግሥት ደግሞ መልሱ በአንድነት ሀገሬ ብሎ መነሳት ነው። በዚህ ሂደት፤ ብዙ የተለያዩ አጀንዳዎች ሊነሱ ይችላሉ። በቅድሚያ ግን ሁሉም ኢትዮጵያዊያን እና ኢትዮጵያዊ ድርጅቶች ወደ አንድ መምጣት አለባቸው። ጠላታችንን እንዴት እንደምናፈልሰው አንድነት ሊኖረን ይገባል። ከጠላታችን መፍለስ በኋላ መከተል ስላለበት የመንግሥት አመሠራረትና አካሂያድ አንድነት ሊኖረን ይገባል። ይህ ደግሞ ከፍ ባለ ትክክለኛ ተራማጅ ድርጅት መዋቀርና መመራትን ግድ ይላል። ሁሉም ከሀገር መለስ ያሉት ጉዳዮች ከሀገር መዳን በኋላ የሚነሱ ሁለተኛ ጉዳዮች ናቸው። በዚህ ጉዳይ ላይ ከማንም ጋር ለመወያየትና አብሮ ለመነሳት ፈቃደኛ ነኝ። አብሬህ አለሁ በማለት እንድንወያይ የምትፈልጉ በ(eske.meche@yahoo.com ) ጻፉልኝ።

No comments: