Tuesday, July 15, 2014

በኖርዌ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያኖች በእልህና በቁጣ የተሞላ ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ አደረጉ

July 15/2014
ሰኞ ጁላይ 15, 2014 የዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ድርጅት በኖርዌ አዘጋጅነት በኖርዌ ኦስሎ በተለያዩ ከተሞች የሚኖሩ ቁጥራቸው በርከት ያሉ ኢትዮጵያውያኖች በአንድ ላይ በመሰብሰብ ከቀኑ 13፡00 ጀምሮ በአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ የግንቦት 7 የፍትህ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ዋና ፀሃፊ በየመን የፀጥታ ኃይሎች ታፍነው በአምባገነኑ ወያኔ እስር ቤት መታሰራቸውን በመቃወም እና በተጨማሪም አቶ ኦኬሎ አኳይ የኖርዌይ ዜግነት ያላቸውና በኖርዌ ሃገር ይኖሩ የነበሩ የቀድሞው የጋምቤላ ክልል ፕሬዘዳንት ከሱዳን በወያኔ የደህንነት ኃይሎች በግፍ ታፍነው መወሰዳቸውንና በወያኔ እስርቤት ታስረው ለሞት ፍርድ መዳረጋቸውን በመቃወም ድምጻቸውን ሲያሰሙ ውለዋል።

ሰልፈኞቹ መነሻቸውን በኖርዌጅያን የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ያደረጉ ሲሆን በዛው በኖርዌጅያን የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር በመገኘት የወያኔን ህገወጥ አፈና እና እስራት የሚቃወሙ የተለያዩ መፈክሮችን በመያዝና በማሰማት የተቃውሞ ድምጻቸውን አሰምተዋል። በስፍራው የነበሩ ሰልፈኞቹ ሲያሰሟቸው ከነበሩት መፈክሮች መካከል በጥቂቱ ኦኬሎ አኳዮ ይፈታ፣ ኖርዌይ ዜጋሽ ኦኬሎ አኳዮ የት ነው ያለው?፣ ኦኬሎ አኳዮ አሸባሪ አይደለም የሚሉ የተለያዩ መፈክሮች ይገኙበታል ::በማያያዝም ሰልፈኞቹ የኖርዌ መንግስት ለአምባገነኑ የወያኔ መንግስት የምትሰጠውን እርዳታ እንድታቆምም ጠይቀዋል:: በእለቱ የተዘጋጀውን ደብዳቤ የዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ዳንኤል አማካኝነት ለውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ተወካይ አስረክበዋል። ተወካይዋም ደብዳቤውን ከተቀበሉ በኋላ ጉዳዩ ን እንደሚያዩትና ችግሩ አሳሳቢ ከመሆኑም አኳያ በትኩረት እየተከታተሉት እንደሆነ አሣውቀዋል። በመቀጠልም ሰልፈኞቹ በቀጥታ ጉዟቸውን ወደ እንግሊዝ ኢምባሲ በማቅናት ታላቅ እልህና ቁጣ የተቀላቀለበት ደማቅ ሰላማዊ ሰልፍ ያደረጉ ሲሆን በዛው በእንግሊዝ ኢምባሲ ፊት ለፊት በመሆን የተለያዩ መፈክሮችን በመያዝ በታላቅ ጩህትና በስሜት ሲያሰሟቸው ከነበሩት መፈክሮች መካከል Britin were is you citizen, Free Andrgachew Tsige, where is your action, stop discrimination among citizens, we are all Andrgachew Tsige, Brtain dont support terrirost regim in Ethiopia የሚሉት ይገኙበታል::

እነዚሁ በኖርዌ የሚኖሩ ኢትዮጵያ ሰልፈኞች በዚሁ በእንግሊዝ ኢምባሲ ፊት ለፊት በመገኘት ባለፈው ጁላይ 3, 2014 ሰልፍ ማድረጋቸው ይታወሳል::የዛሬው ሰልፍ ከባለፈው ሰልፍ እጅግ በጣም ለየት የሚያደርገው ነገር ቢኖር ሰልፈኞቹ በጠቅላላ እኔም አንዳርጋቸው ፅጌ ነኝ የሚል የአንዳርጋቸውን ምስል የያዘ ቲሸርት የለበሱ ሲሆን ለሰልፉም ድምቀትን በመስጠት ለነጻነት ታጋዩ ለአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ያላችውን ፍቅር በአደባባይ ያስመሰከሩ ሲሆን የተቃውሙ ሰልፉም በሰልፈኞቹ ቁጣና እልህ የተሞላበት እንደነበር ለማየት ተችሏል::ሰልፈኞቹም የያዙትን ደብዳቤ በሰልፉ አዘጋጅ ኮሚቴ ተወካይ በአቶ ዳዊት መኮንን በኩል ለእንግሊዝ ኢምባሲ ተወካይ ያስረከቡ ሲሆነ ተወካይዋም ጉዳዩ እንዳሳሰባቸው፣ በትኩረትና በቅርበት እየሰሩ መሆኑን እንዲሁም አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ነፃ እስኪወጡ ድረስ የተቻላቸውን ሁሉ እንደሚያደርጉና ክትትላቸውን እንደሚቀጥሉ ለሰልፈኛው አሳውቀዋል።

 በመጨረሻም ሰልፈኞቹ በአንድ ላይ በመሆን የግንቦት 7 ህዝባዊ ኃይል መዝሙር ላንቺ ነው ሐገሬ ላንቺ ነው ላንቺ ነው ኢትዮጵያ ላንቺ ነው የሚለውን ህዝባዊ መዝሙር በደማቅና በሀገራዊ ስሜት ዘምረው ዝግጅቱ በተሳካ ሁኔታ ከቀኑ 15፡00 ተጠናቋል።
ሁላችንም አንዳርጋቸው ፅጌ ነን!!!
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!

No comments: