Saturday, July 19, 2014

የፕሬስ አፈናው በ”ሎሚ” መጽሔት ተጀመረ

July19/2014
ሐምሌ 7 ቀን 2006 ዓ.ም ከመንግስት በተላኩ ኃይሎች የ‹‹ሎሚ›› መጽሔት ቢሮ ‹‹ያለ ንግድ ፍቃድ›› በሚል ሠበብ ታሸገ፡፡ እነዚህ ከየትኛው ወገን እንደተላኩ ያልታወቁት ኃይሎች በቢሮ ውስጥ የነበሩትን የሂሳብ ሠነዶች ‹‹ይዘን እንሄዳለን፣ አትሄዱም›› በሚል በተፈጠረው እሰጥ አገባ ምክንያት ስልክ ደውለው ቁጥራቸው ከ20 ያላነሱ የታጠቁ የፌደራል ኃይሎችን በመጥራት እንዲሁም በድርጅቱ ውስጥ የሚገኙትን ንብረቶችና ወረቀቶችን ጨምሮ እንዳናወጣ በመከልከልና በማስፈራራት አስቀድመው ታዘው ይዘውት የመጡት ወረቀት “ያልታሰደ ንግድ ፍቃድ” የሚል ቢሆንም፣ ንግድ ፍቃዱ የታደሰበትን ማጋገጫ ሲመለከቱ ደግሞ ፊት ለፊታችን ወረቀቱን በመሠረዝ “ያለ ንግድ ፍቃድ” በሚል ጽፈው አሽገውታል፡፡ በወቅቱ ሐምሌ 12 ቀን 2006 ዓ.ም ለንባብ የምትበቃው ‹‹ሎሚ›› መጽሔት ወደ ማተሚያ ለመግባት በዝግጅት ላይ እንዳለች ይህ ችግር መፈጠሩ በሎሚ አባላቶች ላይ ግሬታን ቢፈጥርም፣ በተወሰደው ሕገ-ወጥ እርምጃ ሳንደናገጥ ከምንገባበት አንድ ቀን ዘግይተንም ቢሆን በተከፈለው ከፍተኛ መስዋዕትነት ማተሚያ ቤት ልናስገባ ችለናል፡፡ በወቅቱም ቢሮአችን እንደሚታሸግ ለምን አስቀድማችሁ በደብዳቤም ሆነ በስልክ አላሳወቃችሁንም ቢባሉም ‹‹የእናንተ ስፔሻል ኬዝ ነው፤ እኛ ከላይ ታዘን ነው›› የሚል ምላሽ ሠጥተዋል፡፡

ከዚህም በተጨማሪ የሎሚ መጽሔት አጋር ሆና በሣምንት ሁለቴ ለንባብ የምትበቃው ‹‹አፍሮ ታይምስ›› ጋዜጣም ከወዲሁ ልትዘጋ እንደምትችል አሁን በእስር ላይ የሚገኙት የዞን 9 አባሎች ያውቁ እንደነበር መረጃዎች እየጠቆሙ ይገኛሉ፡፡ ይኸውም እነዚሁ ኃይሎች ከመጀመሪያው ቀን በተለየ ሁኔታ በበነጋታው ተደራጅተው በመምጣት “ሠነዶችን እንፈልጋለን” በሚል ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ በፌደራል ኃይሎች የታገዘ የ5 ሠዓታት ፍተሻ (ከብርበራ አይተናነስም) ከአካሄዱ በኋላ በቢሮ ውስጥ የሚገኙትን የሂሳብ ሠነዶች በሙሉ ሰብስበው ወስደዋል፡፡ ሆኖም ግን የምንፈልገው የሂሳብ ሠነዶችን ይበሉ እንጂ፣ በቢሮው ውስጥ የሚገኙትን በተለያዩ ጊዜ የታተሙ የሎሚ መጽሔቶች፣ የአፍሮ ታይምስ ጋዜጦችና በእጅ ጽሁፍ የተተየቡ ወረቀቶችን አንድ በአንድ ሲፈትሹ ተስተውሏል፡፡ ይሄ ሕገ-ወጥ እርምጃ የእኛ የፕሬስ ውጤቶች በሆኑት ሎሚ መጽሔትና አፍሮ ታይምስ ጋዜጣ ላይ ሆነ ተብሎ ለማጥቃት የታለመ መሆኑን የሚያመለክተው እነዚሁ ያልታወቁት ኃይሎች አስቀድመው ከመምጣታቸው በፊት ‹‹የአፍሮ ታይምስ ቢሮን ለማሸግ እየመጣን ነው›› በማለት የደወሉ ቢሆንም፣ ቢሮ ድረስ መጥተው የነበሩትን ሠነዶች ከወሰዱ በኋላም ከአለቆቻቸው ጋር በስልክ በመነጋገር ሊያሽጉበት ይዘውት መጥተው የነበረውን የማሸጊያ ወረቀት ሳያሽጉበት ተመልሰዋል፡፡

በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ከአንድ ወር በፊት ገዢው መንግስት ነፃውን ፕሬስ ጥላሸት በመቀባትና እርምጃ እንደሚወስድ (ሎሚ መጽሔትን ጨምሮ) በፈበረካቸው የተለያዩ ዶክመንተሪዎቹ ሲዝት የቆየ ሲሆን፣ አሁን አፈናውን በሎሚ መጽሔት ‹‹አሃዱ›› ብሎ ጀምሯል፡፡ ሎሚ መጽሔትም ሆነ አፍሮ ታይምስ ጋዜጣ እራሱ ገዢው መንግስት ባወጣው የፕሬስ አዋጅ መሠረት ሕግና ደንቡን ተከትለን ለኢትዮጵያ ሕዝብ አማራጭ ድምጽ በመሆን ተገቢውን መረጃ በወቅቱ እያደረስን ቢሆንም፣ ይህንን ያልወደደው ገዢው መንግስት ነፃ ፕሬሱን ከነአካቴው ለማጥፋት የተለያዩ ወጥመዶችን እያዘጋጀ መሆኑን አንባቢያን እንድታውቁልን እንፈልጋለን፡፡ ውድ አንባቢዎቻችንም ይሄንን ተገንዝባችሁ እስከመጨረሻው ድረስ የሚከፈለውን መስዋዕትነት ለመቀበል ከጎናችን እንድትቆሙ እናሳስባለን፡፡

No comments: