Friday, July 11, 2014

ወያኔ አንዳርጋቸው ያፈነበት እለት የሚረግምበት ቀን ሩቅ አይደለም!

July11/2014
ህወሃት ጉጅሌ እንደማንኛውም አምባገነን ከፊት ከነበሩ አምባገነኖች ቅንጣት ትምህርት አልተማረም። ወያኔዎች በእብሪት የያዙት ስልጣንና ከህዝብ የዘረፉትን ንብረት የሚያጡት እየመሰላቸው በባነኑ ቁጥር የነጻነት አርበኞችን በማፈን በመግደልና በማሰቃየት ፍርሃታቸው የተወገደ ይመስላቸዋል።
ወያኔ የእኛ መሪና የኢትዮጵያ ህዝብ የነጻነት አርበኛ በሆነው አንዳርጋቸው ጽጌ ላይ ያካሄደው አፈና ከአፈናውም በሆላ በሚያደርሱበት አካላዊ ስቃይ ፍርሃታቸው የሚወገድ ወይም ስርአታቸው ከሞት የሚተርፍ መስሏቸው ከሆነ በእጅጉ ተሳስተዋል። አንዳርጋቸው ዛሬ በእጃቸው ሆኖ በነጻነት ይኖር ከነበረበት በበለጠ የሚለበልባቸው የውስጥ እግር እሳት ይሆናል።
አንዳርጋቸው ሰበአዊ ምቾቱንና ለራሱና ለቤተሰቡ መኖርን አቁሞ የኢትዮጵያን ህዝብ ነጻነት በህይወቱ ሊጋፈጥ ከቆረጠ ቆይቷል። እኛ የትግል ጓዶቹና ለህዝብ ነጻነት የቆሙ ሃይሎች ሁሉ አንዳርጋቸውን እናውቀዋለን። ወያኔ በአካሉ ላይ የለመደውን ስቃይ ጀምሮበታል፣ ከዚህ የበለጠም ጉዳት እንደሚያደርስበትም እናውቃለን። የአንዳርጋቸውን ታላቅ የነጻነት ሰውነትና ክብረ ህሊናውን፣ በአርበኝነቱ የሚሰማውን የኩራት ስሜቱን ለግፈኞች ያለውን ንቀትና መጸየፍ ሊለውጡ እንደማይችሉ አስረግጠን እናውቃለን።
አንዳርጋቸው እንደሁላችን ሰው ነውና በፈሪዎች በትር የሚደርስበት አካላዊ ስቃይ ግን ለህዝባችን የገባነውን ቃል ውሳኒያችንን እና አቋማችንን እንደብረት ያጠነክረዋል እንጂ አያላላውም።ይልቁንም በአንዳርጋቸው መታፈን ምክንያት ከመላ ሀገራችን በአለም ዙሪያ ከተበተነው ኢትዮጵያውያን እና ሌሎች የነሰታነት ሃይሎች የምንሰማውና እየሰማን ያለነው የሚያስገመግም ህብረ ድምጽ ከብረት የሚያጠነክር ሃይል ሆኖኗል።
አንዳርጋቸው የዘራው የነጻነት የአርበኝነት ዘር ከመብቀል አልፎ እየጎመራ በመሄድ ላይ ነው። አንዳርጋቸው ሺ አንዳርጋቸውን ተክቷል። ወያኔ አንዳርጋቸውን በማፈንና በእጁ አስገብቶ በራሱ መስኮት ቲቪ ስቃዩን እንግልቱን በማሳየት ሊያላምጠው የማይችል የብረት እንክብል ነው የነከሰው። ይህንንም ሳይውል ሳያድር ያየዋል፡፡
መላው ህዝባችን በእልህና በቁጭት ላይ ያለህ ወገናችን ና የሀገራችን የነሰታነትና የዴሞክራሲ ሃይሎች በሙሉ፡- በአንዳርጋቸው ላይ ወያኔ የፈጸመው የአሸባሪዎች ውንብድና በየአንዳንዳችን ላይ የተፈጸመ በደል ግፍ ነው።
ይህንን የሽብርና የውንብድና ስርአት ለማስወገድ አብረን ከመነሳት ውጪ አማራጪ የለንም። የልዩነታችንን አጥር አፍርሰን የወየኔን እድሜ እንድናሳጥር ግንቦት 7 ለሁላችንም ጥሪውን ያቀርባል።
አንድ ሆነን የአንዳርጋቸውን ስምና ምግባር እንሁን!
አንዳርጋቸው የዘራው እና እየጎመራ ያለው የአርበኝነት ንቅናቄ ተጠናክሮ ይቀጥላል። ወያኔ አንዳርጋቸውን ያፈነበት ቀን የሚረግምበት ጊዜ ከዚህ በኋላ ሩቅ አይሆንም፡፡
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!

No comments: