Saturday, July 26, 2014

“መሰበር” የማይቀር ነው

July 26/214
(ርዕሰ አንቀጽ)
pieces


የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ “በድርብ አኻዝ አድጓል፤ እያደገም ይሄዳል፣ ይቀጥላል፣ ይመነደጋል” እየተባለ “በተዘመረበት” ዓመታት ሁሉ በአንጻሩ በገሃድ ያለውን እውነታ ቁልጭ ባለ መልኩ የሚያሳዩ ዘገባዎች ሲወጡ ቆይተዋል፤ እየወጡም ይገኛል፡፡ ሆኖም እነዚህ ዘገባዎች በሥልጣን ላይ ያሉትን ሁለቴ እንዲያስቡ ሊያደርጋቸው እንደሚገባ ቢነገርም ምላሹ የተለመደው “የልማት ጸሮች” ያወጡት፣ “የአሸባሪዎች እጅ ያለበት”፣ “የኒዎ-ሊበራል አቀንቃኞች ዘገባ”፣ “የኪራይ ሰብሳቢዎች ምኞት”፣ ወዘተ ከሚል አልፎ አያውቅም።
በተደጋጋሚ የሚወጡ ዓለምአቀፋዊ መረጃዎች አገራችን በመክሸፍ ወይም በመሰበር አደጋ ላይ እንደምትገኝ ይናገራሉ። እነዚህ ጥናቶች በአብዛኛው የሚወጡት በምዕራቡ ዓለም በሚገኙ የጥናት ተቋማት በመሆናቸው ከላይ እንዳልነው “የወገኑ ናቸው”፣ “የልማታችንና የህዳሴያችን ተቃዋሚዎች ናቸው”፣ “ሚዛናዊ አይደሉም”፣ “የምዕራባዊያን ምኞት ማስፈጸሚያ”፣… ሲባልባቸው ቆይቷል። ኢህአዴግ ለዚህ ዓይነቱ ፍረጃ ቀዳሚነቱን በመውሰድ ከድቃይ የሚዲያ ተቋማቱ በተጨማሪ በተለይ “በአዲስ ራዕይ” ሲያብጠለጥላቸው በየደረጃው ያለው ካድሬ ደግሞ እንደ ገደል ማሚቶ ማስተጋባቱን ይቀጥላል።
የሚሰማው ኖረም አልኖረ የማስጠንቀቂያው ዘገባ አያቆምም ማስጠንቀቁን ይቀጥላል! ጥቂቶቹ ይህንን ይመስላሉ፡-
የዛሬ አንድ ዓመት ተኩል አካባቢ “የአሜሪካ የብሔራዊ የደኅንነት ምክርቤት እንደ አውሮጳውያን አቆጣጠር በ2030 የሚከሽፉ 15 መንግሥታትን (failed states) ዝርዝር” አውጥቶ ነበር። “በግጭት መብዛትና በአካባቢ ጥበቃ ቀውስ ምክንያት” ይከሽፋሉ ተብለው ከተተነበዩት የአፍሪካ፣ የእስያና የመካከለኛው ምስራቅ አገራት መካከል ኢትዮጵያ አንዷ መሆኗን ተናግሮ ነበር። (ጎልጉል ያጠናከረው ሙሉ ዘገባእዚህ ላይ ይገኛል)።
የዛሬ ዓመት አካባቢ “ዓለምአቀፉ የግልጽነት ድርጅት (Transparency International) በርካታ የአፍሪካ አገራት በሙስና “መበስበሳቸውን” ከእነዚህም መካከል ኢትዮጵያ ከቀዳሚዎቹ አገራት መካከል እንደምትገኝ” ዘግቦ ነበር። “በዚህ ዘገባ መሠረት በሙስና የተዘፈቁትን አገራት በመከፋፈል ባስቀመጠው ባለዘጠኝ መዘርዝር ውስጥ ኢትዮጵያ ከመጨረሻ ሁለተኛ መሆኗን በመግለጽ ከፍተኛ የሙስና አደጋ ውስጥ ከሚገኙ አገራት ዋንኛዋ አድርጓታል። ለዘገባው ግብዓት እንዲሆን ከቀረቡ ጥያቄዎች መካከል “ጉቦ ሰጥተዋል ወይ (ያውቃል)?” በማለት ለአንድ ሺህ ሰዎች ለቀረበው የናሙና ጥያቄ 44በመቶ ኢትዮጵያውያን “አዎን” በማለት መልሰዋል። ይህ የምዕራባዊ ድርጅት ዘገባ ቢሆንም “ውርሳቸውን እናስጠበቃለን” የሚባሉት ሟቹ መለስ፤ በረሃ በነጻአውጪነት፤ ከዚያም “በመንግሥትነት” ራሳቸው ስለመሩት ድርጅት የተናገሩትን የሚያረጋግጥ ነው። እንዲህ ነበር ያሉት “ከእንጥላችን ገምተናል”! (ጎልጉል ያጠናከረው ሙሉ ዘገባ እዚህ ላይ ይገኛል)።
የዛሬ ስድስት ወር ገደማ የመፈንቅለ መንግሥት ስጋት ከሚታይባቸው 40 አገራት መካከል ኢትዮጵያ በ25ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ትንበያ ተሰጥቶ ነበር። ለዚህ ትንበያ የተወሰዱት ነጥቦች “የጂኦግራፊያዊ አቀማመጥ፣ የፖለቲካ አለመረጋጋት፣ የእርስበርስ ግጭት፣ የነጻ ምርጫ ሁኔታ፣ የኢኮኖሚ ዕድገት፣ በየቀጣናው ያለ የመፈንቅለ መንግሥት እንቅስቃሴ፣ ወዘተ” መሆናቸው ተጠቅሶ ነበር። ይኸው ዘገባ “ከሚከሽፉ መንግሥታት” ሪፖርት ጋር በመሆን በዚህ መልኩ ተዘግቦ ነበር።
እንዲህ ዓይነቶቹን መረጃዎች በሥርዓት የሚመለከቱና የሚያጠኑ ፖሊሲ አውጪዎችና ተመራማሪዎች ወራት ጠብቀው የኢህአዴግን ፈር የለቀቀ አካሄድ ከመኮነን በማለፍ “የአፍሪካ ቀንድ ስጋት” ነው በማለት በግልጽ እስከመናገር ደርሰዋል። “በኢትዮጵያ አንድ ችግር ቢፈጠር ለማረጋጋት አስቸጋሪ እንደሚሆን፣ ህዝቡ በተለይ በህወሃቶች ላይ የሚያሳየው ጥላቻ እየተካረረ መምጣቱ፣ በአገሪቱ የሚፈጸመው ያልተመጣጠነ የሃብት ስርጭት፣ አፈናውና ሌሎች የህወሃት/ኢህአዴግ ተግባራት ተዳምረው ህዝቡን ክፉኛ ማስቀየሙ ያልታሰበ ችግር ሊቀሰቅስ እንደሚችል” ጎልጉል አንድ አሜሪካዊ ዲፕሎማት ጠቅሶ የዛሬ አራት ወር አካባቢ ዘግቦ ነበር። ዲፕሎማቱ እንደሚሉት “ህወሃቶች የቀጠናው የሰላም ምንጮች ስለመሆናቸው ለራሳቸው ምስክርነት ለመስጠት ቢሞክሩም በተግባር የሚታየው ግልባጩ ነው” ማለታቸውን በዚሁ የዜና ዘገባ ተገልጾዋል። (ጎልጉል ያጠናከረው ሙሉ ዘገባ እዚህ ላይ ይገኛል)።
የዛሬ ወር አካባቢ በኢኮኖሚው መስክ “በኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ የዓለምአቀፍ ልማት ትምህርት ክፍል ሥር የኢኮኖሚ ጥናት የሚያካሂደው የኦክስፎርድ የድህነትና የሰብዕ ልማት ማዕከል (The Oxford Poverty and Human Development Initiative (OPHI)) ያወጣው የ2014 የጥናት መረጃ ደሃ ከሚባሉት 108 አገራት ዝርዝር ኢትዮጵያ ከመጨረሻው ሁለተኛ መሆኗን” ዳጎስ ያለ ጥናት ማቅረቡ ተዘግቦ ነበር። “ትምህርት፣ ጤና እና የኑሮ ሁኔታ ማለትም ኤሌክትሪክ፣ ጽዳት፣ የሚጠጣ ውሃ፣ የንብረት ባለቤትነት፣ ወዘተ” እንደ ጠቋሚ መረጃ በመውሰድ እዚህ ድምዳሜ ላይ መድረሱን ማዕከሉ አስታውቋል። ሪፖርቱ እንዳብራራው ከሆነ በኢትዮጵያ “ከ100 ሰዎች መካከል 87ቱ ድሃ ተብለው የሚጠሩ ሲሆን 58ቱ ሰዎች ግን መናጢ ደሃ ተብለው የሚጠሩ” መሆናቸውን ጠቅሶ ድህነቱ “በተለይ በገጠር እጅግ የከፋ እንደሆነ በመጠቆም ከ100 ሰዎች ውስጥ 96ቱ ደሃዎች” መሆናቸውን በግልጽ ተናገሯል። (ጎልጉል ያጠናከረው ሙሉ ዘገባ እዚህ ላይ ይገኛል)።
እነዚህ ለአብነት የጠቀስናቸው ከብዙዎቹ መካከል የተወሰኑት ናቸው፡፡ በምዕራባዊ ተቋማት በመውጣታቸው ብቻ ዘገባውን ጸረ-ኢህአዴጋዊ አያደርገውም፡፡ ምክንያቱም የምዕራብ ተቋማት የሚያወጡትን መረጃ በጭፍን የሚያጥላላው ኢህአዴግ ለራሱ ድርጅታዊ አሠራር የሚፈልገው ዓይነት ዘገባ በምዕራባዊ ድርጅቶች እያስወጣና እያሰራ ለፖለቲካው ድርሰት ሲጠቀምበትና ካድሬዎቹንም ይህንኑ ሲያዘምር በተደጋጋሚ ተሰምቷል።
በኮምፒውተር ፕሮግራም ቋንቋ “garbage in garbage out” የሚባል አነጋገር አለ፤ ፕሮግራም የሚያደርገው ሰው የሚጨምረው ኮድ “ጥራጊ” (ትርጉም አልባ) ከሆነ የፕሮግራሙ ውጤት “ጥራጊ” (ትርጉም አልባ) ይሆናል። “ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ” በግልባጩ እንደማለት ነው።
ከላይ የተጠቀሱትን ጥናቶች የሚያካሂዱት ተቋማት የራሳቸው አጀንዳ አላቸው ቢባልም ለዘገባቸው ግብዓት የሚጠቀሙት መረጃ ግን የሚገኘው በተግባር ከሚፈጸመውና ሕዝብ በየዕለቱ ከሚጋፈጠው የኑሮ ውጣውረድ በቀጥታ የተወሰደ ነው። እየሆነ ያለውን ነገር በየትኛውም ዓይነት ፕሮፓጋንዳ ቢሸፍኑትና ቢያጥላሉት ዕውነታውን እንዲስት ግን ማድረግ አይቻልም። የሕዝብ ሰቆቃ፣ ምሬት፣ ሃዘን፣ … ለኢህአዴግና ካድሬዎቹ ጆሮገብ ባይሆኑም የኢትዮጵያን ሰማይ ግን ጥሶ አልፎ ሄዷል። እንደፈለጉ ቢያንቋሽሹትና ቢያጥላሉትም በየጊዜው የሚወጣው ዘገባ የሕዝብን ምሬት ቁልጭ አድርጎ የሚመሰክር ነው። ኢህአዴግ ግን አሁንም “አልሰማም” በሚል ዕብሪት እንደተነፋ ነው!
ኢህአዴግ እንዲሰማ በተደጋጋሚ ከአገር ውስጥም ቢሆን ከውጭ፤ ከኢትዮጵያውያንም ይሁን ከሌሎች፤ ከተቃዋሚዎችም ሆነ ከራሱ ደጋፊዎች፤ … ቢነገረውም በተቃራኒው በሚፈጽመው ድርጊት “አልሰማም” የሚል የዕብሪት ምላሽ እየሰጠ ነው። ከውድቀት በፊት ዕብሪት እንደሚቀድም የዘነጋው ወይም እርሱንም ጭምር “አልቀበልም” ያለ ይመስላል!
አላቆም ያለው ሰቆቃ፣ እስራት፣ ግድያ፣ እንግልት፣ … የውሸት ክስ፣ የውሸት ውንጀላ፣ የውሸት ፍርድቤት፣ የውሸት ብያኔ፣ … ኅሊናን የሸጠ ዲስኩር፣ መግለጫ፣ ቃለምልልስ፣ … ጥቂቶች “አይሰማም” ቢሉም ሕዝብን እያስለቀሰ፣ እያስመረረ፣ እያንገፈገፈ፣ … ሄዷል። በሕዝብ ደምና እምባ ጸንቶ መቆም አይቻልም፤ ለዚህ ታሪክ ምስክር ነው። “ከተማን በደም ለሚሠራ ወዮለት” እንደሚል ያልተዘራ አይታጨድምና፤ “ንፋስን የዘራ ሁሉ አውሎ ንፋስን ያጭዳል”! አሁን ባይመስልም ሁሉም ወቅቱን ጠብቆ ይሆናል። እኛ የምንመኘው ወይም ከመመኘት የምንታቀብበት ቢሆንም ባይሆን “መሰበር” ግን አይቀርም! እጅግ የሚያሳስበን ግን ከዚያ በኋላ ያለው ጨለማ ነው! ሳይመሽ ጆሮ ያለው ቢሰማ መልካም ነው እንላለን!

No comments: