Tuesday, June 17, 2014

የጀኔራሎቹ የጓዳ ሽኩቻ! – ቀጣዩ ኢታማዦር ማን ነው?

June17/2014

‹‹ደመወዝ አነሰኝ ብሎ ጭማሪ የሚጠይቅ ካለ አሁንኑ ከሰራዊቱ መልቀቅ ይችላል፡፡›› ይህ የጦር ኃይሎች ኢታማዦር ሹምየሆነው ጀኔራል ሳሞራ የኑስ ሁለተኛው የሰራዊት ቀን በተከበረበት ሰሞን ባህር ዳር ከተማ ሙሉዓለም አዳራሽ ከተሰበሰቡት የሰራዊቱ አባላት መካከል የደመወዝ ጭማሪን በተ መለከተ ለተነሳለት ጥያቄ ምላሽ ሲሰጥ የተናገረው ነው፡፡ ኢትዮጵያ ከአጼ ኃይለስላሴ ዘመነ መንግስት ጀምሮ ዘመናዊ ውትድርናና የጦር ስልት ሰልጣኝ ወታደሮችንና መኮንኖችን በተደራጀ ስልጠና ማፍራት መጀመሯ ይጠቀሳል፡፡ በሀረርና ሆለታ የጦር አካዳሚዎች በመታገዝ ዘመናዊ የውትድርና ሳይንስ ትምህርት መሰጠት የተጀመረው በዚሁ በንጉሱ ዘመን ነበር፡፡ በዚህ መልኩ እየተደራጀ የመጣው የሀገሪቱ ሰራዊት እስከ ኢህአዴግ ወደ ስልጣን መምጣት ዘመን ድረስ የሀገሪቱ ብሄራዊ ሰራዊት ሆኖ ለመዝለቅ ችሏል፡፡ ሆኖም የደርግ ውድቀትን ተከትሎ በነበረው ጊዜ አያሌ የሰራዊቱ አባላት ለስደትና ሞት እንዲሁም ለብተና ለመዳረግ በቅተዋል፡፡

(በእርግጥ ቀደም ብለው የተማረኩትን የቀድሞው የሰራዊቱ አባላት በኢህአዴግ ውስጥ ማግኘት እንደሚቻል ኩማ ደመቅሳ (የፖሊስ መቶ አለቃ እነደነበር ይነገርለታል)፣ እና ተራ ሚሊሻ እንደነበር የሚነገርለት አቶ አባዱላ ገመዳን ከፊት መስመር ላይ በማስቀመጥ መጥቀስ ይቻል ይሆናል፡፡ እንደነዚህ ያሉት የቀድሞው ሰራዊት አባላት ደርግ ከመውደቁ በፊት ከድተው የህወሓትንና የኢህዴንን ታጋዮች የተቀላቀሉት ናቸው፡፡) እናም በጊዜው ታጋዮች ሀገሪቱን በሙሉ ለመቆጣጠር መቻላቸውን ተከትሎ የኢትዮጵያ ሰራዊት (የደርግ ሰራዊት ብቻ ብሎ ማቃለሉን አልፈለግሁትም) ሜዳ ላይ ተበትኖ እንደቀረ ይታወሳል፡፡ ስለሆነም የኢህአዴግ ሰራዊት ሲያሸንፍ ሊያስተምሩት የሚችሉ አንዳንድ የቀድሞው ሰራዊት አባላት መኮንኖችን ብቻ አስቀርቶ ሌላውን ወደጎን ገፍቶታል፡፡ በተለይም የኢትዮጵያ የባህር ኃይል ሙሉ ለሙሉ ሲፈርስ ያለቀው ሰራዊት አልቆ በዚያው የሸሸውም የመን ላይ ለእስር ተዳርጎ ከፍተኛ ስቃይ መጋፈጡ የአደባባይ እውነት ሆኖ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡ በዚህም ኢትዮጵያ አሁን ላይ ያለ አንዳች ባህር ኃይል፣ ያለ አንዳች የተፈጥሮ የባህር በር የቀረች ሀገር ለመሆን ተዳርጋለች፡፡ አሁን ያለው መከላከያ ሰራዊታችን የምድርና የአየር ኃይልን ብቻ ያቀፈ ነው፡፡ የምድር ኃይሉ ሙሉ ለሙሉ ለማለት በሚያስደፍር ሁኔታ በቀድሞ ታጋዮችና በቅርብ ጊዜ ምልምሎች የተደራጀ እንደሆነ ሲነገርለት፣ አየር ኃይሉ ላይ ግን ኢህአዴግ እንደገባ የአየር ኃይል ሳይንስን እንዲያስተምሩት የመረጣቸውን ጥቂት የቀድሞው የኢትዮጵያ ሰራዊት አባላትን በውስጡ የኋላ ደጀን አድርጎ ይዞ መቆየቱ ይነገራል፡፡ በአጠቃላይ ህወሓት/ኢህአዴግ ደርግን አሸንፎ ስልጣን ላይ እንደወጣ በትግል ይዞት የመጣውን ሰራዊት ‹‹ብሄራዊ ሰራዊት›› ለማድረግ ችሏል፤ ወዲያውም እዙ በመለስ ዜናዊ ስር እንዲሆን መደረጉ ታወቀ፡፡ ኢህአዴግ እንደገባ አካባቢ ብዙ ሰዎች ሰራዊቱን ‹የገበሬ ሰራዊት› እያሉ ይጠሩት እንደነበር ይታወሳል፡፡ በሂደት ግን ቀድሞ የነበሩትንና ሌሎች አዳዲስ የወታደራዊ ትምህርት ቤቶችን በመጠቀም ሰራዊቱን የማዘመን ስራ ተሰርቷል፤ አዳዲስ የሰራዊቱ አባላትን በአዲስ ዘመናዊ ስልጠና ኮትኩቶ ወደሰራዊቱ ማካተት ተችሏል፡፡ አሁን ላይ የኢትዮጵያ ሰራዊት ልክ እንደ አያቶቹና አባቶቹ ሁሉ ግዳጁን በብቃት የመወጣት ተፈጥሮአዊ የጀግንነትና የግዳጅ ስብዕናን የተላበሰ እንደሆነ ብዙዎች ምስክርነታቸውን ይሰጡታል፡፡

በእርግጥም የሰራዊቱ ጀግንነት ሊካድ የሚችል አይደለም፤ ሀቅ ነውና፡፡ አንዱ ማሳያ የሚሆነንም በተለያዩ ዓለም አቀፍ የሰላም ማስከበር ግዳጆች ላይ አመኔታን አትርፎ በመመረጥ በተ ሰማራበት ግንባር ሁሉ በሚገባ ግዳጁን ለመወጣት መቻሉ ነው፡፡ አሁን ያለው ሰራዊት በአዲስ መልክ ‹ብሄራዊ ሰራዊት› ሆኖ በአዋጅ የተደራጀው የካቲት 7/1988 ዓ.ም እንደነበር ይታወሳል፡፡ (ይህን ቀን ከዛሬ ሁለት ዓመት በፊት ጀምሮ የሰራዊት ቀን በሚል ሰራዊቱ እንዲያከብረው ተወስኖ ሁለት ጊዜ ለማክበር ችሏል፤ የአድዋ ድል የተመዘገበበት ታሪካዊ ቀን እያለ ይህኛው እንዴት ‹‹የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ቀን›› ተብሎ እንደተመረጠ አወዛጋቢ ቢሆንም ቅሉ!) ለማነኛውም በማደራጃ አዋጁ ላይ የመከላከያ ሰራዊቱን ግዳጅና ‹የማንነት› ተዋጽኦ በአጭሩ ለመግለጽ ተሞክሯል፤ ‹‹የሐገሪቱን ሉዓላዊነት የሚያስከብር፣ የኢትዮጵያን ብሔር ብሔረሰቦች ሚዛናዊ ተዋጽኦ ያካተተ፣ ከማናቸውም ፖለቲካ ድርጅት ወገንተኝነት ነጻ በሆነ ሁኔታ ተግባሩን የሚያከናውን ሰራዊት ማደራጀት…›› በሚል፡፡ ቃል የሚዋሸከው እንግዲህ እዚህ ጀምሮ ነው፡፡ ‹‹ሚዛናዊ ተዋጽኦ›› እና ‹‹ከማናቸውም ፖለቲካ ድርጅት ወገንተኝነት ነጻ…›› የሚሉትን ሀረጎች ወስደን ተግባር ላይ ያለውን ስናይ እውነታው ለየቅል መሆኑን እንገነዘባለን፡፡

በመጀመሪያ ደረጃ ኢህአዴግ ነባሩን የኢትዮጵያ ሰራዊት አፍርሶ በምትኩ ተሸክሞ ይዞት የመጣውንና ለስልጣኑ ያበቃውን ሰራዊት ‹ብሄራዊ ሰራዊት› ነው ሲል ወገንተኛነቱ እንደምን ያለ ሊሆን እንደሚችል ቀድሞ የሚያውቀው ጉዳይ ይሆናል፡፡ ሲቀጥል ደግሞ ካሉት አጠቃላይ የሐገሪቱ የጦር ጀኔራሎች መካከል ስንቶቹ የህወሓት ቀኝ እጅ እንደሆኑ ከኢህአዴግም ሆነ ኢትዮጵያ ህዝብ የተሰወሩ አለመሆናቸውን ኢህአዴግ ሊያጣው የሚችለው እውነታ አይደለም፡፡ እስካሁን ከነበሩትና አሁን ካለው የመከላከያ ሰራዊቱ ኢታማዦር ሹሞች መካከል ስንቶቹ የህወሓት እንደሆኑስ የማያውቅ ማን ነው? በእርግጥ አሁን ላይ በጣም አስቸጋሪ በሚባሉ የጦር ግዳጆች ላይ የትኞቹ የሰራዊቱ ክፍሎች በቀዳሚነት እንደሚመደቡ ይታወቃል፡፡ በመከላከያ ሰራዊት ኢንዶክትሪኔሽን ክፍል ውስጥ የሚሰራ አንድ ባለማዕረግ የሰራዊቱ አባል ስለዚህ ሁኔታ ሲገልጽ፣ ‹‹ያስፈልገኛል የምትለውን መሰረታዊ ነገር ለማግኘት እንኳ በጣም አዳጋች ነው፡፡ ሌላው ቢቀር በተለያዩ የሀገሪቱ የልማት ፕሮጀክቶች ላይ ጥበቃ የሚያደርጉ በረሃ አካባቢ ያሉ የሰራዊቱ አባላት ምን አይነት የግዳጅ ሁኔታ ላይ እንዳሉ የሚያውቀው ያውቀዋል፡፡ ስለሰራዊቱ ብዙ መናገር አይቻልም እንጂ ስንት ነገር አለ መሰለህ? አድራጊ ፈጣሪዎቹ ግን እዚህ አዲስ አበባ ላይ ያሉት ሰዎች ናቸው፡፡ ምደባው ጎጠኝነትና ጎሰኝነትንም እንደ ስውር መስፈርት ያስቀመጠ ነው፡፡›› ይላል፡፡ በእርግጥ የእነዚህ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሆነው ግዳጃቸውን የሚወጡ የሰራዊቱ አባላት ሁኔታ እዚህ መሀል ሀገርና አንጻራዊ ሰላም ባለበት ቦታ ላለነው ኢትዮጵያውያን በግልጽ ባይታየንም፣ በከፍተኛ የሀገርና የወገን ፍቅር ስሜት ሆነው ግዳጃቸውን ስለሚወጡ ግን ምስጋና ይገባቸዋል፡፡

የእነዚህ ቆራጥ ወገኖቻችን ጥረት ነው ሀገርንና ህዝብን የሚ ያስከብረው፡፡ ዳሩ ግን እንዲህም ሆነው ግዳጃቸውን ሲፈጽሙ ትንሽ እንኳ የደመወዝና የጥቅማጥቅም ጥያቄ ሲያነሱ፣ ‹‹ደመወዝ አነሰኝ ብሎ ጭማሪ የሚጠይቅ ካለ አሁንኑ ከሰራዊቱ መልቀቅ ይችላል፡፡›› የሚል አግባብ ያልሆነና አሳፋሪ መልስ ይሰጣቸዋል፡፡ ይህን መሰሉን መልስ የሚሰጡት ጀኔራሎች እዚህ አዲስ አበባ ላይ የተንደላቀቀ ኑሮ እየኖሩ፣ ምንጩ ያልታወቀ ሀብት እያፈሩ መሆኑ ደግሞ ግርምትን የሚያጭር ነው፡፡

 አሁን አሁን ጄኔራሎቻችን የብዙ ኃብት ባለቤቶች እንደሆኑ ይነገራል፤ ይህ ፎቅ የጀኔራል እገሌ ነው፣ ያኛው ደግሞ የጀኔራል እገሌ ነው የሚሉ በርካቶች ናቸው፡፡ ለመሆኑ እነዚህ ጀኔራሎች ገቢያቸው ምን ያህል ነው ብለን ስንጠይቅ ግን ምላሽ አናገኝም፤ ገቢያቸው ይሆናል ብለን ከምናምነው ጋር ለማገናዘብ ከሞከርን ደግሞ ሰዎቹ ሙስና ውስጥ መዘፈቃቸውን ለመናገር እንደፍራለን፡፡ (በነገራችን ላይ የኢትዮጵያ ኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት መስሪያ ቤት ኃላፊ ተደርጎ የተሾመው ሰው ራሱን ከሙስና ያራቀ እንደሆነ የሚነገርለት ሲሆን በሌሎች ሰዎች ላይ ያለውን አሰራር በቅርበት እየተከታተለ እንደሆነ ምንጮች ያነሳሉ፡፡ ‹‹ተውአቸው የሰሩትን ፎቅ ይስሩ፤ በባንክም የሚያስቀምጡትን ያህል ያስቀምጡ፤ በቅርብ ጊዜ ግን ሀብቱ ለሚመለከተው የኢትዮጵያ ህዝብ ይመለሳል›› በማለት መናገሩንም የሚያስታውሱ አሉ፡፡ ይህን የሰውየውን ባህርይ ያጤኑት አንዳንድ ጀኔራሎችና ባለስልጣናት ታዲያ ሰውዬውን ከሙስናና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ጋር ለማነካካት ሙከራ ማድረጋቸው አልቀረም፤ እስካሁን እየተሳካላቸው እንዳልሆነ ቢነገርም ቅሉ፡፡) ዝሆኖቹ ጀኔራሎች ይህ ሁሉ ነገር አያሳስባቸውም፤ ተቆጭም ያላቸው አይመስሉም፡፡ እነሱን የሚያሳስባቸው በመካከላቸው ያለውና ሊኖር የሚገባው የእርስ በእርስ የበላይነት ነው፤ በስልጣንም በሀብትም፡፡ ባለ አራት ኮከብ ጀኔራሉ ሳሞራ የኑስ በመለስ ዜናዊ ምርጫ የጦር ኃይሎች ኢታማዦር ሹም ተደርጎ የተሾመው የዛሬ ሰባት አመት ገደማ እንደነበር ይታወሳል፡፡ (የመጀመሪያው ባለ ሙሉ ጀኔራል ማዕረግ ያገኘ በሚል ምስሉ ብሄራዊ ሙዚየም የተቀመጠለት የጦር ሰው ሳሞራ የኑስ ነው፡፡) ይህ ሰው እስካሁን በስልጣን ላይ ለመቀመጡ ዋነኛ ምክንያት የሚባለው ለመለስ ዜናዊ የነበረው ቅርበትና ታዛዥነት ነው፡፡ በእርግጥ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሞት ባይቀድመው ኖሮ ሳሞራን ከኢታማዦርነቱ የማንሳት እቅድ እንደነበረው ይነገራል፡፡

ይህንን ጠንቅቆ ያውቅ የነበረው ጀኔራል ሳሞራ ታዲያ የሚሻርበትን ቀን ሲጠብቅ መለስ ህይወቱ በማለፉ በያዘው ቦታ ለመደላደል ስራዎችን መስራት እንደጀመረ ይወሳል፡፡በመለስ ዜናዊ እቅድ ውስጥ ሳሞራን እንዲተካው ተዘጋጅቶ የነበረው ደግሞ ሳሞራ የሙሉ ጀኔራልነት ማዕረግ ሲደፋለት በሁለተኛነት ደረጃ የሌትናት ጀኔራልነት ማዕረግን የተጎናጸፈው የ‹ብአዴኑ› ወጣቱ የጦር ሰው አበባው ታደሰ ነበር፡፡ ይህን የአበባው ወደ ኢታማዦር ሹምነት መምጣትን አጥብቀው ከማይፈልጉት ሰዎች ደግሞ ጀኔራል ሳሞራ ዋነኛው እንደሆነ ይነገራል፡፡ በዚህም የተነሳ የመለስን ህልፈት ተጠቅሞ ሳሞራ አበባውን ከሰራዊቱ የማግለል ስራ እንደሰራ የሚጠቅሱ አልጠፉም፡፡ እናም የማዕከላዊ እዝ ዋና አዛዥ የነበረውን ሌትናንት ጀኔራል አበባው ታደሰን በቦታው መቆየት ሳሞራ የፈለገው አይመስልም፡፡ አበባው ከማዕከላዊ እዝ አዛዥነት እንዲነሳ ተደረገ፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን ሳሞራ እምብዛም ቅርብ እንዳልሆነ የሚነገርለትን ሌላው ‹ጠንካራ› ሰው ሌትናንት ጀኔራል ሳዕረ መኮንን (የሰሜን እዝ ዋና አዛዥ የነበረ) ከኃላፊነቱ እንዲነሳ ተደረገ፡፡ አሁን ጀኔራል ሳሞራ ስጋቶቹን ያቃለለ መሰለ፡፡

ሂደቱ በዚህም የሚያበቃ እንዳልሆነ ነው ምንጮች የሚጠቁሙት፡፡ በተለይም በሌትናት አበባው ታደሰ ላይ ያለው ስጋት እሱን ከኃላፊነት በማንሳት ብቻ የሚያበቃ አልሆነም፡፡ በማዕከላዊ እዝና በሌሎችም በሰራዊቱ ከፍተኛ ተቀባይነት እንዳለው የሚነገርለት በእድሜ ትንሹ ጀኔራል አበባው ታደሰ ኃላፊነቱ ከተነሳም በኋላ ከፍተኛ ክትትል እንደሚደረግበት ነው የሚነገረው፡፡ በተለይም ከሰራዊቱ ከአዛዥነቱ ከተነሳ በኋላ ምዕራብ ጎጃም አዊ ከሁለት ሲቪሎች ጋር አንድ ሻይ ቤት እንደታዬ መነገሩ ከፍተኛ ጥርጣሬ እንዲነሳበት አስችሎአል፡፡ ይህን ተከትሎ በማዕከላዊ እዝ ሲደረግ በነበረው ግምገማ ወቅት አንዳንድ የሰራዊቱ አባላትን በጎጠኝነት ሰበብ የማደናገር ሁኔታ እንደታዬ ይጠቀሳል፡፡ አንዳንዶች በግልጽ ‹‹የአበባው አሽከር ነበርኩ ብለህ ሂስህን ዋጥ!›› እየተባሉ እንደተገመገሙ ምንጮች ያወሳሉ፡፡

በእርግጥም አሁን ጀኔራል ሳሞራ ጡረታ የሚወጣበትን ጊዜ በሚገባ ያራዘመ ይመስላል፤ ስጋት ያላቸውን ሰዎችም ከቁልፍ ቦታቸው ለማሸሽ ችሏል፡፡ በመከላከያ ሰራዊት ደንብ መሰረት ቅድሚያነትና ብቃት (ሲኔሪቲ) ትልቅ ተጽዕኖ አላቸው፡፡ ይህን ካየን ደግሞ አሁን ላይ ሰራዊቱ ውስጥ ካሉ ጀኔራሎች መካከል የሳሞራ ምትክ ሊሆን የሚችለው በቀዳሚነት ከሳሞራ አንድ ደራጃ ወረድ ብሎ የሚገኘውና ከሌሎቹ ቀደም ብሎ ሌትናት ጀኔራልነትን ያገኘው አበባው ታደሰ ነበር፡፡ ይህ እንዲሆን ያልፈለገው ሳሞራ ግን ሰውዬውን ገለል ማድረጉን መርጧል፡፡ ሳዕረንም እንዲሁ፡፡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ጀኔራል ሳሞራ እንዲተካው የሚፈልገው አሁን በአብዬ የሰላም ማስከበር ግዳጅን በአዛዥነት የሚመራው ሌትናት ጀኔራል ዮሃንስ ገብረመስቀል ነው፡፡ ይህ ሰው ሌትናት ጀኔራልነቱን ያገኘው በቅርብ ቢሆንም የእሱን ሲኔየሮች ከኃላፊነት ገለል በማድረግ እሱ ወደመሪነቱ እንዲመጣ የተፈለገ ይመስላል፡፡ ሌትናት ጀኔራል ዮሃንስ ገብረመስቀል ከጄኔራል ሳሞራ ጋር ጥብቅ ወዳጆች እንደሆኑ ይነገርላቸዋል፡፡ ዮሃንስ ከፍተኛ ሀብት እንዳካበቱ ከሚነገርላቸው ጀኔራሎች መካከል ሲሆን በአሁኑ ጊዜ ደመወዙ በአስራ ሺ የሚቆጠር ዶላር እንደሆነ ይጠቀሳል፡፡ ቢሆንም ግን ሀብታምነቱ አሁን የዚህ ደመወዝ ባለቤት ከመሆኑም የቀደመ ለመሆኑ መረጃዎች ያሳብቃሉ፡፡ (ሌትናት ጀኔራል ዮሐንስ የደህንነቱን ስራ በኃላፊነት የሚዘውረው ጌታቸው አሰፋም ድጋፍ እንዳለው ይጠቀሳል፡፡)

 በዚያም አለ በዚህ ግን አሁን ላይ ሳሞራ መለስ በህይት እያለ ከነበረው እቅድ በወጣ መልኩ በኢታማዦር ሹምነቱ መቆየቱ ሀቅ እንደሆነ ይገኛል፤ የጡረታ ጊዜውን ማንም ቆርጦ ማስቀመጥ የተቻለው የለም፡፡ በስብሰባዎች ወቅት በድፍረት እያንዳንዱን ነጥብ እያነሳ ይገስጻቸው ነበር የሚባልለት ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ አሁን የለም፡፡ ስለዚህም አሁን ሳሞራም ሆነ ሌሎች ጄኔራሎች ተቆጭ የሌላቸው እንደሆኑ ነው የሚነገረው፡፡ በትንሹም ቢሆን አቶ በረከት ስምዖን የመለስን ቦታ ተክቶ ለመገሰፅ የሚሞክርበት አጋጣሚ ቢኖርም እንደመለስ ግን አይደነግጡለትም፤ በስልጣናቸውም ላይ ለውጥ የሚያመጣ መስሎ አይሰማቸውም ነው የሚባለው፡፡ በመጨረሻም፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝን ሚና እዚህ ላይ ማንሳቱ እምብዛም አስፈላጊ አይመስለኝም፡፡ በእርግጥ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ናቸው፡፡ ያም ቢሆን ግን ጀኔራሎቹ ለሰውዬው እንደቀድሞው አዛዣቸው መለስ ዜናዊ አድርገው የሚመለከቷቸው አይመስለኝም፡፡ እናም አሁን በሰራዊቱ ውስጥ ወሳኙ አድራጊ ፈጣሪው ሰው ሳሞራ የኑስ ለመሆኑ ጥርጥር የለውም፡፡ ለዚያም ይመስላል ከሰራዊቱ ለተነሳለት ጥያቄ ‹‹ካልፈለግህ ልቀቅ…›› ምላሽ ለመስጠትየበቃው፡፡ ለዚያም ይመስላል ለቀጣይ የስልጣን ጊዜው ‹ስጋቴ› ናቸው ያላቸውን ሲኒየር ጀኔራሎችን ከአዛዥነት ያነሳቸው፡

No comments: