Sunday, June 1, 2014

ከማረሚያ ቤት ያመለጠው የሦስት ሕፃናት ወላጆች ገዳይ ተጠርጣሪ ተያዘ

June 1/2014

-የተያዘው የሴቶች ብሔራዊ ቡድን ጨዋታ ሲመለከት ነው

በወሰን ግጭት ምክንያት የሦስት ሕፃናትን ወላጆች በጥይት ደብድቦ በመግደል ወንጀል ታስሮ ከነበረበት የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች ግንቦት 8 ቀን 2006 ዓ.ም.

አምልጦ የነበረው ተጠርጣሪ፣ ግንቦት 17 ቀን 2006 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ስታዲየም የኢትዮጵያንና የጋናን ብሔራዊ ቡድን ጨዋታ ሲከታተል መያዙን ምንጮች ለሪፖርተር ገለጹ፡፡

አቶ ዳንኤል ነጋሽና ወ/ሮ ምስለ ማሞ የተባሉ የሦስት ሕፃናት ወላጆችን፣ የካቲት 24 ቀን 2006 ዓ.ም. በንፋስ ስልክ ላፍቶ ከፍለ ከተማ ለቡ ማዞሪያ አካባቢ በጥይት ደብድቦ ገድሏል የተባለው ተጠርጣሪ መቶ አለቃ ጌትዬ አለሜ የተባለ ግለሰብ ሲሆን፣ እስከ 1999 ዓ.ም. ድረስ የመከላከያ ሠራዊት አባል እንደነበር በወቅቱ መዘገባችን ይታወሳል፡፡

ግለሰቡ የግድያ ወንጀሉን ፈጽሟል በሚል ተጠርጥሮ በቁጥጥር ሥር ውሎ በተመሠረተበት ክስ፣ ማረሚያ ቤት ሆኖ ክሱን እንዲከታተል በፍርድ ቤት በተሰጠው ብይን መሠረት ማረሚያ ቤት መውረዱን ምንጮቹ ገልጸዋል፡፡

ማረሚያ ቤት ውስጥ መታመሙን በመግለጽ በማረሚያ ቤቱ ክሊኒክ በመታከም ላይ እያለ የላብራቶሪ ምርመራ ታዞለት ወደ መፀዳጀ ቤት ከገባ በኋላ፣ የመፀዳጃ ቤቱን መስኮት በመስበር ከግንቦት 8 እስከ 17 ቀን 2006 ዓ.ም. ድረስ ተሰውሮ መክረሙን ምንጮች አስረድተዋል፡፡

የተጠርጣሪውን ሙሉ መረጃ የወሰደው የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ልዩ ክትትል ሲያደርግ ቆይቶ፣ ግንቦት 17 ቀን 2006 ዓ.ም. በቁጥጥር ሥር አውሎ ለማረሚያ ቤት ማስረከቡን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ግለሰቡ የኢትዮጵያ ወንዶች ብሔራዊ ቡድን ለዓለም ዋንጫ ማጣሪያ አዳማ ላይ ልምምድ ሲያደርግ፣ በሥፍራው ተገኝቶ ‹‹ለቡድኑ የደኅንነት ሠራተኛ ልሁን›› ብሎ ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ባቀረበው ጥያቄ መሠረት ተቀባይነት በማግኘቱ፣ ከቡድኑ ጋር ናይጄሪያ መሄዱን፣ ለቻን ውድድርም ደቡብ አፍሪካ ደርሶ መመለሱንና ከቡድኑ ጋር ሽልማትም እንደተበረከተለት ምንጮች አክለዋል፡፡

No comments: