Saturday, June 7, 2014

የኢትዮ-ኤርትራ የድንበር ጉዳይ ለምን አይቋጭም?

June 7/2014
"የለዘብተኞችና የእስስት” ፖለቲካ ልዩነት እየፈጠረ ነው
ethio er


መለስ በሁለቱ አገሮች ድንበር ላይ “የጅራፍ ድምጽ እንኳን አይሰማም” በማለት ሲመጻደቁበት የነበረው የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት በ”ወረራ” እና “ወረራን መቀልበስ” በሚል ድራማ ተጀምሮ ከተቋጨ አስራ አምስት ዓመት አልፎታል። ኢህአዴግና ሻዕቢያ ጉዳያቸውን በጠረጴዛ ዙሪያ ወይም በጡንቻ መቋጨት ያልቻሉበት ምክንያት ለብዙዎች እንቆቅልሽ ሆኖ እስካሁን አለ። ሁለቱም ወገኖች ድንበር ላይ ወታደር አፍስሰው መቀመጣቸውን አስመልከቶ “አውቀው ነው” ከሚለው ውሃ የማይቋጥርአስተያየት ጀምሮ በርካታ ጉዳዮች በገሃድና በሹክሹክታ ሲሰማ ቆይቷል።
የጎልጉል የዜና ምንጮች ሰሞኑን ከአዲስ አበባ የላኩት መረጃ ግን በይዘቱ የተለየ ነው። ይህንኑ አዲስ ጉዳይ የሚመለከታቸው ክፍሎች አስተያት እንዲሰጡበት ያደረግነው ሙከራ ባይሳካም ዜናው ለውይይት የሚጋብዝ በመሆኑ አትመነዋል።
የድንበር ውዝግቡ አንዲቋጭ ይፈለጋል?
የኢትዮ-ኤርትራ የድንበር ውዝግብ ጦርነት ከኢትዮጵያ ወገን ብቻ ከ100 ሺህ በላይ ጉዳዩ በውል ያልገባቸው ወገኖች ህይወት የተገበረበት ነው። የአይደር ትምህርት ቤት ህጻናትን ጨምሮ የበርካታ ሰላማዊ ዜጎችንና ህጻናትን ህይወትም ቀጥፎ አልፏል። አቶ መለስ ለዚህ ሁሉ ቀውስ ተጠያቂ ቢሆኑም በድንገት ተስፈንጥረው ፍርድ ቤት ህግ ሳይጠቀስባቸው አልፈዋል። “ታላቁ መሪ” በህይወት እያሉ በኤርትራ ጉዳይ በተፈጠረ አለመግባባት ትግራይ ውስጥ እስከመታገት ቢደርሱም ከጥንቃቄ ጉድለት በአንጋቾቻቸው ፈጥኖ ደራሽነት ተርፈው ተቃዋሚዎቻቸውን “ውህዳን” በማለት በየተራ አራግፈው ብቻቸውን “ውርስና ቅርስ” ለመሆን በቅተዋል።
ayider
አይደር
ከህንፍሽፍሽ፣ የልዩነት ጊዜ ጀምሮ አደባባይ የወጣው የልዩነት መሰረት በወቅቱ ይፋ ሲደርግ ኢትዮጵያውያንን አሳዝኖና አስቆጥቶ እንደነበር በወቅቱ በስፋት የተዘገበበት ጉዳይ ነው። ዛሬም ይህ ወቅት ዳግም እየተመለሰ እንደሆነ እየተሰማ ነው። “የኤርትራን ጉዳይ እንቋጭ” የሚሉ የከረረ አቋም ያላቸው ተነስተዋል። እነዚህ ወገኖች ሁለት አማራጭ በማቅረብ ሃሳባቸው ተግባራዊ ሊሆን እንደሚችል እየወተወቱ ነው።
የመጀመሪያው አሁን ያለው የመከላከያ አቅም የድንበሩን ውዝግብ በሃይል ለመቋጨት አቅም እንዳለው እየታመነ ለምን “ቸልተኛነት ተመረጠ” በሚል በቂ ጡንቻ ስለመገንባቱ አበክረው የሚከራከሩበት አግባብ ነው። ሁለተኛው ደግሞ “የኤርትራን ተቃዋሚዎች አደራጅተናል፤ ለምን እነሱ ወደ ኦፕሬሽን አይገቡም” የሚል እንደሆነ መረጃዎቻችን ያስረዳሉ።
ቸልተኞቹ ምን ይላሉ?
በዚህ ጉዳይ ቸልተኛ የሚባሉት የተለየ ምክንያት ያላቸው፣ ነገር ግን “ጦርነት አያዋጣም” በሚል በገሃድ የሚከራከሩ ወገኖች ናቸው። እነዚህ ውስን የብአዴንና የህወሃት ቁልፍ ሰዎች በትግራይ ድንበር አካባቢ አስተዳደር የሚሰሩትን ጨምሮ የኤርትራ ደም አላቸው። በደህንነትና በጸጥታ ክፍሉ አጠቃላይ መዋቀር ላይ ቁልፍ ቦታ ተጎናጽፈዋል። የመረጃ ምንጮቹ ማብራሪያ እንደሚያመለክተው እነዚህ ወገኖች “ኢሳያስን የክፉ ቀን መጠባበቂያ” ነው የሚሏቸው። ሰዎቹ ኢህአዴግ ላይ አንዳችም አይነት ስጋት እንደማይሆኑ የሚታወቅ ሲሆን ዋና ዓላማቸው “ከመሃል አገር ወይም ከመካከል ለውጥ ካልተነሳ አርፈህ ተቀመጥ” የሚል ዓይነት መንገድ የሚከተሉ ናቸው።
ሃሳቡን ሲያብራሩ “ጉዳዩ ስትራቴጂክ ነው” በሚል ነው የሚጀምሩት። ኢትዮጵያዊነት ለሚያንገበግባቸው ህወሃቶች የማይገባቸው ይህ “ቁልፍ ስትራቴጂ” ለማመን የሚከብድ መረጃ ነው። እንደ መረጃው ምንጮች ከሆነ “የመሀሉ አገር ለለውጥ ከተነሳ የመጨረሻ መመሸጊያችን ኤርትራ ናት” የሚል ነው፡፡ እነዚህ የተቀላቀለ ደም ያላቸው ክፍሎች የሚያራምዱት “ቁልፍ” የተባለው ስትራቴጂ “የከፋ ቀን ከመጣ ወንድሞቻችን አይጥሉንም” የሚል ነው። ይህም ተግባራዊ የሚሆነው የቁርጥ ቀን ሲመጣ ለኢሳያስ የሚፈልጉትን በማድረግና በመስጠት ሰላም አውርዶ ህወሃት በገነባው ኢኮኖሚ አማካይነት የንግድ ትስስር መፍጠርና መኖር ነው። በኢትዮጵያ ውስጥ “በማንምና በምንም የማይገሰስ” የንግድ ኤምፓየር በመገንባት ኤርትራን በኢኮኖሚ ድቀት እንድትቀጥል የማድረጉ አካሄድ የ“ቁልፉ” ስትራቴጂ አንደኛው ግብዓት እንደሆነም ይነገራል፡፡
ኢሳያስን “አስልሎ መጣል” በሚለው መርህ ሻዕቢያን መጣል ከተቻለ ኢህአዴግ ያደራጃቸውን ተቃዋሚዎች በመያዝ የሚፈልገውን መንግስት ኤርትራ ላይ የመትከልና ከህወሃት ጋር ተዳቅለው የኖሩት የኤርትራ ደም ያላቸው የኤርትራ ተወላጆችን ወደ ግንባር ማምጣት ነው። በነዚህ ሁለት አማራጭ ሃሳቦች የተተከሉት ከላይ የተጠቀሱት ዓይነት “ለዘብተኞች” ይህንን ሃሳብ ይፋ አውጥተው መከራከርና ማሳመን ስለማይችሉ ጉዳዩ ውስጥ ውስጡን እየተብላላ ወደ ልዩነት እንዳያመራ ስጋት አለ። እነዚህ ስጋት የገባቸው ክፍሎች “ቁልፍ” የሚባለውን ስትራቴጂ “የህወሃት የለዘብተኞችና የእስስት ፖለቲካ” ሲሉ ይጠሩታል።
ከኤርትራና ከኢትዮጵያ የሚንደረደሩ ኃይሎች
ህወሃት/ኢህአዴግና ሻዕቢያ/ኤርትራ አንዱ የሌላውን ተቃዋሚ በይፋ በመደገፍ ሃይል ማደራጀት ከጀመሩ ቆይተዋል። ከሁለቱም ወገን ከፍተኛ የሚባል ሃይል ያላቸው የተቃዋሚ ክፍሎች፣ ድርጅቶች፣ ፓርቲዎች አሏቸው በሚባለው ሃይል ተጠቅመው አንዱ ሌላውን በማጥቃት ነጻ መሬት እስካሁን መያዝ አልቻሉም። ከዚህም ከዚያም ከሚሰሙት መጠነኛ የጦርነት ሪፖርቶች ውጪ ተለቅ ያለ ድል ስለመገኘቱ ከሁሉም ወገን አልተሰማም። ሰፊ ሃይል አለው የሚባለው ደሚትም ሆነ ኤርትራ ላይ መሳሪያ አነሳ የሚባለው የአፋር ቀይ ባህርና ኩናማ ንቅናቄ ስለ ሃይል ግንባታ ከመናገር ውጪ ይህ ነው የሚባል ድል እስካሁን አልጨበጡም።eritrea-opposition-conference
ምንም እንኳን ጥንቃቄና ማስተዋል የሚጠይቅ ቢሆንም ከኤርትራ የሚንደረደሩት የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ሃይሎች፣ ከኢትዮጵያ ይወናጨፋሉ የተባሉት የኤርትራ ተቃዋሚዎች ወደ ተግባር ሳይገቡ ጊዜ መፍጀታቸው “ቁልፍ” የተባለው ስትራቴጂ ሊመረመር የሚገባው እንደሆነ አመላካች እንደሆነ የመረጃው ምንጮችይጠቁማሉ። የኤርትራ ተቃዋሚዎች አዲስ አበባ ላይ የሽግግር መንግስት አቋቁመው፣ መሪያቸውን ሰይመው፣ ህገ መንግሰት አዘጋጅተው፣ ሽግግር ወቅት መተዳደሪያ አርቅቀው፣ የሃይማኖትና የሲቪክ ተቋማትን አካትተው በዝግጅት ላይ እንዲቀመጡ መደረጉ፣ ምናልባትም በኢህአዴግ በኩል ያለው ዝግጅት “ቸልተኛ” በሚባሉት “እስስት ፖለቲከኞች” ታልሞና ታቅዶ የሚከናወን ስለመሆኑ አመላካች አይመስልም? በኢትዮጵያ ወገን ግን ተቃዋሚዎች “እኔ በጠራሁት ሰልፍ ላይ አትገኝም” እየተባባሉ እርስበርስ እየተቆራቆሱ፣ በገጽ ብዛት ብቻ የሚለያይ ተመሳሳይ ማኒፌስቶና ፕሮግራም ይዘው ትግሉን የርስ በርስ አድርገውታል። ከኢትዮጵያ ውጪ ያሉትም በመቀዳደምና በመጠላለፍ ፖለቲካው ተክነውበት የኢትዮጵያ ነጻነት ያደላደሉትን መደብ የሚያፈርስባቸው ይመስል አትላንቲክን ማቋረጥ አስግቷቸዋል፡፡ ሁሉም “እስስት ፖለቲከኛ” መሆን አልቻሉም። የአብዛኛዎቹ የትግል ሁሉ መጀመሪያና መጨረሻ “የምትታገለውን ዋና ባላንጣ ትተህ ያንተው ቢጤውን በመቃረን ዕድሜህን አርዝም” የሚል ያልተጻፈ የፖለቲካ ፕሮግራም፣ የጸና እምነትና ግብ ያላቸው ይመስላሉ።

No comments: