Tuesday, October 14, 2014

ወገኖቻችን ዋጋ ለመከፈል ሲዘጋጁ እኛ ከጎን መቆም አለብን (የትግል ጥሪ)

October 14,2014
አንድነት አዲስ ወጣት አመራር ይዞ ብቅ ብሏል። አቶ በላይ ፍቃዱ። ከዚህ በፊት በተከበሩ ዶር ነጋሶ ጊዳዳና እና የተከበሩ ኢንጂነር ግዛቸው አመራር ወቅት የተጀመሩ መልካም ስራዎችን በማጠናከር፣ በአዲስ አሰራና በአዲስ የትግል ግለት አዲስ ጉዞ ተጀምሯል።

የአንድነት ፓርቲ በአገሪቷ አራቱም ማእዘናት መረቡን የዘረጋ፣ ፍትሐዊና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ከተደረገ ኢሕአዴግን ማሸነፍ የሚችል፣ ብዙ አመራር አባላቱ እየታሰሩበትና ከፍተኛ ጫና እየደረሰበትም፣ የአምባገነኖችን ዱላ ተቋቁሞ የሕዝብን ጥያቄ ለማስከበር የሚተጋ ድርጅት ነው። ሕወሃት/ኢሕአዴግ፣ የአንድነት ፓርቲ፣ በፓርቲዎች ምክር ቤት እንደኮለኮላቸው፣ መድበለ ፓርቲ አለ ብሎ ለማስመሰል ለዲፕሎማሲ ፍጆታ እንደሚጠቀምባቸው፣ ፓርቲ ነን ባዮች ጀሌዎቹ፣ እንዲሆን ነው የሚፈልገው። ነገር ግን አንድነቶች፣ ትልቅ ዋጋ እየከፈሉም፣ ለአገዛዙ ራስ ምታት በመሆን፣ ትግሉን እየመሩት ነው።
ከሐምሌ 2005 እስከ ሰኔ 2006 ባሉት ጊዜያት፣ አንድነት የሚሊዮኖች ድምጽ ለነጻነትና የሚሊዮኖች ድምጽ ለመሬት ባለቤትነት በሚል መርህ በሃያ ከተሞች ተንቀሳቅሷል። በአዲስ አበባ፣ በአዳማ፣ በደሴና በባህር ዳር ሁለት ጊዜ ፣ በአርባ ምንጭ፣ በጂንካ፣ በፍቼ፣ በደብረ ማርቆስ፣ በጎንደር፣ በጊዶሌ፣ በወላይታ ሶዶ አንድ ጊዜ ሰላማዊ ሰልፎችን ጠርቶ ሕዝቡን ያንቀሳቀሰ ሲሆን፣ በአዋሳ፣ በቁጫ፣ በመቀሌና በባሌ/ሮቢ ለቅስቀሳና ለመጓጓዣ ከፍተኛ ወጭ ከተደረገ በኋላ፣ በአገዛዙ አፈና ሰልፎቹ ቢስተጓጎሉም ፣ ቢያንስ በነዚህ ከተሞች ሕዝቡ የነጻነትን ድምጽ በቅስቀሳ ወቅት ለመስማት በቋቷል።
ኢሕአዴግ ከምእራቡ አለም የሚያገኘው እርዳታ፣ በግብር የሚሰበስበው በእጁ ነው። የአገሪቷ አበይት የመገናኛ ተቋማትን ይቆጣጠራል። ኢቲቪ፣ ፋና ፣ አዲስ ዘመን ….በመለስተኛነት ሪፖርተር የመሳሰሉ ሜዲያዎቹ ጠዋትና ማታ የአገዛዙን ፕሮፖጋንዳ ነው የሚረጩት።
አንድነት የሚተማመነው በሕዝቡ ድጋፍ ነው። የአንድነት ብቸኛ የኃይል ምንጭ እኛ ነን። እኛ ከመሪዎች ለዉጥ መጠበቅ የለብንም። እኛ መሪዎችን እየደገፍን የለውጡ አካል ነው መሆን ያለብን።
አንድነት የምርጫው ሜዳ እንዲሰፋና የፖለቲክ ምህዳሩ እንዲከፈት ሕዝባዊ እንቅስቃሴዎችን፣ ሰልፎችን ማካሄድ አለበት። በአገሪቷ ሁሉ ያሉ ሕዝባዊ እንቅስቃሴዎች ለማደራጀት፣ አክቲቪስቶችን አስተባባሪዎችን፣ አደራጆችን በየክልሉ በብዛት ማሰማራት የግድ ነው። እንደ አቶ አንዱዋለም አራጌ፣ ሃብታሙ አያሌው አሁን ያሉትም አመራሮች፣ ነገ ሊታሰሩ እንደሚችሉ እያወቁ ትግሉን ለመምራት የቆረጡ፣ የፓርቲው አመራሮች፣ በራሳቸው ይሄን ትልቅ ሃላፊነት ሊወጡ አይችሉም። እንግዲህ እነርሱ ለመታሰር፣ ለመደብደብ፣ ለመገደል ሲዘጋጁ እኛ ትንሿን የድርሻችንን መወጣት ሊያቅተን አይገባም። አንድነትን ባለን አቅምና ጉልበት ሁሉ ለመደገፍ መዘጋጀት ይኖርብናል።
በአገር ቤት የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን በስፋት ለመከታተል የሚከተለውን የፌስ ቡክ ገጽ ላይክ ያደርጉ
https://www.facebook.com/MillionsOfVoicesForFreedomUdj
በዉጭ አገር ያላችሁ፣ ፓርቲዉን በጽሁፍ፣ ጠቃሚና ፕሮፌሽናል አስተያየቶች በመስጠት ሆነ በማንኛዉም ገንዝበ ነክ ባልሆኑ ጉዳዮች ለመርዳት ፣ የሚሊዮኖች ንቅናቄ ግብረ ኃይል ወይንም የአንድነት ድጋፍ ድርጅት አካል ሆናችሁ መስራት ለምትፈልጉ በሚከተለው አድራሻ ኢሜል ይላኩልን።
millionsforethiopia@gmail.com
በገንዘብ ለመርዳት http://www.andinet.org/ በመሄድ በስተቀኝ በኩል ከላይ «Donate» የሚለውን ይጫኑ !
ነጻነትን ስለተመኘናት አናገኛትም። ነጻነት ርካሽ አይደለችም። ዋጋ ታስከፍላለች። እያንዳንዳችን የነጻነትን ጉዞ፣ የነጻነትን ትግል እንቀላቀል። ከሚሊዮኖች አንዱ እንሁን:: እስካሁን ብዙ የአገዛዙን ግፍ አውርተናል። እስከአሁን ነጻነታችንን ሌሎች እንዲሰጡን ጠብቀናል። እስካሁን ሌሎችን ተችተናል። አሁን ጣታችንን ወደኛ የምናዞርበትና፣ እያንዳንዳችን የምንነሳበት ጊዜ ነው። አሁን ካልተነሳን ፣ አሁን ትግሉን ካልተቀላቀልን መቼ ? እኛ ካልተነሳን ማን ?

No comments: