Friday, March 8, 2013

ዛሬ ከመቸውም በበለጠ ሀገራችን ወደማትወጣው አደጋ እየተገፋች ነው።

    

ባለፉት 21 የወያኔ የግዛት አመታት አይነቱና መጠኑ ይለያይ እንደሆነ እንጅ ጥቃት፣ ግፍ፣ በደልና እብሪታዊ የመብት ገፈፋ ያልደረሰበት ኢትዮጵያዊና የኢትዮጵያ ክፍል የለም። ገበሬው፣ የመንግስት ሰራተኛው፣ የፋብሪካ ሰራተኛና በየዘርፉ የእለት ጉርሱን አሳዶ የሚኖረው ሁሉ የወያኔን የሰቆቃ ግፍ በትር በየተራ አይቶታል፣ እያየውም ይገኛል። የኢትዮጵያ ህዝብ በድህነት አንጀቱ ለፍቶ ያቋቋማቸው ተቋሞቹ እየፈራረሱ ለወያኔ አገዛዝ እንዲመቹ ሆነው ሲጨፈላለቁም አይተናል።
ወያኔ ይህን ሁሉ ያደረገው “አንዱን በአንዴ” በሚል ስልት ነው። መምህራንን ሲያጠቃ የፋብሪካውን ሰራተኛ ተመልካች ያደርገዋል፤ ገበሬውን ሲያጠቃ ከተሜውን ዝም ይለዋል፤ ከተሜው ላይ ሲዘምት ገበሬው ተመልካች ይሆናል፤ ቤተክርሰቲያን ላይ ሲዘምት ቤተ ሙስሊሙ ይመለከተዋል፤ የቤተ ሙስሊሙ የበደል ተራ ጊዜ ቤተክርስቲያን ተመልካች ትሆናለች። ይህ ወያኔን እስከዛሬ ያደረሰው ስልት ነው።
አራዊታዊው የወያኔ አገዛዝ በተመቸውና ይጠቅመኛል ብሎ በአሰበ ሰአት ሁሉ የውብ ህዝብነት ምልክታችን የሆነውን የባህልና የቋንቋ ስብጥርነታችንን እርስ በርስ ለማናከሻነት ሊጠቀምበትም ሞክሯል፤ በተወሰነ ደረጃ አልሰራላቸውም ማለት ያስቸግራል፡፡
ወያኔዎች ከፋፍሎ መግዛትንና በየተራ ማጥቃትን በኪነ ጥበብ ደረጃ አሳድገነዋል ብለው ያምናሉ። በህዝብ ወገን ያለነውም የዲሞክራሲና የነጻነት ሃይሎች ለዚህ አልተመቸንም ማለት ያስቸግራል፡፡ ይህንን ከፋፍሎ የማጥቃት ግፍ በጋራ ለመመከት ያደረግነው ጥረት ህዝባችን ላይ እየደረሰ ካለው ጥቃት ጋር ቢያንስ የሚመጣጠን አይደለም።
የወያኔ መሪዎች ዛሬ ስልታቸውን በማሻሻል አደገኛ ጭዋታ በቤተ እምነቶቻችን ዙሪያ መጫዎት ጀምረዋል። የቤተክርስቲያን እና የአቢያተ መስጊዶችን አስተዳደር በካድሬዎቻቸው ለመቆጣጠር ከሚያደርጉት ሳይጣናዊ ተግባር በተጨማሪ ህዝቡ ሃይማኖት ለይቶ እንዲባላ ለማድረግ በእጅጉ የሚቀፍ ፕሮፖጋንዳ እያካሄዱ ነው። ፍጹም ምሳሌያዊ የሆነውን የኢትዮጵያ ሙስሊሞች የሲቪል መብት ጥያቄ እንደባዕድ መሳሪያነትና እንደ ሽብርተኝነት ለማሳየት እየሞከረ ይገኛል። በኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ውስጥ ሙሉ እጁን በማስገባት የተጀመረውን እርቀ ሰላም በማፍረስ የራሱን እንደራሴ ሰይሟል። ይህም አልበቃ ብሎት ለዘመናት በመከባበር የኖረውን ሙስሊሙንና ክርስቲያኑን እርስ በርስ ለማጋጨት ሌት ተቀን እየሰራ ይገኛል።
ዛሬ ከመቸውም በበለጠ ሀገራችን ወደማትወጣው አደጋ እየተገፋች ነው። ይህንን ወያኔ ያዘጋጀልንን የክፍፍልና ግጭት ድግስ ለመመከት ይበልጥ በአንድነት የምንቆምበት እና የምንታገልበት ግዜ ዛሬ ነው፡፡
ግንቦት 7 የፍትህ፣ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ለወያኔ የ”ከፋፍለህ በየተራ ቀጥቀጥ” ፖሊሲ መድሃኒቱ አንድ ሆኖ በአንድነት አሻፈረኝ ብሎ መነሳት መሆኑን ያምናል፡፡ ወያኔ ጉልበቱ የኛ መከፋፈልና ለክፍፍሉ መመቸት መሆኑን ያምናል፡፡ እኛ ስንተባበርና ልዩነታችንን ለመጠቀም የሚያደረገውን ሙከራ ስናከሽፍና አንዱ ላይ የሚደርሰውን ጥቃት የሁላችንም ነው ብለን የተነሳን እለት ወያኔ የለም።
ግንቦት 7 ንቅናቄ ወያኔ በፈቃዱ የማይታረም ፋሺስታዊ አምባገነን መሆኑን ከተረዳ ሰንብቷል። በመሆኑም ወያኔን በማስገደድ ወይም በማስወገድ ነጻነታችንን መቀዳጀትና ነጻ ሀገር እንዲኖረን ማድረግ አለብን ብለን እናምናለን። ለዚህ ትግልም ማንኛውንም መሰዋእትነት ለመክፈል ተነስተናል። ነጻነትና ኮርተህ በነጻነት የምትኖርባት ሀገር እንድትኖርህ የምትወድ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ተቀላቀለን።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!

No comments: