Wednesday, March 13, 2013

የአውሮፓ ህብረት የልኡካን ቡድን የኢትዮጵያን የሰብአዊ መብት አያያዝ ይገመግማል

 ኢሳት ዜና:-30 አባላት ያሉት የአውሮፓ የሰብአዊ መብቶች የልኡካን ቡድን በኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የሰብአዊ መብቶች አያያዝ ሁኔታ እንደሚገመግም የዲፕሎማቲክ ምንጮች ገለጹ።
የልኡካን ቡድኑ ዋና አላማ በኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የሰብአዊ መብቶች አያያዝ መገምገም ሲሆን፣ ከተለያዩ የፖለቲካ ድርጅት መሪዎች፣ በእስር ላይ ከሚገኙት ጋዜጠኞች እና የሲቪክና የሀይማኖት መሪዎች ጋር ይገናኛል ተብሎ ይጠበቃል።
ይህ በልማት ሽፋን የሚካሄደው የልኡካን ቡድኑ ጉብኝት በኢትዮጵያ የሰብአዊ መብቶች አያያዝ እና ችግሮች ዙሪያ ከተለያዩ የመንግስት ባለስልጣናት ጋር እንደሚነጋገርም ታውቋል።
የልኡካን ቡድኑ በቃሊቲ ጉብኝት እንዲያደርግ ከመንግስት ፈቃድ ያግኝ አያግኝ ለማወቅ አልተቻለም። ይሁን እንጅ በእስር ላይ የሚገኙት የፖለቲካ እና የህሊና እስረኞች ጉዳይ የልኡካን ቡድኑ ከሚያተኩርባቸው ነገሮች መካከል አንዱ መሆኑ ታውቋል።
የልኡካን ቡድኑ ከአፍሪካ ህብረት ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ጽህፈት ቤት ባለስልጣናት ጋር እንደሚነጋገርም ታውቋል።
16 የአውሮፓ ህብረት የፓርላማ አባላት ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እንዲፈታ ለአቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ ደብዳቤ መጻፋቸው ይታወሳል።

No comments: