Wednesday, March 13, 2013

የውጭ አገር ባለሀብቶች በመንግስት ካድሬዎች ተማረናል አሉ

በኢትዮጵያ ውስጥ በኢንቨስትመንት ስራ ላይ የተሰማሩ የአውሮፓ እና አሜሪካ ባለሀብቶች ፣ በመንግስት ካድሬዎችና ሹመኞች በመማረራቸው ስራ ለመስራት በማይችሉበት ደረጃ ላይ መገኘታቸውን ገልጸዋል።
ባለሀብቶቹ ይህን የገለጹት የሁለት አመት ከስድስት ወራት የ እድገት እና ትራንስፎርሜሽንኑን እቅድ ለመገምገም በተጠራ ስብሰባ ላይ ነው።
ሪፖርተር እንደዘገበው ” የመንግሥት ካድሬዎችና የበታች ቢሮክራቶች በውጭ ኢንቨስተሮች መስተንግዶ ላይ የሚያደርሱት መጉላላት ከፍተኛ በመሆኑ ባለሀብቶቹ ኢንቨስት ከማድረግ እንዲታቀቡ እያደረጋቸው ነው።”
የመንግስት ባለስልጣናት ባለሀብቶች ያቀረቡት ቅሬታ ትክክል መሆኑን ለማመን መገደዳቸውን ጋዜጣው ዘግቧል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ጋዜጣው በኢትዮጵያ ውስጥ በሁለቱም ሀይማኖቶች መካከል ለተፈጠረው መከፋፈል በውጭ አገር የሚገኙ ፖለቲከኞችን ተጠያቂ አድርጓል። ሪፖርተር ” በሚያሳዝንና በሚያሳፍር ሁኔታ በእስልምናና በክርስትና ሃይማኖት ተከታዮች ውስጥ መከፋፈል እየታየ ነው፡፡ መራራቅ እየተስተዋለ ነው፡፡ ክፍተት እየተፈጠረ ነው፡፡ በተከፈተው ቀዳዳም ሌሎች ገብተው ለማባባስና እሳት ለማያያዝ ሲሞክሩ እየታየ ነው፡፡ ሕዝብ እንደድሮው በመቻቻል፣ በፍቅርና በመግባባት መኖር ይፈልጋል፡፡ ይህን የማይፈልጉ ቡድኖችና ግለሰቦች ይህን መልካም ጉዳይ ለማበላሸት እየጣሩ ናቸው፡፡ ለግል ጥቅምና ለቡድን ጥቅም ሲባል የሕዝብና የአገር ጥቅም ለአደጋ እየተጋለጠ ነው፡፡ ዋ! ” በማለት ከገለጠ በሁዋላ ፣ ” በሚያሳዝንና በሚያሳፍር ሁኔታ ውጭ አገር የሚገኙ የፖለቲካ ተቃዋሚ ነን ባዮች ዘላቂውን የአገር ጥቅም ከማሰብ ይልቅ ብጥብጡ ለሥልጣን መወጣጫና ኢሕአዴግን ለመጣል ያመቸናል በሚል፣ ጠባብና ከአፍንጫ የማይርቅ የዓይን እይታ በመያዝ አገርንና ሕዝብን የሚጎዳ ቅስቀሳና ያዙኝ ልቀቁኝ እያሰሙ ናቸው፡፡ ለጊዜያዊ ጥቅም ተብሎ የአገርና የሕዝብን ጥቅም ለአደጋ የሚያጋልጥና ለጠላት መሣሪያነት የሚያገለግል እንቅስቃሴ ነው፡፡ በኋላ ይቆጨናል ከወዲሁ ጠንቀቅ” በማለት አትቷል።
ሪፖርተር ጋዜጣ በምርጫ 97 ወቅት የህወሀት/ኢህአዴግ መንግስት ደጋፊ በመሆን አቋሙን በግልጽ ማሳወቁ ይታወሳል። ጋዜጣው በመንግስት ላይ አደጋ ሲፈጠር እና መንግስት ሊወድቅ ነው ብሎ ሲያስብ፣ የማስጠንቀቂያ ደወል እንደሚያሰማ በጋዜጣው ውስጥ ይሰሩ የነበሩ እና ድርጅቱን ለቀው የወጡ ጋዜጠኞች በተደጋጋሚ መግለጻቸው ይታወሳል። ጋዜጣው ካለፉት ሳምንታት ጀምሮ የሚጽፋቸው ርእሰ አንቀጾች ኢህአዴግ እንደ መንግስት የመቀጠሉ ሁኔታ ጥያቄ ምልክት ውስጥ እየገባ መምጣቱን የሚያመለክት ነው በማለት ዘጋቢያችን ከአዲስ አበባ ገልጿል።
ኢሳት ዜና:-

No comments: