Wednesday, March 6, 2013

ኢህአዴግ በርካታ የመረጃ ሰዎችን በሆቴል ቤት ሰራተኝነት ስም ቀጥሮ አሰማራ

    
 
ኢሳት ዜና:-በአዲስ አበባ የተለያዩ አካባቢዎች በሚገኙ ሻሂ ቤቶች፣ ምግብ ቤቶችና ሆቴሎች ውስጥ የ ኢህአዴግ መንግስት ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ወጣት ሴቶችን በማሰልጠን እና አንድ ለአምስት በመጠርነፍ መረጃ እንዲያቀርቡ እያሰማራ እንደሚገኝ ታውቋል። መንግስት ከሻሂ ቤቶችና ሆቴሎች ስራ አስኪያጆች ጋር በሚስጢር በመነጋገር ደሞዝ የሚከፍላቸውን አስተናጋጆች አሰማርቶ ከህዝቡ መረጃ እየሰበሰበ ነው።
ቀደም ሲል መንግስት ሰዎችን በማስረግ ብቻ የመረጃ ማሰባሰቡን ስራ ይሰራ እንደነበር ለዘጋቢያችን የገለጡ አንድ ስማቸው እንዳይነገር የፈለጉ የድርጅቱ ሰው፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በተጠናከረ ሁኔታ እራሱ ደሞዝ የሚከፍላቸውን ሰዎች በተመረጡ የመስተንግዶ ቤቶች መድቧል። ወጣት ሴቶች በትምህርት ደረጃቸው ዲፕሎማ ሳይቀር ያላቸው ሲሆን፣ ድርጅቱ ለረጅም ጊዜ በመረጃ አሰባሰብ ስራ በደህንነት ሰራተኞች እንዳሰለጠናቸውም ታውቋል።
የመረጃ ሰዎች የሰበሰቡትን መረጃ ለተወካያቸው የደህንነት ሰራተኞች በተሰጣቸው የጊዜ ገደብ የሚገልጹ ሲሆን፣ መስሪያ ቤቱም መረጃዎችን በመተንተን ሊከሰቱ የሚችሉ ስጋቶችን አስቀድሞ ለመከላከል ይጠቀምበታል ።
ከመረጃ ሰዎች የሚሰበሰቡትን መረጃዎች በመንተራስ ስርአቱን ይጠላሉ ተብለው የሚጠረጠሩ ሰዎች ውሎአቸው እየታየ የተግባር ግሳጼ መስጠት መጀመሩ ታውቋል።
በተለይ ከተቃዋሚ ፖለቲከኞችና ከግል ጋዜጠኞች ጋር የሚገናኙ ሰዎች ከግሳጼው በሁዋላ ግንኙነታቸውን ከላቋረጡ፣ በገንዘብ ለመደለል፣ ንብረታቸው ሊወሰድባቸው እንደሚችል በማስፋራራት፣ በመንግስት ቤት ውስጥ የሚኖሩ ከሆነም ቤታቸውን እንደሚቀሙ በማስጠንቀቅ በፖለቲከኞችና በህዝብ መካከል ያለውን ግንኙነት ለመበጠስ እቅድ መያዙን ጉዳዩን ሲከታተለው የቆየው አዲስ አበባው ዘጋቢያችን ገልጿል።
ዘጋቢያችን ፒያሳ በሚገኝ አንድ ሻሂ ቤት ውስጥ በመሄድ ስላጋጠመው ገጠመኝ ሲገልጽ ” ከአንድ ባልንጀራየ ጋር ድምጼን ከፍ በማድረግ ስለወቅቱ ፖለቲካ እወያይ ነበር። አንዲት ወጣት መልከመልካም ቀይ ሴት የማስተናገዱን ስራ ትታ ጆሮዋን ወደ እኛ ቀስራ የምንናገረውን ለመስማት ትጥራለች ፤ ጉዳዩን ያልተረዳው የቅርብ ዘመዴ የሆነው የሻሂ ቤቱ ባለቤትና ስራ አስኪያጅ የሚያስተናግደን መስሎ በመምጣት፣ በለሆሳስ ‘የምታወሩትን አቁሙ ልጂቱ እኛ የቀጠርናት ሳይሆን መንግስት የቀጠራት አስተናጋጅ ነች አለን።” ብሎአል።
የሆቴሉ ስራ አስኪያጅ አስተናጋጁዋ ከመንግስት በመጣ ትእዛዝ እንድትቀጠር መደረጉን፣ አብዛኛው ስራዋም ሰዎች የሚነጋገሩትን መቅዳት መሆኑን እና ድርጅቱ ምንም አይነት ደሞዝ እንደማይከፍላት ለዘጋቢአችን አረጋግጠውለታል። የስለላ ሰራተኞች በብዛት ይገኙባቸዋል ተብለው በተጠቆሙት ሆቴል ቤቶች በመዘዋወር ከአንዳንድ ስራ አስኪያጆች ጋር በመነጋገር መረጃውን ያረጋገጠው ዘጋቢያችን፣ አስተናጋጆቹ ሆቴሎች ደሞዝ ባይከፍሉዋቸውም ያለምንም ማንገራገር የተሰጣቸውን መስተንግዶ ስራ ይሰራሉ። የድርጅቶቹ ባለቤቶች ሰላይ አስተናጋጆች እነሱንም የሚሰልሉዋቸው ስለሚመስሉዋቸው ብዙ እንደማይናገሩዋቸው ለማወቅ ተችሎአል።
የደህንነት መስሪያ ቤት ቀጥሮ ካሰማራቸው ሴት አስተናጋጆች በተጨማሪ በኮሚኒኬሽንና ጆርናሊዝም ትምህርት የተመረቁ በርካታ ተማሪዎችን በአሁኑ ጊዜ በአዋሳ የደህንነት ጽህፈት ቤት መረጃ ስለመሰብሰብ፣ መረጃ ስለማስተላለፍ እና መረጃ ስለመተንተን ስልጣና እየተሰጠ ነው።
በኢትዮጵያ የሚታየው አፈና እየጨመረ መምጣት በተለይም የሙስሊሞ እንቅስቃሴ መጠናከር እና ተቃዋሚዎች ይህን እንቅስቃሴ ለራሳቸው ግብ ሊጠቀሙበት ይችላል የሚለው ስጋት እያየለ መሄድ መንግስት በርካታ የደህንነት ሰራተኞችን አሰልጥኖ ለማሰማራት መገደዱ ይገመታል።
የደህንነት ክትትሉ ቢጨምርም፣ ህዝቡ ግን አሁንም ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ ስሜቱን ከመግለጽ ወደ ሁዋላ አይልም።
በቅርቡ በአዳማ ከተማ ይፋ የሆነ አንድ የኢህአዴግ ሪፖርት እንዳመለከተው የአንድ ለአምስት አደረጃጀት የታሰበውን ያክል ውጤት ሊያስገኝ አልቻለም። በብዙ መስሪያ ቤቶች እና ቀበሌዎች ተግባራዊ የተደረገው የአንድ ለአምስት አደረጃጀት ባለመሳካቱ ኢህአዴግ ሌሎች የመረጃ ማሰባሰብ ዘዴዎችን ተግባራዊ ለማድረግ ግድ ብሎታል።

No comments: