Friday, January 3, 2014

እነ ጃዋር ‹‹የጠላቴ ጠላት›› ብልሹ ፖለቲካ = ባለሜንጫው ወደ ኢትዮጵያ

January 3/2014

Image

ያኔ እንዲህ ሳይምታታበት ጃዋር ኦህዴድን ኦሮሞን የሚያስገዙ አዲሶቹ ‹‹ጎበናዎች›› ብሎ ይተች እንደነበር ይታወቃል፡፡ ያኔ ‹‹ከጎበናዎቹ›› ይልቅ ከእነ አንድነት ጋር በመስራት የበኩሉን አስተዋጽኦም አድርጓል፡፡ እያቆየ ግን ጃዋር ከኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች እየሸሸ አሁን አብሯቸው እየሰራ ከሚገኘው ኢህአዴጎች ጎን መሸጎጥ ጀምሯል፡፡ ጃዋር ‹‹እኔ መጀመሪያ ኦሮሞ ነኝ›› ከሚለው አንስቶ ከህወሓት ጋር እንዲተባበር ያስገደዱት የተለያዩ ምክንያቶችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ አንዱና የመጀመሪያው እሱ ‹‹ቀኝ ጽንፍ›› ብሎ የሚጠራቸው ፓርቲዎች ከሌሎቹ የተሻለ እንቅስቃሴ ማድረጋቸው ነው፡፡ ጃዋርና አቶ ቡልቻ ይበልጡን መጥበብ የጀመሩት አንድነት አብሮት መሄድ ካልቻለው መድረክ ይልቅ ከሌሎች ህብረ ብሄራዊ ፓርቲዎች ጋር ትብብር ለመፍጠር ፍላጎት እንዳለው በተነገረበት ማግስት ነው፡፡ ሰማያዊና አንድነት በሰላማዊ ሰልፍና በሌሎች መንገዶች ጠንከር ያለ የፖለቲካ እንቅስቀሴ ሲያደርጉ ደግሞ እነ ጃዋር ‹‹የጠላቴ ጠላት›› ብልሹ ፖለቲካ ውስጥ ገቡ፡፡

ዶ/ር መረራ ጉዲያ በአዲሱ መጽሃፋቸው እንደሚገልጹት 97 ላይ ቅንጅት ጠንካራ እንቅስቀሴ ሲያደርግ ህወሓትም ሆነ ኦህዴድ ‹‹የጸረ ነፍጠኛ›› ግንባር ለቋቋም ጥሪ አድርገውላቸው ነበር፡፡ ዶክተሩ ‹‹አልፈልግም!›› ብለው ባይመልሷቸው እሳቸውም በነ ጃዋር ‹‹አዲስ ጎበና›› ሆነውት አርፈው ነበር፡፡ ይህ ለደ/ር መረራ የቀረበ ጥሪ አንድነትና ሰማያዊ ሲጠናከሩ፣ አሊያም ከአቶ መለስ ሞት በኋላ ኦህዴድ እራሱን ሊያጠናክር፣ ወይንም የዲያስፖራውን ጫና ለመቀነስ ጃዋርና የእነ ለንጮው ኦነግም ‹የጸረ ነፍጠኛው›› ጥሪ ደርሷቸዋል፡፡ ይህን ተከትሎም የእነ ለንጮ ለታው ኦነግ በ2007 ዓ/ም ምርጫ ለመድረስ እየተሰናዳ እንደሆነ እየተወራ ነው፡፡ ኦነግ ለ‹‹ጸረ ነፍጠኛ›› ትግሉ ያመቸው ዘንድ አገር ውስጥ የራሱን ጠባብ ሚዲያዎች ማቋቋም ጀምሯል፡፡ ለአብነት ያህል ከወራት በፊት ‹‹ሰፉ›› የተባለች በኦሮምኛና አማርኛ የምትታተም መጽሄት ገበያ ላይ አውሏል፡፡ ለዚህም የተደራዳሪዎቹ የኦህዴድም ሆነ ህወሓት ይሁንታ እንደሚያስፈልግ አጠያያቂ አይደለም፡፡ የመጽሄቷ ዋና አላማም ስለ አሁኑ ዘመን ጭቆናም ሆነ በደል ሳይሆን ‹‹አማራ በኦሮሞ ህዝብ ላይ ያደረሰውን በደል ማጋለጥ ነው››፡፡ ይህ እንግዲህ የድርድሩም ሆነ የኦነግ ስልት አንዱ አካል መሆኑ ነው፡፡ ህወሓትና ኦነግ የሚስማሙበት አላማ!

በእርግጥ ወደ አገር ውስጥ የሚመለሱት የኦነግ አመራሮች ብቻ አይደሉም፡፡ ጃዋር ሊመለስ እንደሚችልም አንዳንድ ጭምጭምታዎች እየተሰሙ ነው፡፡ ኢህአዴግ ከሌሎቹ ተቀናቃኞቹ ይልቅ ለጃዋር ርህራሄ ማሰየቱን ማሳየቱ አንድ ፍንጭ ነው፡፡ እነ አቡበክር፣ እስክንድር፣ ርዕዮት…. በእጃቸው ምንም ሳይገኝ፣ በፍጹም ሰላማዊነታቸው ‹‹አሸባሪ›› ተብለው ሲፈረድባቸውና ፊልም ሲሰራባቸው የሜንጫ ጀብድን ሲያስተምር የታየው ጃዋር ምንም አልተባለም፡፡ ከእሱ ይልቅ ኮፈሌ ውስጥ ለበቅ የያዙ ወጣቶችን ከቦኮሃራም፣ ከታሊባንና አልቃይዳ ጋር እያመሳሰሉ ‹‹አሸባሪዎች›› ብለው ፊልም ሰርተውባቸዋል፡፡ ከጥቂት ሰዓታት በኋላ ደግሞ ኤሊያስ ክፍሌ ስለ ኤሌክትሪክ ገመድ ማቋረጥ ያወራው ‹‹የአሸባሪዎች ማንነት ማሳያ!›› ተደርጎ ሊቀርብ ነው፡፡ በምን መመዘኛ የኤሌክትሪክ መስመር መቁረጥ የሰው አንገት በሜንጫ ከመቁረጥ በልጦ ‹‹ሽብር›› ሊሆን ይችላል? የጃዋርን ‹‹ጀብድ›› እነ ዶ/ር መረራ፣ ዶ/ር ብርሃኑ፣ የኢሳት ጋዜጠኞች፣ ተመስገን ደሳለኝ፣ አንዱዓለም አራጌ፣ በቀለ ገርባ….አውርተውት ቢሆን ኖሮ ስንት ፊልም ይሰራበት ነበር? ኢህአዴግ ይህንን የጃዋር ጀብድ አሁን ባይጠቀምበትም መቼም አይጠቀምበትም ማለት አይደለም፡፡ ሌሎች እሱ ከእኛ በላይ የሚያውቃቸውንም ሚስጥሮች እንደተደራደረባቸው ሁሉ ወደ አብሯቸው እየሰራ እንዳያፈነግጥም በልጓምነት ይጠቀሙበታል፡፡ እግረ መንገዱን በርካታ ‹‹ፋኦሎችን›› ያሰሩታል፡፡

በእርግጥ ጃዋር በፖለቲካው ከስሮ ወደ አገር ቤት የገባ የመጀመሪያው ሰው አይደለም፡፡ በርካቶቹ ከእሱ በላይ ‹‹ጀግና›› ተብለው ከህወሓት/ኢህአዴግ ብብት ተሸጉጠዋል፡፡ እነ ሰለሞን ተካልኝ ኤርትራ በርሃ ድረስ ሄደው ‹‹በለው!›› እንዳላሉ ተመልሰው ‹‹ይቀጥል!›› ብለዋል፡፡ ሙዚቀኞች፣ ጋዜጠኞች ፖለቲከኞች፣ የእምነት ‹‹አባቶች›› ብቻ በርካቶች እየከሰሩ ተመልሰዋል፡፡ ሲወናበድ የኖረው ጃዋር ተደራድሮ ቢመለስ የሚገርም አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ ለጃዋር አገሩ ናትና መመለሱን የሚጠላ የለም፡፡ ችግሩ በዚህ ስርዓት ምርጫ እንደሌለ ሲናገር እንዳልቆየ ለምርጫ ሊመለስ መሆኑ መነገሩ ነው፡፡ ለኦሮሞ ህዝብ ባለመቆማቸው ኦህዴዶችን ‹‹ጎበናዎች›› እንዳላለ ከህወሓት፣ ብአዴንና ደኢህዴን ስር የሴቶች፣ የትራንስፖርት……ሚኒስቴር ስር ለመስራት ከፈቀደ ነው፡፡ሚኒሊክ ሳልሳዊ

No comments: