Friday, January 17, 2014

መሬታቸው ለህንድ ሻይ ልማት ኩባንያ መሰጠቱን የተቃወሙ ኢትዮጵያውያን ከመንግስት ዱላ ገጠማቸው

January 17/2014

ሰንደቅ ጋዜጣ ከአዲስ አበባ እንደዘገበው፦

በጋምቤላ እና በሸካ አዋሳኝ ክልል ውስጥ ከሚገኙ ህዝቦች መካከል 100 ሺ የሚሆኑ የሸካ ተወላጆች 3012 የሚደርስ ሄክታር መሬት ከአካባቢያችን ጥብቅ ደን ተወስዶ ቨርዳንት ሃርቨስት አግሮ ኢንዱስትሪ ለተሰኘ የህንድ ኩባንያ መሰጠቱን በመቃወማችን ጉዳት እየደረሰብን ነው ሲሉ የብሔሩ ተወላጆች ምሬታቸውን ለሰንደቅ ጋዜጣ ገለጹ። በክልሉ እንደተካተቱት ሌሎች አምስት ብሔሮች ስድስተኛ ሆነን አልተመዘገብንም፤ ልጆቻችን በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው ማስተማር አልቻልንም፤ በክልሉ ተገቢ የሆነ የመሰረተ ልማት ግንባታ ተጠቃሚ አልሆነም፤ ለዚህም አካባቢው የሚካሄደውን ኢንቨስትመንት ተቃዋሚ እንደሆነ ተደርጎ መታሰቡ አግባብ አለመሆኑን የሸካ ህዝቦች ተወካይ በመሆን አቤቱታቸውን ለማሰማት የመጡት አቶ ታምሩ አምበሉ አስረድተዋል።


በጋምቤላ ክልል የመጀንግ ዞን አመራር የሆኑት አቶ ይማም ቃሪስ በበኩላቸው ይህንን አቤቱታ የሚያሰሙት ጥቂት ግለሰቦች የራሳቸውን ፖለቲካዊ ፍላጎት ያላቸውና ተጨፈጨፈ የሚሉትም ጥብቅ ደን ሳይሆን ቁጥቋጦ ነው ብለዋል። አክለውም እንደጋምቤላ ክልላዊ መንግስት ደንብና አሰራር መሰረት የህንዱ ኩባንያ መሬቱን እንዲያለማ መፍቀዳችን ትክክል ነው ይላሉ።

የሸካ ህዝቦች ለዘመናት ጠብቀው ባቆዩት ጥብቅ ደን ውስጥ ማር በማምረት እንደሚተዳደሩ ያስረዱት አቤቱታ አቅራቢዎቹ የአካባቢውን ህዝብ ባላማከለ መልኩ ጥብቅ ደኑን እንዲጨፈጨፍ ማድረግ ከውስጡ የሚመነጩትን ወንዞች መጉዳት ነው ሲሉ ከአካባቢ ጥበቃ አንፃር መፍትሄ ሊበጅለት ይገባል ይላሉ። ይህንንም አስመልክተው በ1999 ዓ.ም የብሔር ብሔረሰቦች መብት ተጠቃሚዎች አይደለንም በሚል ለፌዴሬሽን ምክር ቤት የ1200 ሰዎችን ፊርማ አሰባስበው የመብት ጥያቄ አቅርበው እንደነበር በማስታወስ፤ የመብት ጥያቄያቸው ሳይመለስ እስከ 2002 ዓ.ም መጠበቃቸውንና አልፎም የህዝቡን ዋና መተዳደሪያ የሆነውን ጥብቅ ደን ለማጥፋት ምክንያት ሆኖብናል ይላሉ።

በተለይም የህንዱ ቨርደንት ሃርቨስት አግሮ ኢንዱስትሪ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር በጋምቤላ ህዝቦች ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት መዠንገር ዞን ጎደሬ ወረዳ የጎማሬ ቀበሌ አስተዳደር በሸካ ክልል ውስጥ ከፍተኛ ጥበቃ የሚደረግለትን 3012 ሄክታር ጥብቅ ደን ለሻይ ልማት መፈቀዱ አግባብ አይደለም ሲሉ በተለያዩ መንገዶች አቤቱታቸውን አሰምተዋል። “እኛ ምንም አይነት ኢንቨስትመንትን የመቃወም ኀሳብ እንደሌለን እንዲታወቅልን እንፈልጋለን” የሚሉት የህዝቡ ተወካዮችና አቤቱታ አቅራቢዎች፤ ይህ ቦታ አማራጭ ቢፈለግለት ይሻላል። ደን ከጠፋ ዘራችን የአኗኗር ባህላችን ሁሉ ይጠፋል የሚል እንደሆነም ተናግረዋል። ያም ሆኖ ለኩባንያው ግንባታ ሲባል በ67 ሄክታር ላይ የሚገኝ ደን ተጨፍጭፎ 1640 በላይ ጣውላዎች ወጥተው ተገኝተዋል ሲሉ አስረድተዋል።

ይህን ጉዳይ አስመልክቶ የቀድሞው የኢፌዲሪ ፕሬዝዳንት አቶ ግርማ ወ/ጊዮርጊስ በወቅቱ ለአካባቢ ጥበቃ ኃላፊ በፃፉት ደብዳቤ፤ በጋምቤላ አካባቢ ያለውን የተፈጥሮ ደን ያለበት ሰፊ መሬት ደኑ በጣም ጥቅጥቅ ያለና ለአየር ጥበቃ ሊቆይ የሚገባው ሆኖ ሳለ ለሻይ ልማት ኢንቨስትመንት ተሰጥቶ ሊመነጠር ስለመሆኑ የአካባቢው ህዝብ ይህን ችግር ለማሳወቅ ሰዎች ወክሎ መላኩን በመግለፅ አስቸኳይ እርምጃ እንዲወስድ ማሳሰባቸውን ተናግረዋል።

በበርካታ ባለሙያዎች ጥናት ተደርጎለት የአካባቢው የደን ሀብት እንዲጠበቅ ቢወሰንም አሁንም ድረስ የተሰራ ስራ አለመኖሩንና የአካባቢው ህዝብም ስጋት ላይ መሆኑን በመጥቀስ ህዝብና መንግስት ጉዳያችን ተረድቶ ጥብቁን ደን ከጥፋት ይከላከለው ዘንድ ድምጻችንን እናሰማለን ብለዋል፤ አቤቱታ አቅራቢዎቹ።

የመጀንግ ዞን አመራር በሰጡት ምላሽ ቦታው ጥናት ተደርጎበት ለልማት የተመራ መሆኑን በመግለፅ፤ ኩባንያው የሻይ ልማት ስራውን ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ እየሰራ እንደሚገኝና ነገር ግን ጥቂት የግል ፍላጎት ያላቸው ግሰቦች እንቅፋት የሚሆን እንቅስቃሴ አድርገዋል ሲሉ ይወቅሳሉ።

ዘ-ሐበሻ

No comments: