Tuesday, January 21, 2014

የደህንነት ሰራተኞች ሃላፊነታችን ለአገር ወይስ ለፖለቲካ ስርአቱ ነው የሚል ጥያቄ አነሱ

January 20/2014

ጥር ፱ (አስራ ሁለት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-መንግስት በመረጃዎች አያያዝ ዝርክርክነት ፣ በሳይበር በሚደረጉ ስለላዎች እና ከውስጥ ባሉ የመንግስት አካላት እየሾለኩ በሚወጡ መረጃዎች ህልውናየ አደጋ ላይ ወድቋል በማለት ግመገማ ማድረጉን ተከትሎ  ”የደህንነት ሰራተኞች ሃላፊነታችን ለማን ነው?” የሚል ጥያቄ ማንሳታቸውን  ከደህንነት መስሪያ ቤት ለኢሳት የደረሰው በድምጽ የተደገፈ መረጃ አመለከተ። በስብሰባው ላይ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት እና የመንግስት ሹሞችም ተገኝተው ነበር።

ጥያቄውን ያነሱት በፌደራል ስር የሚገኙ የደህንነት ስራተኞች እና ቀደም ብሎ በአቶ መለስ ዜናዊ ዘመን በትግራይ ውስጥ በመቀሌ ዩኒቨርስቲ ሽፋን የተቋቋመው ኤም አይ ቲ እየተባለ በሚጠራው ከመቀሌ ከተማ 9 ኪሎሜትር ርቀት ላይ በተገነባው ተቋም ውስጥ ተመርቀው የወጡት የደህንነት ሰራተኞች ናቸው።

የደህንነት ሰራተኞቹ “የእኛ ሃለፊነት የአገር ደህንነትን ማስጠበቅ ነው የፖለቲካ ስርአቱን ?” በሚል  ጥያቄ ያነሱ ሲሆን፣ አንድ  የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣን  ” የፖለቲካ ስራ የማይሰራ ደህንነት የለም፣ የደህንነት ስራ ሲጀመር ስርአት የማቆየት ስራ ነው፤ ስርአቱን የምናቆይበት ደግሞ ፕሮፌሽናል ነው፣ በስርአቱ ላይ እምነት ማሳደር የሚጠይቅ ተግባር ነው፣ የግንቦት7ትን አስተሳሰብ የሚያቀነቅንና ስርአቱ በጉልበት መፍረስ አለበት ብሎ የሚያስብ ሰው፣ የተስፋየ ወልደ ስላሴ አይነት የደህንነት ብቃት አለው ቢባል፣ ሞሳድ 20 አመታት አሰልጥኖታል ቢባል ስርአቱን ከማፍረስ ውጭ ደህንነቱን ሊያስጠብቅ አይችልም” ፣ ስለዚህ የደህንነት ስራ ለሚሰሩ ወገኖች የፖለቲካ ወገንተኝነታቸው ወሳኝ ነው የሚል መልስ ሰጥተዋል ።

“የደህንነት ተቋሙ ፣ ሰራዊቱና ሚዲያው በተቃዋሚዎች ዘንድ መቼውንም ቢሆን ገለልተኛ ተደርጎ አይቆጠርም” ያሉት እኝህ ከፍተኛ ባለስልጣን ፣ ገለልተኛ ማድረግ የሚባል አስተሳሰብ ያለው ካለ እንደዛ ሊሆን አይችልም፣ ሊሆን የሚችለው የተቃዋሚዎችን ሰዎች ደህንነት ውስጥ ማስገባት ነው ብለዋል። ” በተለይም በተቋም ደረጃ ፤በምህጻረ ቃል ኢንሳ እየተባለ የሚጠራው የመረጃ ደህንነት መስሪያ ቤት፤ የዜግነት እና ኤምግሬሺን ፤የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፤በጀኔራል ሳሞራ የኑስ የሚመራው የመከላከያ ደህንነት ፤የአስተዳደር እና ፀጥታ ፤ የፌደራል ፖሊስ ፤ የፀረ ሽብር ግብረ ሃይል በእዝ ሰንሰለት በሚፈጠር ልዩነት እርስ በርስ እየተወዛገቡ ሲሆን፣ ተቋሞቹን በትክክል የሚመሩትን አካላት  ለመለየት አስቸጋሪ ሆኖ መገኘቱና እርስ በርስ በሚፈጥሩት  እሰጥ አገባ  አንዱ አንዱ የሚሰራውን የማጠፋፋት እርምጃ እየወሰዱ መሆኑ በግምገማው ላይ ተነስቷል፡፡

የመንግስት ሚስጥሮች ለሶስተኛ ወገኖች ተላልፈው እየተሰጡ በመሆኑ ሚስጢሮችን  መደበቅ የማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል ሲሉ አንዳንድ ባለስልጣኖች አስተያየቶችን ሰጥተዋል።
ለተነሱት አስተያየቶች መልስ የሰጡት ባለስልጣኑ፣ ኢንሳ የተቋቋመውም ይህን ለመስራት መሆኑን  ገልጸው፣ “አገሮች ሙሉ በሙሉ ከሳይበር ስለላ ነጻ ባለመሆናቸው አቶ ሃይለማርያምም ነጻ ናቸው ብየ አላስብም” ብለዋል። “አሜሪካኖች የምንናገረውን ሁሉ ከፈለጉ ይሰሙታል” የሚሉት እኝሁ ባለስልጣን፣ “እኛም የአቅማችንን ያክል አሜሪካኖች የሚናገሩትን ለማዳመጥ እንሞክራለን” ብለዋል። የሳይበር ስለላ ለማካሄድ ጥሩ ጅምሮች ቢኖሩም፣ ያን ያክል የምንኩራራበት ግን አይደለም በማለት ኢነሳ ያለበትን ደረጃ አመላክተዋል

ከኦሮሚያና ከደቡብ የመጡ የደህንነት ሹሞች ደግሞ “በመከላከያ የደህንነት ተቋሞች ውስጥ የአንድ ብሄር የበላይነት ጎልቶ ይታያል” በሚል ቅሬታ ያነሱ ሲሆን ፣ ባለስልጣኑም “የሰራዊት ማመጣጠን ስራ በረጅም ጊዜ የሚሰራ ስራ  ነው ” በማለት ለመመለስ ሞክረዋል።

” ትግሉን መርተው እዚህ ድረስ የመጡ ሰዎችና በመከላከያ ውስጥ ያለውን የመኮንኖች ቦታ የያዙት ከአንድ አካባቢ የመጡ መሆናቸው ግልጽ ነው የሚሉት ባለስልጣኑ፣ ያም ሆኖ ከትግራይ የመጡ በርካታ ጄኔራሎች ጡረታ እንዲወጡ ቢደረግም ሂደቱ ግን ረጅም ጊዜ የሚወሰድ ነው ሲሉ አክለዋል።

“የብሄር ተዋጽኦ ብቻ የአንድን ሰራዊት ጠንካራና ደካማ ጎን መገለጫ ተደርጎ መወሰድ ካለበት አደጋ አለው ” ያሉት ባለስልጣኑ፣ የአንድ ብሄር የበላይነት አለ ተብሎ በአጭር ጊዜ ለማመጣጠን ብቻ በአንድ አዳር ሁሉንም ነገር መቀየር እንደማይቻል መንግስት ያምናል ሲሉ ተናግረዋል

አቶ መለስ ዜናዊ በውጭ ሃይሎች ተገድለዋል ይባላልና በምን እንደሞቱ በትክክል ይነገረን በሚል ባለስልጣናት ላነሱት ጥያቄም የደህንነት ባለስልጣኑ፣ “አቶ መለስ በውጭ ሃይሎች ተገድለዋል የሚል ትክክለኛ ማስረጃ የለም በማለት መመለስ የጀመሩት ባለስልጣኑ፣ እርሳቸው የሞቱት በስራ ብዛት ተዳክመው እና ህክምናውን መቋቋም ባለመቻላቸው ነው ሲሉ ደምድመዋል።
በተያያዘ ዜናም የሃገሪቱን ደህንነት አደጋ ላይ ለመጣል ከኢሳት ጋር በመሆን እየሰራችሁ ነው፣ ለኢሳትም መረጃ ታቀብላላችሁ  ተብለው የተጠረጠሩ  5 የደህንነት አባላት በቁጥጥር ስር ውለዋል።  ወጣት መብራቴ ታምራት ፤ወጣት ጀማል አወል ፤ወጣት ደጀኔ አድማስ ፤ ወጣት ሃይሉ ጨርቆስ ፤መቶ አለቃ አሰፋ አብርሃ ሰሞኑን በደህንነቶች ቁጥጥር ስር መዋላቸውን የኢሳት የደህንነት ምንጮች ገልጸዋል።

በተመሳሳይ ዜናም በሃገሪቱ በ28ቱ ዩኒቨርስቲዎች የሚገኙ የህወሃት አባላት ተማሪዎች እና የደህንነቶች ሃለፊዎች ግምገማ መጀመራቸውን ለማወቅ ተችሎአል።
በግምገማው ወቅት የኦህዴድ እና የብአዴን መሪዎች የተማሪዎችን እንቅስቃሴ በመከታተል ባሰዩት ውጤት የተገመገሙ ሲሆን፣ ባለፉት ስድስት ወራት የአክሱም ፤ ደብረ ታቦር እና ደብረ ብርሃን የኒቨርስቲዎች ከፍተኛ የአመጽ እንቅስቃሴ የታየባቸው በመሆኑ ልዩ የደህንነት ክትትል እንደሚያስፈልጋቸው ተወስቷል።

No comments: