Sunday, January 19, 2014

ሌንጮ ባቲ “ኦቦ ሌንጮ ፊንፊኔ አልገቡም፤ ኖርዌይ ነው ያሉት፤ በቅርቡ በግልጽ እንገባለን” ሲሉ የአዲስ አድማስን ዘገባ አስተባበሉ



(ዘ-ሐበሻ) የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ግምባር የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሌንጮ ባቲ ከዘ-ሐበሻ ጋር በስልክ ባደረጉት ቃለ ምልልስ የድርጅታቸው መሪ አቶ ሌንጮ ለታ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ዛሬ እንደጻፈው ኢትዮጵያ አልገቡም፤ ኖርዌይ ነው ያሉት አሉ። ዛሬ ኦቦ ሌንጮ ባቲን ኖርዌይ ደውዬ በስልክ አዋርቻቸዋለሁ ያሉት አቶ ሌንጮ ኢትዮጵያ የምንገባው በድብቅ ሳይሆን በግልጽ ነው ብለዋል። ድርጅታችን ሃገር ቤት ገብቶ መታገልን የወሰነው አሁን አይደለም ያሉት አቶ ሌንጮ ባቲ በቅርቡ ኢትዮጵያ እንደሚገቡ፤ የአዲስ አድማስ ወሬ መሠረተ ቢስ ነው ሲሉ አስታውቀዋል።

ከዘ-ሐበሻ ጋር ያደረጉትን አጭር ቃለ ምልልስ ለማድመጥ ይኸው ሊንኩ



የአዲስ አድማስ ጋዜጣ እንደወረደ ዘገባ የሚከተለው ነው፡-

በኢትዮጵያ መንግስት “ሽብርተኛ ተብሎ የተሰየመው የኦሮሞ ነፃ አውጪ ግንባር /ኦነግ/ ከፍተኛ አመራር የነበሩት አቶ ሌንጮ ለታ፣ አዲስ ያቋቋሙትን ፓርቲ ይዘው በሰላማዊ መንገድ ለመታገል አዲስ አበባ መግባታቸውን ምንጮች ገለፁ፡፡ ኢህአዴግ የደርግ ስርዓትን አስወግዶ አዲስ አበባን ሲቆጣጠር ከአቶ መለስ ዜናዊ ጋር ለፕሬዝዳንትነት እንዲወዳደሩ ተጠቁመው አልፈልግም ማለታቸው የሚነገርላቸው አቶ ሌንጮ፤ ወደ ሰላማዊ ትግል መግባታቸውን በተመለከተ ብዙዎች አምነው እንዳልተቀበሏቸው የገለፁ ሲሆን ከሶስት ቀናት በፊት አዲስ አበባ መግባታቸው ታውቋል፡፡ በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ኢትዮጵያ መግባታቸውን አስመልክቶ የቀድሞ ድርጅታቸው ኦነግ ስላለው አቋም ከውጭ ሚዲያዎች የተጠየቁት አቶ ሌንጮ፤ “እሱን ኦነግ ነው የሚያውቀው” ሲሉ መልሰዋል፡፡ የአቶ ሌንጮ ለታን ወደ ሀገር ቤት መመለስ አስመልክቶ አስተያየት የተጠየቁት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፤ ቀደም ሲል ኦነግ በሁለት አመለካከቶች መሃል ሲዋልል የነበረ ፓርቲ መሆኑን ይገልጻሉ፡፡ አንደኛው፤ ኦሮሚያ ሙሉ ለሙሉ መገንጠል አለባት የሚለው ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ትገንጠልም አትንገንጠልም በሚለው አመለካከት መሃል የሚዋልል ነበር ይላሉ፡፡

አሁን የእነ አቶ ሌንጮ ወደ ሠላማዊ ትግል መመለስ፣ በኢትዮጵያ አንድነት እምነት የነበረው አካል ተለይቶ መውጣቱን ያመለክታል ብለዋል፡፡ ይህም በበጐ የሚታይ ነው ያሉት ዶ/ር ነጋሶ፤ ለኢትዮጵያ ህዝብና ለኦሮሞ ህዝብ ትግል መልካም መንገድ እንደሚከፍትም ያላቸውን እምነት ገልጸዋል፡፡ ዶ/ር ነጋሶ ቀደም ሲል በኦነግ የፖለቲካ ትግል ውስጥ ማለፋቸውን “ዳንዲ፣ የነጋሶ መንገድ” በሚለው መጽሃፋቸው ጠቁመዋታል፡፡ ከኦነግ ዋና ዋና መሪዎች አንዱ የነበሩት ሌንጮ ለታ “ወደ ሰላማዊ ትግል ተመልሻለሁ” ማለታቸውን መንግስት ያውቀው እንደሆነ የተጠየቁት የመንግስት ኮሚዩኒኬሽን ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል፤ በበኩላቸው፤ በግለሰብ ደረጃ የተሟላ መረጃ እንደሌላቸው ጠቁመው፣ አንድ ሽብርተኛ ተብሎ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተሰየመ ድርጅት ወደ ሰላማዊ ትግል መመለሱ የሚረጋገጥለትና ስያሜው የሚነሳለት ግን በራሱ በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ነው ብለዋል፡፡ አቶ ሌንጮ ለታን በአካል አግኝተን ለማነጋገር ያደረግነው ጥረት አልተሳካም፡፡

ከቀናት በፊት ኦቦ ሌንጮ ለጀርመን ድምጽ ራድዮ የሚከተለውን ብለው ነበር፦


  ዘ -ሐበሻ

No comments: