Monday, January 27, 2014

የአገር አቋራጭ አውቶቡስ ተገልብጦ 17 ሰዎች ሕይወታቸው አለፈ፤ የ2 ዓመት ህፃን ሕይወቱ ተረፈ

January 26/2014


(ዘ-ሐበሻ) ከሞያሌ ወደ ሻሸመኔ ተጓጓዦችን ጭኖ ይጓዝ የነበረ አንድ አገር አቋራጭ አውቶቡስ ተገልብጦ የ17 ሰዎች ሕይወት ማለፉ ተሰማ። የ2 ዓመቱ ህፃን ምንም ጉዳት ሳይደርስበት ሲተርፍ፤ ሌሎች 31 የሚሆኑ ሰዎች ግን ከባድ የአካል ጉዳት እንደደረሰባቸው ለዘ-ሐበሻ የደረሱት መረጃዎች አመልክተዋል።

ትናንት ማምሻውን ከሞያሌ ወደ ሻሸመኔ ሲጓዝ የነበረው ሃገር አቋራጭ አውቶቡስ የተገለበጠው በይርጋ ጨፌ ወረዳ ቆንጋ ቀበሌ እንደሆነ ሲገለጽ የአካባቢው የትራፊክ ፖሊስ በሰጠው መግለጫ ለአደጋው መንስኤ በፍጥነት ማሽከርከር ነው ተብሏል። ፖሊስ ጨምሮም መንገዱ ከፍተኛ ቁልቁለት የነበረው ሲሆን ሹፌሩ ሃላፊነት በጎደለው መልኩ በፍጥነት በማሽከርከሩ አደጋው ሊከሰት እንደቻለ ገልጿል።

በዚህ አካባቢ የተለያዩ የትራፊክ አደጋዎች በተለያየ ጊዜ እንደሚደርስ የጠቆሙት የአካባቢው ነዋሪዎች አደጋዎች በሹፌሮች አማካኝነት ይፈጠሩ እንጂ መንግስትም ተጠያቂ ነው ይላሉ። በተለይ ይህ ቦታ ብዙ የመኪና አደጋ የሚደርስበት ቢሆንም ትራፊክ ፖሊስ በሙስና በመጨማለቅ በፍጥነት በሚያሽከረክሩ ሰዎች ላይ ተገቢውን ቅጣት እንደማይጥሉባቸው የገለጹት እነዚሁ ታዛቢዎች ከአስተዳዳሪው ጀምሮ በሙስና የተጨማለቁ በመሆናቸውና ትራፊክ ፖሊስም የሚገባውን ሥራ ስለማይሰራ ለአደጋዎቹ መበራከትም ምክንያት ነው። በተለይ በኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት የአንድ ትራፊክ የወር ደመወዝ አንድ ሰው ለአንድ ምሽት በሬስቶራንት 2 ሰው ራት የሚጋብዝበት ሂሳብ መሆኑ ፖሊሶቹ በሙስና ላይ እንደሚሰማሩ ታዛቢዎች ለዘ-ሐበሻ ዘጋቢዎች ገልጸዋል። በተጨማሪም በይርጋ ጨፌ ወረዳ በቂ የትራፊክ ምልክቶች አለመኖራቸው ለአደጋው መበራከት እንደምክንያት ያቀርባሉ።

በዚህ የመኪና አደጋ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል የታወቀ ሲሆን አብዛኞቹ በዲላ ሆስፒታል ህክምና ላይ እንደሚገኙ ጨምሮ የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

ከዚህ ቀደም በዘ-ሐበሻ ድረ ገጽ ላይ ይህን ጥናት ስለመኪና አደጋ አቅርበን ነበር። በድጋሚ እነሆ፦
በዓለም የጤና ድርጅት (WHO) የ2012 ሪፖርት መሰረት በዓለማችን በዓመት 1ሚሊየን 3 መቶ ሺ ህዝብ በትራፊክ አደጋ ህይወታቸው እንደሚያልፍ ሲታወቅ በኢትዮጵያ በተደረገ ጥናት ደግሞ በዓመት ክ2000 ሰዎች በላይ በመኪና አደጋ ሕይወታቸው ያልፋል።
ለመኪና አደጋ መንስኤ ተብለው ከሚጠቀሱት መካከል በፍጥነት ማሽከርከር፣ ለእግረኞች ቅድሚያ አለመስጠት፣ የሌሊት ጉዞ፣ ደርቦ ማለፍ፣ ከአቅም በላይ መጫን፣ አደንዛዥ ዕፅ መጠቀምና ጠጥቶ ማሽከርከር ከመንስኤዎቹን መሀል ዋነኞቹ እንደሆኑ ታውቋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የተሽከርካሪ የቴክኒክ ጉድለት ወይም ብልሽት፣ የእግረኛ ግራ መንገድ ይዞ አለመሄድና የማቋረጫ ምልክቶችን (ዜብራ) በአግባቡ አለመጠቀም፣ የመንገዶች በጥራት አለመሰራትና የመንገድ ላይ ምልክቶች ተሟልተው አለመዘጋጀት ለአደጋው እንደመንስኤ የቀረቡ ናቸው፡፡

ዘ -ሐበሻ

No comments: