Wednesday, November 20, 2013

በግጭት መካከል የሚሰራ ጋዜጠኛና ለመረጃ ፍቅር ያለው ዜጋ ህይወት

November 20/2013

 ዛሬ ሳውዲ አረቢያ በተለይም በመንፉሃ ሪያድ የተከሰተውን ሁከት ተከትሎ መረጃዎችን ስንለዋዎጥ ባጅተናል ። አሰቃቂውን የወገን ጉዳት አብረን አውግዘን ፣ ወገኖቻችን ደራሽ ያገኙ ዘንድ ኢትዮጵያውያን ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ በመላ አለም ያሰማነው ድምጽ ፍሬ አፍርቷል ! ደስ ሲል …  በሁከቱ የተፈጠረውን ችግር ፣ የፈሰሰውን እንባና ደም የአይን ምስክሮችን በአካል ላነጋገረና ህመሙን ሲታመም ለከረመ የእኔ ቢጤ ዛሬ የተገፊው ወገን ችግሮች ተቀርፈው ማየትና መስማት ቢችል ከምንም በላይ እንደሚያስደስት ቃላት የሚገልጹት አይሆንም!  ከሁከቱ ዋዜማ ጀምሮ በሁከቱና ከሁከቱ በኋላ ባሉት ቀጣይ ቀናት የእለቱን ክንዋኔ በቅርብ  ተከታትየዋለሁ ። ሁከቱ ሲግም “ጋመ !”  በማለትና ወገን ግፍ ሲበዛበት የዋይታ ድረሱልኝ ድምጹን የማሰማቴን ያህል ሃገር ሰላም ሲሆን መረጃ አጣቅሸ ” ሃገሩ አማን ነው! ጸጥ ረጭ ብሎ ረግቷል ” አላለሁ  … ይህን ሳደርግ ተቃውሞና ድጋፉ በሁሉም አቅጣጫ እንደ ጎርፍ ይወርድኛል  !  ይህን መሰሉን ኑሮ ከወጣትነት እስከ ጎልማሳነት የጋዜጠኝነት እድሜየ የገጠመኝ መሰናክል፣ የኖርኩበትና የማውቀው በመሆኑ አልደነቀኝም!


      ይህን ሁለት ሶስት ቀን በሳውዲ አረቢያ ዋና ከተማ ሪያድ ውስጥ በምትገኘውንና ብዙ ኢትዮጵያውያን የሚኖሩባት የነበረችውን የመንፉሃን መንደር ጨምሮ በመላ ሪያድ የሚገኙትን ከስልሳ በላይ መጠለያዎች ሁኔታ በቅር እከታተላለሁ ። በጅዳ መካና በተለያዩ የሃገሪቱ ክፍ  ስላለው እንቅስቃሴ  ከተለያዩ የማህበረሰቡ አካላትና በተለይም በጊዜያዊ እስር ቤት ያለውን ጭብጥ መረጃዎችን አገኛለሁ ።  ነባራዊ የዜጎቻችን አያያዝና እየሆነ ያለውን ከክስተቶች ጋር ገምግሜ ተደጋጋሚ መረጃዎች ማቅረቤ ያልተመቻቸው ” ይህን ሶስት ወን የምታቀርበው ተረጋግቷል የሚል መረጃ አይመችም  ፣  ይህም  ከታች ያሉት እንዳይረዱ አንቅስቃሴውን አበረድከውሳ? ! ” በሚል የሰላ ወቀሳ አቅርበውልኛል ። የመንግስት ደጋፊዎች ደግሞ በአንጻሩ  በአንጻሩ “መንግስት እየወሰደው ያለውን እንቅስቃሴ አትዘግብም !” በማለት ይቃወሙኛል። አንዳንዴማ ሙግታቸውን ያወርዱታል። በሳውዲ ሪያድ መንፉሃ የቤት ለቤት አሰሳ ዝርፊያ ፣ማሳደድ ፣ድብደባ፣ ሴቶችን የመድፈር እና የግድያው ጥቃት በእኛ ላይ ህግና መመሪያ ተጥሶ መሆኑ ግንዛቤ ሳይኖራቸው ቀርቶ ይሁን አውቀው ” በሳውዲ በእኛ ላይ የተለየ የተወሰደ እርምጃ የለም! ” ብለው ቅር ያሰኙኝን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩን ብቻ “አወድስ !” ለማለት ይከጅላቸዋል። በትዊተር ጠቃሚ መረጃን የሚሰጡን ዶር ቴዎድሮስ አደሃኖም  ድምጻቸውን እስካሁን ካልሰማነው ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለ ማርያም ደሳለኝ የተሻለ እንቅስቃሴ አድርገዋል ብልም ለአሁኑ ችግር መንስኤ መስሪያ ቤታቸው ድርሻ አለው ለምለው እማኝ ሚኒስትሩ ጥሩ ሰሩ እንኳ ቢባል ብቻቸውን ስራውን እየሰሩት እንዳለ ተደርጎ አድሃኖምን በመለስ ቦታ ለማስቀመጥና ” ለማምለክ !” እየተኬደ ያለው ፕሮፖጋንዳ በስራየ ላይ ተጽዕኖ እንዲያደርግ ይሞክራሉ።  ከሁሉም የሚደንቀው በስልጡኑ ሚኒስትር ዶር ቴዎድሮስ የሚመሩት የሳውዲ አረቢያ ዲፕሎማቶች መረጃን አልቀበል አልሰጥ እያሉ ፍዳችን እያሳዩን ነው!
አዎ !  ዛሬም ነገም በግጭት መካከል የሚሰራ ጋዜጠኛ ኑሮ ከዚህ ያለፈ አይደለም !   … ትናንት ምሽት ካንድ ብርቱ ወዳጀ ለስለስ ብሎም ቢሆን የተሰነዘረብኝ ወቀሳ ግን ከዚህ በፊት ሞነጫጭሬያት የነበረችን የማለዳ ወጋወግ ሳብ አድርጌ ይህን መግቢያ ሰርቸ ወደ እናንተ እንዳደርሰው ምክንያት ሆነኝ  …  በግጭት መካከል የሚሰራ ጋዜጠኝነት ህይወት እንዲህ ነው!
መረጃ ስላለው ጠቀሜታ ያለኝ እምነት ጽኑ ነው፡፡ ይህ በመሆኑም የግል ፍላጎቴ ሆኖ በአረቡ አለም በሀገሬንና በዜጎቻችን ዙሪያ  የሚለቀቁ መረጃዎችን በቅርበት እከታተላለሁ ! የማገኘው መረጃ ትክክለኛ ለመሆኑ አስቀድሜ እጠነቀቃለሁ ፡፡ ተገቢ መረጃዎችን አሰባስባለሁ ፡፡ የዜናውን ክብደትና አስፈላጊነት አውጥቸ አወርዳለሁ ! ከዚያም እውነታው እንዲህ ነው ብየ መረጃን በትክክል ማግኘት ላለበት ወገኔ አቀርባለሁ፡፡ ዋናው ቁምነገር የያዝኩት መረጃ  እስከሆነ ድረስ የሚያሳስበኝ ነገር የለም ! ሁሉንም መረጃዎች ማቅረብ ባልችልም ይጠቅማሉ የምላቸውን መረጃዎች ለማካፈል ጥረት አደርጋለሁ፡፡  በአረብ ሃገር እንደ ሌላው ሃገር መረጃን ለማድረግ ቀላል አይደለም፡፡ ብዙ ድካም አለው ፡፡ ያም ሆኖ አስቸጋሪ የሆነው ውስብስብና አደገኛ የመረጃ ስብሰባ እኔን አያደክመኝም ! አይታክተኝምም  !
     መረጃውን ከወዲያ ወዲህ ቧጥጨና ፈልፍየ “እውነቱ ይህ ነው !” ስል የሚሰማኝ የደስታ ስሜት ከምንም በላይ ነው !  አዎ መረጃዎችን ሳቀርብ ከፊትና ከኋላ የሚሰነዘርበኝ በጎና በጎ ያልሆኑ አስተያየቶች መጠነ ሰፊ ናቸው፡፡  ባንድ ወቅት የማቀርበውን የሚወዱት በሌላ ጊዜ ይቃዎሙታል ! እኔኑ እንደ ግለሰብም ይጠሉኛል ብቻ ሳይሆን ድምጥማጤን ለማጥፋት ምለው ይገዘታሉ ! አንዳንዴ ደግሞ ይቃወሙኝ የነበሩት ያቀረብኩት መረጃ እንዳስደሰታቸው መጠን ይደግፉኛል ! ያሞካሹኛልም ! ይህ ሁሉ መረጃውን በአየር ላይ ባቀረብኩ ቅጽበት የሚስተዋል እውነታ ነው፡፡  ይህ ሁሉ ሲሆን እኔ የማንም ድርጂት አባልና ተቀጽላ ሆኘ ከማንም እንቅስቃሴ ላይ ቀዝቃዛ ውሃ  ለመቸለስና የማንንም ትግል ለማኮሸት አይደለም፡፡ የሚሰማኝ እንደ ዜጋና እንደ ባለሙያ መረጃ ማቀበሌ ብቻ ነው የማውቀው ! ብዙዎች የሚደሰቱበትን መረጃ አቀብየ ሁሉንም ደስ ላሰኝ አልልም ፣ ብዙዎች ሲደሰቱ በእርኩስ መንፈስ ደስታቸውን ለማደፍረስና አንገታቸውን እንዲደፉ አስደናጋጭ መረጃ ማቀበሉንም ነፍሴ ፍጹም አይፈቅደውም  !
      በመረጃ ቅበላው ዙሪያ አንዱን ወገን በማደሰትና ሌላውን በማስከፋት የመረጃ ፍሰቱን ላዛባው ህሊናየ አይፈቅድም ! የምወደው ሙያ ነውና ላረክሰውም አልሻም ! ይህ እስከሆነ ድረስ የማቀርበው መረጃ እውነተኛ ድርጊቱን እስከ ሆነ ድረስ ሁሉንም የሁሉንም ስሜት በአንድነት መግዛት አይቻለውምና የተቃውሞም ሆነ የድጋፍ አስተያየቶች ማስተናገድ ግድ ይላል ፡፡ ሁሉም በአግባቡና በጨዋ መንፈስ በየፈርጁ ሲቀርቡ ያስደስቱኛል !  ግርታን ይፈጥራሉ ለምላቸውና መልስ ለሚያስፈልጋቸው መልስ ለመስጠት እሞክራለሁ ! እንዲህ እየሆነ የጎልማሳነት እድሜየን ገፍቻለሁና ለምጀዋለሁ ! በግጭት መካከል የሚሰራ ነጻ ጋዜጠኛና ለመረጃ ፍቅር ያለው ዜጋ ህይዎት ደግሞ ከዚህ ያለፍ ሊሆን አይጠበቅም ! አይችልምም !
እስኪ ቸር ያሰማን !

በነቢዩ ሲራክ



No comments: