Thursday, November 14, 2013

በሳውዲ አረቢያ በሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ላይ የሚደርሰው ሰቆቃ አሁኑኑ ይቁም!!!

በሳውዲ አረቢያ በሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ላይ የሚደርሰው መከራ መስማት ህሊና መሸከም ከሚችለው በላይ ሆኗል። ኢትዮጵያዊን እህቶቻችን ወንድሞቻችን በአሰቃቂ ሁኔታ እየተገደሉ፤ አካሎቻቸው በስለት እየተቆራረጠ፤ እየተደበደቡና እየተደፈሩ ነው።
ይህ ሁሉ የሚፈፀው በሪያድ፣ ጂዳና አዲስ አበባ የሚገኙ የወያኔ ዲፕሎማቶች መልካም ፈቃድና ሙሉ ተባባሪነት መሆኑ ደግሞ ይበልጥ የሚያንገበግብ ነው። ወያኔ ለአረብ ሀብታም ሸሪኮቹ ለም መሬቶቻችንን ሰጥቶ ኢትዮጵያዊ በአገሩ ሠርቶ የእለት ጉርሱን መሸፈን የማይችልበት ደረጃ ላይ እንዲደርስ አደረገው። ቀጥሎ ደግሞ በሺዎች የሚቆጠሩ ልጃገረዶችና ወጣት ኢትዮጵያንን እየደለለ ከባርነት ላልተሻለ ግርድና አሳልፎ ሰጣቸው። ይህ ሁሉ ግፍ አልበቃ ብሎ “በሏቸው፤ ቀጥቅጧቸው፤ ህገወጦች ናቸው” እያለ በወገኖቻችን ላይ የሚደርሰውን ሰቆቃ በአጋፋሪነት እያስተናገደ ነው።
በኩየት በሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ላይ ተመሳሳይ ሰቆቃ ሊደርስ የሚችል መሆኑ ምልክቶች እየታዩ ነው። በኩዌት ያለአንዳች ምክንያት ቁጥራቸው በአንድ ሺህ በላይ የሆኑ ኢትዮጵያዊያን በድንገት ከሥራ ተባረዋል። እዚህም የወያኔ እኩይ እጆች እንዳሉት መረጃዎች አሉ። በሌሎች የመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች የሚገኙ ኢትዮጵያዊያንም ሕይወታቸው በዘወትር ስጋት ላይ ወድቋል።
የኢትዮጵያዊያን እጣ ፈንታ በአገር ውስጥም ከአገር ውጭም ሰቆቃና እንግልት መሆኑ የሚያሳዝን ብቻ ሳይሆን የሚያስቆጭ፤ ለመራራ ትግል የሚያነሳሳም ነው። ለአገሩ ሕዝብ የሚቆረቆር መንግሥት ኑሮን ቢሆን ኖሮ ሕይታችን እንዲህ የተመሰቃቀሰ ባልሆነም ነበር።
ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ የሳውዲ አረቢያ እና ሌሎችም የመካከለኛ ምሥራቅ አገራት መንግሥታት ለኢትዮጵያዊያን እህቶቻንና ወንድሞቻችን ሰብዓዊ ክብር እንዲሰጡ አበክረን እናሳስባለን። ሰብዓዊ መብቶችን መድፈር ዓለም ዓቀፍ ወንጀል መሆኑን ልንነግራቸው እንፈልጋለን። በወገኖቻችን ላይ የሚደርሰው ሰቆቃ አሁኑኑ ይቁም!!! ሰቆቃ ፈፃሚዎች ለፍርድ ይቅረቡ!!!
በተቻለው ፍጥነትና ባገኘነው እድል ሁሉ ተጠቅመን ሕይወታቸው አደጋ ላይ ላሉት ወገኖቻችን እንድንደርስ ግንቦት 7 ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጥሪ ያደርጋል።
በኢትዮጵያዊያን ላይ የሚደርሰው ሰቆቃ በዘላቂነት የሚወገደው ወያኔ ከሥልጣን ተባሮ የኢትዮጵያ ሕዝብ የመረጠው መንግሥት ሲያስተዳድር በመሆኑ ለዚህ ታላቅ ግብ በኅብረት እንነሳ።
በወገኖቻችን ላይ የሚደርሰው ሰቆቃ ይቁም!!
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

No comments: