Thursday, August 7, 2014

በአምስት ነጻ ጋዜጦች ላይ ጥቁር ሽብር እየተፋፋባቸው ነው!!

August 7/2014
(ኢ.ኤም.ኤፍ) ከትላንት በስትያ የፍትህ ሚንስትር መስሪያ ቤት በህዝብ መገናኛ ብዙሃን በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን እና ሬድዮ አምስት ጋዜጦችና መጽሄቶች ህገ መንግስቱን ለመናድ መሞከራቸውን በመግለጽ መግለጫ አውጥቶ ነበር። የመግለጫው ጭብጥ እንደሚያስረዳው ከሆነ፤ አምስት የፕሬስ ውጤቶች መንግስትን ሰላም የነሱ መሆናቸውና ወደፊትም በእንደዚህ መሰል የፕሬስ ውጤቶች ላይ እርምጃ እንደሚወስድ ነው ዛቻ በተቀላቀለበት ሁኔታ የተገለጸው። በአሁኑ ወቅት የሰብ አዊ መብት ገፈፋዎችን ጨምሮ ከህግ ውጭ የሚደረጉ የመንግስት አሸባሪ እርምጃዎችን፣ “ጥቁር ሽብር” የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል። ይህ በፕሬስ ውጤቶች ላይ የተካሄደው እርምጃም የ”ጥቁር ሽብር” ሌላኛው ማሳያ በመሆኑ በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው።
ጥቁር ሽብር እየተፋፋመባቸው ያሉት የፕሬስ ውጤቶች
ጥቁር ሽብር እየተፋፋመባቸው ያሉት የፕሬስ ውጤቶች
በስም የተጠቀሱት አምስት የፕሬስ ውጤቶች ክስ ሳይመሰረትባቸው፤ ለፖሊስ ቃላቸውን ሳይሰጡ፤ የፍርድ ቤት መጥሪያ ሳያገኙ ነው፤ የፍትህ ሚንስቴር መስሪያ ቤቱ “አሸባሪ” የሚል ስያሜ ሊሰጣቸው የሞከረው። የፍትህ ሚንስቴር መስሪያ ቤት በዚሁ መግለጫው ላይ “ፋክት፣ ጃኖ፣ ሎሚ፣ አዲስ ጉዳይ፣ እና እንቁ የሚባሉ መጽሄቶችን እንዲሁም አፍሮታይምስ የሚባለውን ጋዜጣ በሚያሳትሙ ተጠርጣሪዎች ላይ ክስ መስርቻለሁ” ብሏል። ይህ ክስ ፕሬሶቹ በቀጣይ የህትመት ስራዎቻቸውን ለማገድ የታቀደ ሲሆን፤ ይህን ተከትሎ ህትመት ያቆሙ መጽሄቶች እና ጋዜጦች ስለመኖራቸው የታወቀ ነገር የለም።
ትላንት ረቡዕ ለህትመት ወጥቶ የነበረው ሰንደቅ ጋዜጣ ይህን ጥቁር ሽብር አስመልክቶ የፍትህ ሚንስቴርን መግለጫ በማስቀደም የፖለቲካ ፓርቲ ሃላፊዎችንእና ጋዜጠኞችን አነጋግሯል። ስለሁኔታው ተጨባጭ መረጃ ይኖራቹህ ዘንድ የሰንደቅ ጋዜጣን ዝግጅት በፒ.ዲ.ኤፍ አቀናብረን ከዚህ በታች አቅርበነዋል። ሙሉውን ለማንበብ እዚህ ላይ ይጫኑ።

No comments: