Wednesday, August 20, 2014

መኢአድን ለማፍረስ እየተፈጸሙ ያሉ ሴራዎችና ደባዎች

August20/2014
የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) በሰላማዊ መንገድ እየታገሉ ካሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል አንጋፋውና ጠንካራው ፓርቲ ነው፡፡
aeupበዚሁ መሠረትም የተለያዩ ፓርቲዎችን በማጠናከር ቅንጅት እንዲፈጠር ካደረጉ የፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ታላቁን ድርሻ የወሰደና ለውጤትም የበቃ ነው፡፡ ዛሬም የቅንጅትን መንፈስ በመመለስ ህዝባችን ለሠላማዊ ትግሉ እንዲነሳሳ ለማድረግ ከአንድነት ጋር ለመዋሃድ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ከጫፍ ላይ ደርሶ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ በህውሓት/ኢህአዴግ መንግሥት የሚመራው ምርጫ ቦርድ የተለያዩ ምክንያቶችን በመፍጠር ውህደቱ እንዳይሳካ በመስራት ላይ ይገኛል፡፡
በአገር ውስጥ ሆነ በውጭ የምትገኙ የመኢአድ ደጋፊዎችና የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ!
በአቶ ማሙሽት አማረ የሚመሩት ጥቂት ግለሰቦች እሁድ ነሐሴ 11 ቀን 2006 ዓ.ም ከጠዋቱ 12፡00 ሠዓት ጀምሮ የታርጋ ቁጥሩ አ.አ ኮድ3-43511 የሆነች ተሽከርካሪ መኪና በያዙ የደህንነት አባላትና ካሜራቸውን ከፓርቲው በር ላይ በጠመዱ የኢቲቪ ጋዜጠኞች በመመራት የፓርቲውን ጽ/ቤት ወረሩ፡፡ በውስጥ የነበሩት እንዳይወጡ እና በውጭ የነበሩት ወደ ጽ/ቤቱ እንዳይገቡ አግተው እስከ 9፡00 ሰዓት ድረስ ውለዋል፡፡ ይህ ቡድን ከአራት አመት በፊት በዲስኘሊን ጥሰት ከፓርቲው የተወገደ እና በፍ/ቤትም እንዲወገድ የተወሰነበት ነው፡፡ ይሁን እንጂ ይህ ቡድን በህውሓት/ኢህአዴግ የደህንነት አባላት በመመራት በፓርቲው ላይ ከፍተኛ ጥፋት በመፈፀም ላይ መሆኑ በግልጽ ሊታወቅ ይገባል፡፡ ይህ ጥፋትም ሆን ተብሎ የኢትዮጵያን ሕዝብ ትግል ለማዳከምና ብሎም ጨርሶ ለማጥፋት ከተያዙ እቅዶች አንዱ ነው፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ!
እንግዲህ ይህ ቡድን ለእውነት እና ለኢትዮጵያ ሕዝብ ትግል የቆመ ቢሆን ኖሮ በደህንነቱና በኢቲቪ መሪነት የፓርቲውን ጽ/ቤት መውረር ነበረበትን? እውን የዚህ ቡድን መሪዎች ለኢቲቪ በሰጡት ቃለ ምልልስ ላይ ምርጫ ቦርድ ለመኢአድ ፍቃዱን እንዳይሰጥ መጠየቅ ነበረባቸውን? ከዚህ ላይ ልብ ልንለው የሚገባው ጉዳይ እነዚህ ግለሰቦች ለኢትዮጵያ እውነተኛና ለሕዝቧ ነፃነት የሚታገሉ ቢሆኑ ኖሮ ከገዢው ፓርቲ ደህንነትና የገዢው ፓርቲ ከሚቆጣጠረው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ሬዲዮ እንዲሁም ከምርጫ ቦርድ ጋር አብሮ መስራትና በእነዚህ ድርጅቶችም ተመርቶ መምጣት አልነበረበትም፡፡
መኢአድ የብዙ ታጋዮቹ ደም የፈሰሰበት፣ ቤት ንብረታቸውን ያጡበትና አገር ጥለው የተሰደዱበት አሁንም ቢሆን የስቃይ እና የጭቆና ቀምበር ተሸክመው እየታገሉ ባሉበት ባሁኑ ወቅት ይህ ቡድን ፓርቲውን ለማፍረስ ከገዢው ፓርቲ ጋር ማበር አልነበረበትም፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት ከሥልጣን እወገዳለሁ በሚል ስጋት ውስጥ በመውደቁ የተነሳ በሚያደርገው መፍጨርጨር ለሕዝብ መረጃ የሚያቀርቡ እውነተኛ መጽሔቶችንና ጋዜጦችን ለመዝጋት ጥረት በማድረግ ላይ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ እንደሁም ጠንካራ ፓርቲዎችን ለማጥፋት በያዘው እቅድ መሠረትም ከአራት አመታት በፊት ከፓርቲው ክስ ቀርቦ በፍ/ቤት የተወገዱትን ጥቂት ግለቦች በማበረታታት መኢአድን ለማፍረስ ጥረት ያደርጋል፡፡
ዛሬ በአገሪቱ ላይ ሕግና ሥርዓት እየጠፋ መምጣቱን የተረዳነው ሕግ እንዲያስከብሩልን ለአራዳ ፖሊስ ጣቢያ አቤት በማለት ያመጣናቸው ፖሊሶች በደህንነቱ ሥራቸውን እንዳያከናውኑ መከልከላቸውንና ወደመጡበት እንዲመለሱ መደረጉን ስንመለከት ነው፡፡
ስለዚህ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ! በድህነትና በጭቆና ቀንበር ውስጥ ወድቀህ አቅምህን እንድታጣ የተሰራብህ ብትሆንም ቅሉ ባለን አቅም ለምናደርገው ሰላማዊ ትግሉ ሁሉ ከጎናችን እንድትቆም እንጠይቃለን፡፡
ህውሓት/ኢህአዴግ እየተጫወተ ያለው የፖለቲካ ቁማር እነ ማሙሸት አማረን በፓርቲው ማፍረስ ላይ በማነሳሳትና በመኢአድ የውስጥ ችግር ያለ በማስመሰል የውጭውን እንድንረሳ ለማድረግ የሚያደርገውን ጥረት ለአገራችንም ሆነ ለሕዝባችን የሚጠቅም ስላልሆነ እንዲያስብበት እንመክራለን፡፡
እነዚህን በተሳሳተ ጐዳና እየተጓዙ ያሉ ወንድሞችና እህቶችን የኢትዮጵያን ሕዝብ ትግል ከማዳከም እንዲቆጠቡ በዱላና በአመጽ ከመሔድ ይልቅ ወደ ሰለጠነ መንገድ እንዲመጡ ምክርህን እንድትለግሳቸው እናሳስባለን፡
የመኢአድ አባላትም በያላችሁበት በጥንካሬ በመቆም ፓርቲያችሁን በንቃት እንድትጠብቁ፣ በተለመው መንገድም የሰላማዊ ትግላችሁን እንድታጧጡፉ ፓርቲያችሁ መኢአድ ጥሪውን ያቀርብላችኋል፡፡
አንዲት ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!
ነሐሴ 13 ቀን 2006 ዓ.ም

No comments: