Thursday, August 21, 2014

ሰማያዊ ፓርቲ “ለተማሪዎች በግዳጅ የሚሰጠውን ካድሬያዊ ስልጠና እና ትውልድን የማኮላሸት ሴራ አጥብቀን እናወግዛለን!” አለ

August21/2014
ሰማያዊ ፓርቲ ዛሬ ባወጣው መግለጫው ለተማሪዎች በግዳጅ እየተሰጠ ያለውን ካድሬያዊ ስልጠና በማውገዝ ኢሕአዴግ እየሰራ ያለውን ትውልድን የማኮላሸት ሴራ አጥብቀን እናወግዛለን አለ። መግለጫው እንደወረደ እነሆ፦
blue partyላለፉት 23 ዓመታት ህወሓት/ኢህአዴግ ስራዬ ብሎ ካዳከማቸውና ጉዳዬ ከማይላቸው ዘርፎች ውስጥ የሚመደበው የትምህርት ስርዓቱ ሲሆን ይህም ከኢህአዴግ ስህተቶች ሁሉ ዋነኛው እና አሳፋሪ ተግባሩ ነው፡፡ ለሁለት አስርት አመታት ትውልዱን በማምከን በሀገሩ ተስፋ እንዲቆርጥ ከገፉት ጉዳዮችም ግንባር ቀደሙ የህወሓት/ኢህአዴግ የተምታታበት የትምህርት ፖሊሲ መሆኑም ይታወቃል፡፡ ትምህርት ለአንድ ሀገር እድገት የጀርባ አጥንት መሆኑ እየታመነ የትምህርት ስርዓቱ ሆን ተብሎ በንቀት እና በዝርክር አሰራር እንዳያድግና ጥራት እንዳይኖረው ኢህአዴግ እየተጋ አሁን ድረስ ዘልቋል፡፡

በዚህ አይነቱ አጥፊ አካሄድ ምክንያትም ሀገራችን በዓለም ደሃ ሀገራት ተርታ ቀዳሚዋ ሆናለች፡፡ የተማረ እየተገፋ በስራ አጥነት ሲንከራተት እና ለስደት ሲዳረግ በካድሬነት የስርዓቱ አገልጋይ መሆን ደግሞ በተቃራኒው ተጠቃሚ እያደረገ ይገኛል፡፡ በተለይም ተማሪዎች በዩኒቨርስቲ ቆይታቸው የገዢው ፓርቲ አባል እንዲሆኑ ሲገደዱ መቆየታቸውና የኢህአዲግ አባል ካልሆኑም ስራ ሊያገኙ እንደማይችሉ እየተነገራቸው በፍራቻ ለአባልነት የተመዘገቡ ብዙዎች እንደሆኑ የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡ በዚህ ሳያበቃ አሁን አሁን ደግሞ የገዢውን ፓርቲ ያረጀና ያፈጀ ኋላቀር አስተሳሰብና ርዕዮተ-ዓለም በተማሪዎች ላይ ለመጫን በየዓመቱ መጀመሪያ ‹ስልጠና› በሚል ፈሊጥ በጀት በጅቶ በግድ ሊግታቸው እየሞከረ ይገኛል፡፡
በዚሁ በያዝነው ወርም በሁሉም ዩኒቨርስቲዎች ተማሪዎች እንዲሰበሰቡና ስልጠና እንዲወስዱ ጥሪ የተላለፈ ሲሆን ስልጠናውን ያልተከታተለም መደበኛ ትምህርቱን እንደማይቀጥል ማስፈራሪያ አይሉት ማሳሰቢያ በገዢው ፓርቲ በኩል ተላልፏል፡፡ ሌላው አስገራሚ ዜና ደግሞ ተማሪዎቹ በግድ ስልጠናውን እንዲወስዱ መገደዳቸው ሳያንስ ወደ ግቢ ከገቡ በኋላ ተመልሰው መውጣት እንደማይችሉ መሰማቱ ነው፡፡ ይህም ኢህአዴግ ካድሬዎቹን የሚያሰለጥንበት ዝግ የስብሰባ ስልት መሆኑ ጉዳዩን የበለጠ አስገራሚ ያደርገዋል፡፡
ህወሓት/ኢህአዴግ ይህንን ስልጠና ሲያካሂድም፡-
1. ህግን በጣሰ መልኩ የትምህርት ማዕከላትን የፖለቲካ ማራመጃ እና የአንድ ፓርቲ ርዕዮተ-ዓለም ማስፈፀሚያ አድርጓል፡፡
2. ይህን ፋይዳ ቢስ ስልጠና በሁሉም ዩኒቨርሲቲዎችና ከ800.000 በላይ ለሚሆኑ ተማሪዎች በሚሰጥበት ወቅት ከፍተኛ የህዝብ ሀብት እያባከነ ይገኛል፡፡
3. ተማሪዎች የእረፍት ጊዜያቸውን በነፃነት ማሳለፍ ሳይችሉ በአስቸኳይ ወደ ዩኒቨርስቲዎች እንዲመለሱ ተገድደዋል፡፡
4. በሚሰጠው ስልጠናም ላይ በአክራሪነት በብሔርተኝነትና በመሳሰሉት ጉዳዩች ሽፋን በተማሪዎች ዘንድ መርዛማ ጥላቻን እየረጨ ይገኛል፡፡
5. በአጠቃላይ በስልጠናው ወቅት ርካሽ የፕሮፖጋንዳ ስልትን በመጠቀም መጪውን ምርጫ በማምታታት ለማለፍ እየሞከረ ሲሆን ይህም በአምባገነንነቱ ቀጥሎ ህብረተሰቡን አማራጭ ለማሳጣትና ሀገሪቷን ወዳልተፈለገ አለመረጋጋት ሊወስድ እየሞከረ መሆኑን ያሳያል፡፡

በመሆኑም ሰማያዊ ፓርቲ ይህን የገዢው ፓርቲ ህገ ወጥ አድራጎት አጥብቆ እያወገዘ ጉዳዩን እየተከታተለም አቋሙን ይፋ የሚያደርግ መሆኑንን ይገልፃል፡፡ ተማሪዎችም በዚህ ህገ ወጥ ተግባር ሳይደናገጡ ያለምንም ፍርሃት ህጋዊ በሆነ መንገድ ይህን ካድሬያዊ ስልጠና በማውገዝ፣ የገዢውን ፓርቲ ድብቅ ሴራ በማጋለጥ እና ለህወሓት/ኢህአዴግ የተለመደ አጥፊ ፕሮፖጋንዳ ባለመታለል ተማሪዎች በአንድነት እንዲቆሙ ሰማያዊ ፓርቲ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡

ነሀሴ 15/2006 ዓ.ም ሰማያዊ ፓርቲ
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!

No comments: