Wednesday, August 6, 2014

ለጋዜጠኛ አዚዛ መሐመድና የሰማያዊ ፓርቲ አባል ወይንሸት ሞላ የተፈቀደው ዋስትና ተከለከለ

August6/2014
  • 135
    Share
aziza ena weyeneshetከአሸናፊ ደምሴ
በአንዋር መስጊድና አካባቢው ሐምሌ 11 ቀን 2006 ዓ.ም በተፈጠረ ግጭትና ሁከት ተሳትፈዋል በሚል ፖሊስ ምርመራ እያደረገባቸው ከሚገኙ 14 ተጠርጣሪዎች መካከል ጋዜጠኛ አዚዛ መሐመድና የሰማያዊ ፓርቲ አባል ወይንሸት ሞላን ጨምሮ ለሦስት ሰዎች ፍርድ ቤት ትናንት ጠዋት ፈቅዶት የነበረው የ5 ሺህ ብር የዋስትና መብት ከሰዓት በኋላ በፖሊስ በቀረበ ይግባኝ ውድቅ ሆኖ ዋስትናው ተከለከለ።
ሜክስኮ በሚገኘው የፌዴራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የፖሊስ ኮሚሽን ጉዳዮች የምርመራ ጊዜ ቀጠሮ ማስቻያ ችሎት የዛሬ ሳምንት የተሰጣቸውን የጊዜ ቀጠሮ ተከትሎ በችሎት ካቀረቡት 14 ተጠርጣሪዎች መካከል የአዲስ ጉዳይ መጽሔት ፎቶ ጋዜጠኛዋ አዚዛ መሐመድና የሰማያዊ ፓርቲ የብሔራዊ ምክር ቤት አባል የሆነችውን ወ/ት ወይንሸት ሞላን ጨምሮ አራት የፖሊስ አባላት (ማለትም አንድ ኢንስፔክተር፣ አንድ ምክትል ኢንስፔክተርና አንድ ምክትል ሳጅንና አንድ የኮንስታብል ማዕረግ ያላቸው) እና ሌሎች ስምንት ተጠርጣሪዎች በችሎች ሲያቀርብ የተቀሩት ከሁለተኛው የጊዜ ቀጠሮ በኋላ ፖሊስ ምርመራዬን ጨርሼባቸዋለሁ ሲል ማሰናበቱን ለፍርድ ቤት ማስታወቁ ይታወሳል።
አሁን ድረስ በምርመራ ላይ የሚገኙት ተጠርጣሪዎች ጠበቃ ያልቆመላቸው ሲሆን፤ በትናንት ጠዋቱ የችሎት ውሏቸውም በባለፈው የጊዜ ቀጠሮ ወቅት ለፍርድ ቤቱ ባቀረቡት የዋስትና ጥያቄያቸው መሠረት ፍርድ ቤቱ፤ አዚዛ መሐመድ፣ ወይንሸት ሞላ እና ኡዝታዝ መንሱር የ5 ሺህ ብር ዋስ አቅርበው እንዲሄዱ ትዕዛዝ ቢሰጥም፤ በቀደመው ችሎት ያቀረባቸውንና ምላሽ ያላቀረበባቸውን የዋስትና መቃወሚያዎች ፖሊስ ለችሎቱ አቅርቦ አስረድቷል። ይኸውም ምርመራዬን አልጨረስኩምና ዋስትና ሊፈቀድላቸው አይገባም፤ በሕክምና ላይ ያሉና ጉዳት የደረሰባቸውን የፖሊስ አባላትንም መጨረሻ ማወቅ ያስፈልጋል በሚል ለፍርድ ቤቱ ባቀረበው ይግባኝ መሠረት ችሎቱ ጠዋት ላይ የተፈቀደ ዋስትና በከሰዓት ላይ ውድቅ ሆኖ ወደ አዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ማረፊያ እንዲመለሱ ተደርጓል።
የምርመራ ተግባራቶቼን አላገባደድኩም ሲል ተጨማሪ የጊዜ ቀጠሮን የጠየቀው ፖሊስ በጥቁር አንበሳ እና በፖሊስ ሆስፒታል የሚገኙትንና በብጥብጡ ወቅት ጉዳት ደርሶባቸዋል የተባሉትን ሰዎች ሁኔታና ቃል ተቀብሎ ለማቅረብ ፍርድ ቤቱን በጠየቀው ተጨማሪ የጊዜ ቀጠሮ መሠረት የ7 ቀናት የምርመራ ጊዜ የተፈቀደለት ሲሆን፤ ለመጪው ነሐሴ 7 ቀን 2006 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል።

No comments: