Monday, March 24, 2014

የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ሰራዊትና የአማራ ዴሞክራሲያዊ ሃይል ንቅናቄ ሰራዊት ወታደራዊ ጥቃት ፈፀሙ።

March 24/2014


የኢትዮጵያን ሕዝብ ከጎጠኛውና ከአሸባሪው የወያኔ አምባገነናዊ ስርዓት ለማላቀቅ የትጥቅ ትግሉን አማራጪ አድርጎ ለሀገርና ለወገኑ መስዋዕትነት ለመክፈል ቆርጦ የተነሳው የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር /ኢሕአግ/ ለአንድነት እና ለዴሞክራሲ ከሚታገሉ ድርጅቶች ጋር ውህደት በመፍጠር የፀረ- ወያኔ ትንቅንቁንና ፍልሚያውን አጠናክሮ በመቀጠል በተሰለፈባቸው አውደ-ውጊያዎች በጠላት ላይ ወታደራዊ የበላይነትን በመቀዳጀት የሀገርና የወገን መከታነቱን እያስመሰከረ ይገኛል።

በዚህም መሰረት የጋራ ጠላትን በጋራ ለመደምሰስና የኢትዮጵያን ሕዝብ የመብቱ ተጠቃሚ ለማድረግ የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባርና የአማራ ዴሞክራሲያዊ ሃይል ንቅናቄ ውህደት በመፍጠር በመጋቢት 12 ቀን 2006 ዓ.ም በሰሜን ጎንደር ጠገዴ ወረዳ ልዩ ስሙ ግጨው በተባለ ቦታ ከወያኔው የሚሊሺያ ታጣቂ ሀይል ጋር ባደረጉት ውጊያ ከፍተኛ ወታደራዊና ፖለቲካዊ ድል ማስመዝገባቸዉን የድርጅቱ አመራሮች አስታውቀዋል።
በዚህ ውጊያ የሚሊሺያ ሰራዊት አመራር የነበሩት፦


1ኛ. አየልኝ ጫቅሌ 2ኛ. ደጀን ተጫኔ 3ኛ. ተስፉ አያናው የተባሉትን የሚሊሺያ ሰራዊት አመራሮች በመማረክ ስለድርጅቱ አላማና ፕሮግራም በማስተማር ወደ መኖሪያ ቀያቸው እንዲመለሱ ተደርጓል ።


በዚሁ እለትም በተደረገው ውጊያ በቅርቡ የወያኔውን አምባገነን ሥርዓት እድሜ ለማሳጠር ድርጅቶች በአንድነት መስራት አለባቸው በሚል ግንባር የፈጠሩት የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባርና የአማራ ዴሞክራሲያዊ ሃይል ንቅናቄ ባደረጉት ወታደራዊ የማጥቃት እርምጃ 17 የወያኔ የሚሊሺያ አባላትን ገድለው 14 በማቁሰል እንዲሁም የተለያዩ የጦር መሳሪያዎችን ከነመሰል ጥይቶቻቸው ጋር በተጨማሪም 2 ሽጉጦችን በመማረክ በጠላት ላይ ወታደራዊ የበላይነትን በመቀዳጀት አንፀባራቂ ድል ማስመዝገባቸውን የሁለቱ ድርጅቶች አመራሮች አስታውቀዋል።


የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞ ግንባርና የአማራ ዴሞክራሲያዊ ሃይል ንቅናቄ የፈጠሩት ወታደራዊ ግንባር አብሮ መስዋዕትነት ከመክፈል ባሻገር አምባገነኑን የወያኔ ገዥ ቡድን እድሜ ለማሳጠር ውሕደት ፈጥረው የትግሉን ሂደት ለማፋጠን ከመቸዉም ጊዜ በበለጠ መልኩ ጠንክረው እንደሚሰሩ የድርጅቶቹ አመራሮች ገልፀዋል።

No comments: