Friday, March 21, 2014

መኢአድ የቅድመ ውህደት ፊርማውን አደናቀፈ

March 20/2014

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)                                                     
  UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)
በመኢአድ በኩል የቀረበው ቅድመ ውህደት ያለመፈረም ሰበብ አሳዛኝና የሕዝቡን ጥያቄ ያኮሰሰ ነው!!
ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ  ፓርቲ (አንድነት) የተሰጠ መግለጫ
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ለረዥም ዓመታት የሕዝብ ፍላጎትና  አንገብጋቢ የሆነውን ተቃዋሚዎች ‹‹ተባበሩ ወይ ተሰባበሩ›› ጥያቄ   ለመመለስ በስትራቴጂና አምስት ዓመት ዕቅድ ውስጥ በማካተት መንቀሳቀስ ከጀመረ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ የውህደት ጉዳይ ለአንድነት ፓርቲ የአንድ ሰሞን ጥያቄ ሳይሆን ስትራቴጂክ ግብ ነው፡፡ የዚሁ አካል የሆነ እንቅስቃሴ በመኢአድና አንድነት ፓርቲዎች መሐከል መካሄድ ከጀመረ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ሂደቱን ለመቋጨት በርካታ ድርድሮችና የደብዳቤ ልውውጦችም  ቢከናወንም እነሆ አሁንም ተጨባጭ ውጤት በተግባር አለመታየቱ የሁለቱም ፓርቲ አባላት በእጅጉ እያሳዘነ ነው፡፡
በተለይ በቅርቡ እየተካሄደ ከነበረው ተግባር መካከል ከመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ)    መጋቢት 1 ቀን 2ዐዐ6 ዓም የተፃፈልንን  ደብዳቤ መሠረት በማድረግ የሁለቱ ፓርቲዎች ከፍተኛ አመራሮች እንዲገናኙ የተጠየቀውን ጥያቄ በደስታና በላቀ መንፈስ  ተቀብለነዋል፡፡ በዚሁ መሠረት      መጋቢት 4 ቀን 2ዐዐ6 ዓም  በሰጠነው የደብዳቤ መልስ ላይ እንደገለጽነው  በአንድነት ፓርቲ እይታ አመራሩ  የፊት ለፊት ውይይት የምንፈልገውና ወሳኝ ጉዳይ በመሆኑ  መጋቢት 7 ቀን 2006 ዓ.ም በመኢአድ ጽ/ቤት በተጠራውና የሁለቱ ፓርቲዎች የብ/ም/ቤት አባላትና የላዕላይ ም/ቤት አባላት በተገኙበት ለታሪክ በተቀረፀ ወሳኝ ስብሰባ ሠፊ የኃሳብ ልውውጦች ተካሂደው የፓርቲዎቹ ከፍተኛ አመራሮች የሚከተሉትን አስገዳጅ የውሳኔ ሃሳብ አቅርበው ነበር፡፡
በዚሁም መሠረት፡-
  1. የሁለቱም ፓርቲዎች አባላት አላስፈላጊ ጥቃቅን ጉዳዮችን በማንሳት ውህደቱን አታጓቱ ውህደት የማትፈፅሙ ከሆነ እኛ አባላት በራሳችን ውህደት እንፈፅማለን የሚል ጥብቅ ተማፅኖና ማስጠንቀቂያ አስተላልፈዋል፡፡
  2. በአጠቃላይ የሁለቱ ፓርቲዎች ፕሬዚደንቶችና አደራዳሪ ሽማግሌዎች በገቡት ቃል መሠረት ሐሙስ መጋቢት 11 ቀን 2006 ዓ.ም ቅድመ ውህደት የመግባቢያ ሰነድ እንዲፈረም ከስምምነት ተደርሶ ነበር፡፡
  3. የሁለቱ ፓርቲዎች ከፍተኛ አመራሮች የውህደት አስፈፃሚውን ጠቅላላ ጉባኤ ጠሪ ኮሚቴ አባላት የሚሆኑትን የስም ዝርዝር፣ የፊርማው ስነ ሥርዓት በሚከናወንበት እለት እንዲያመጡ ተስማምተን ነበር፡፡
በከፍተኛ አመራሮችና በሁለቱ ሥራ አስፈፃሚዎች ውሳኔ መሠረት የሁለቱ ፓርቲ ፕሬዝደንቶች ተስማምተው፣ የቅድመ ውህደት መግባቢያ ሰነድ በሁለቱ ፓርቲዎች የድርድር ኮሚቴ አባላት መካከል ተፈራርመን፤ ሆቴል ተከራይተንና ከአዲስ አበባ አስተዳደር የሕዝባዊ ስብሰባና ሰላማዊ ሰልፍ ማሳወቂያ ክፍል  የዕውቅና  ሠነድ አግኝተን  የመጨረሻ የስነ-ስርዓቱን መርሃ-ግብር በመጠባበቅ ላይ እያለን  በድንገት በመኢአድ ፕሬዝደንት  በኩል  በቁጥር መ/ኢ/አ/ድ 278/06 መጋቢት 9 ቀን 2006 ዓ.ም በእለቱ የቅድመ ውህደት ፊርማውን መፈረም እንዳማይችሉ የሚገልጽ ደብዳቤ ለፓርቲያችን  መድረሱ በእጅጉ አሳዝኖናል፡፡  ከደብዳቤው እንደተረዳነው  መጋቢት 7 ቀን 2006 ዓ.ም የፓርቲዎቹ ከፍተኛ  አመራሮች ከበርካታ የሃሳብ ልውውጥ በኋላ የደረሱበትን ውሳኔ  የሚቀለብስ፣ የሁለቱ ፓርቲዎች ተደራዳሪዎች እየተስማሙ በቃለ ጉባኤ ያፀደቁትንና ከሁሉም በላይ የሁለቱ ፓርቲ  ተደራዳሪዎች ለቅድመ ውህደት ባዘጋጁትና ባፀደቁት የመግባቢያ ሰነዶች ላይ የሰፈሩ ነጥቦችን እንደ አዲስ  በማንሳትና በጥቃቅን ጉዳዮች በመጠመድ የቅድመ ውህደቱ እንዳይፈረም ተደርጓል፡፡ ለዚህ ታሪካዊና የሕዝብ ጥያቄ መደናቀፍ  ምክንያቱ የመኢአድ ፕሬዚንት ሲሆኑ  ይህን ሁኔታ   በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር ለሚገኙ  ለሁለቱ ፓርቲዎች አባላት፣  ደጋፊዎች፣ በግል ተነሳሽነትና በሀገር ተቆርቋሪነት ስሜት ሁለቱን ፓርቲዎች ለማደራደር ሲደክሙ ለነበሩ ኢትዮጵያውያን ዜጎችና ለሕዝቡ ጥሩ ዜና ባይሆንም ላለመፈረሙ   ኃላፊነቱን የሚወስዱት የመኢአድ አመራሮች በተለይም ፕሬዝደቱ  መሆናቸውን  ማሳወቅ እንወዳለን፡፡
በዚህ አጋጣሚ  ለውህደቱ መሳካት የመኢአድ አባላትና ከፊል አመራሩ  እያሳዩ ለሚገኘው ፍላጎትና ጥረት ፓርቲያችን መልካም አክብሮቱን መግለፅ ይወዳል፡፡
መጋቢት 11 ቀን 2006 ዓ.ም
አዲስ አበባ

No comments: