Saturday, July 26, 2014

ወያኔን የሚሸነቁጥ ሕዝባዊ አመጽ

July 26, 2014
ዳኛቸው ቢያድግልኝ
Photo: ለ24 ሰዓታት የዱንያ ግንኙነታችንን የማቋረጥና በዱዓ የመጠመድ ጥሪ!!!
#Ethiopia #EthioMuslims #BlackTerror #SwitchOffYourPhone #ምንሊክሳልሳዊ

ሞባይሎቻችንን ከዛሬ ሐሙስ መግሪብ እስከ ጁሙዓ መግሪብ (ለ24 ሰዓታት) እንዝጋ!

እኛ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች አላህን የምንለምንባቸው ብዙ ጉዳዮች አሉን፡፡ ከምንም በላይ እምነታችን ላይ በመንግስት ጥቃት መሰንዘር ከጀመረ አመታት ተቆጠረዋል፡፡ ጀግኖቻችን በእስር ቤት ታጉረዋል፡፡ ተደብድበናል፤ ተዘርፈናል፤ ታስረናል፤ ተሰደናል፤ ተገድለናል፤ ሌላም ሌላም ብዙ በደል ተፈጽሞብናል፡፡ ባለፈው ጁሙዓ መንግስት ሰላማዊ ትግሉን አስቆማለሁ በሚል ቀቢጸ ተስፋ የ‹‹ጥቁር ሽብር›› እርምጃ በሺዎች በሚቆጠሩ ሙስሊሞች ላይ ወስዷል፡፡ የእምነት ቤታችን ተደፍሯል፤ የእምነት አልባሳቶቻችን ተቃጥለዋል፤ አካላችን ተጎድቷል፤ በዚህ ሁሉ በደል መካከል በ27ኛዋ ሌሊት አላህን መማጸን እና ችግራችንን ለእርሱ ማቅረብ መተኪያ የማይገኝለት ታላቅ እድል ነው፡፡

በመሆኑም ይህንን የ27ኛ የረመዳን ሌሊት እና የቀኑን ጾም ታላቅ የዱዓ ጊዜ ለማድረግና አላህን በሙሉ ልባችን ለመለመን ከዱንያ ጋር ሙሉ ለሙሉ የምንቆራረጥበት የ24 ሰዓት ጊዜ ማወጅ አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ከዱንያ ሙሉ ለሙሉ የምንቆራረጠው ከነገ ሐሙስ መግሪብ ሰላት ጀምሮ እስከ ጁሙዓ መግሪብ ሰላት ባለው የ27ኛ ረመዳን የሌሊትና የቀን ጊዜ (24 ሰዓታት) ስልካችንን ሙሉ ለሙሉ ስዊች ኦፍ አድርገን በማጥፋት ሲሆን አንገብጋቢ ለሆነ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀርም ስልካችንን በሌሊቱም ሆነ በቀኑ ክፍለ ጊዜ የማንከፍት ይሆናል፡፡ በዚህች የዱንያ ግንኙነታችንን ለመግታት ስልካችንን በምናጠፋባት የ24 ሰዓት ጊዜ አላህ ዱዓችንን እንዲቀበለን እና ያለንበትንም ፈተና እንዲያነሳልን እንመኛለን!
ድምፃችን ይሰማ
“ሰብሰብ ብሎ የጋራ አቋም መያዝና አንድ እርምጃ ወደፊት የመራመድ ምኞት” በሚል ርዕስ ይህንን ጽሁፍ ጀምሬው የዛሬው ዜና ቸር ወሬ ሲያሰማኝ ርዕሱን መቀየር መረጥኩ። የእስልምና ሀይማኖት ተከታዮች የወሰዱት ስልክ ያለመጠቀም እርምጃ እጅግ አበረታች ሆኖ በማግኘቴ አድናቆቴን መገለጽም ፈለኩ። ምንም እንኳ ይህንን አይነት እርምጃ ከፖለቲካ ድርጅቶች የጠበቅሁ ቢሆንም ሌላው ዘርፍ ጀምሮታልና በዚህ ጎዳና መሄዱ መልካም ነው። ያልተቀጠቀጠ የለምና ለምን እንደ ድጋፍ ድምጽ ስልክ ያለመጠቀሙን እንደ ትብብር መግለጫ ይሆን ዘንድ ለአንዲት ቀን ለምን አናደርገውም? የፖለቲካ ድርጅቶች የአገዛዙን ክፋት አስመልከተው መግለጫ እንደሚያወጡት ሁሉ አሁን ደግሞ ሙስሊሞች ‘ጥቁሩን ሽብር’ ለመቃውም ለጀመሩት ሰላማዊ አመጽ የጋራ ጥሪና ትብብር ቢደረግ መልካም ነው።

አሁን ወያኔ የሽብር ጥቃቱን በአንድ ደረጃ ከፍ በማድረግ ብቅ ያለውን ሁሉ እስር ቤት መጨመር ቀና ያለውን ሁሉ በየመንገዱ መቀጥቀጥ፣ ጠያቂ እንኳን እንዲጠፋ ዘመድ አዝማድ እያሳደዱ ከስራ ማባረር፣ ከሀገርና ከመንደር ማፈናቀል አፍነው መውሰድና ደብዛ ማጥፋትን ከሁለተኛና ሶስተኛ አገር አፍኖ መውሰድን በፊት ለፊት ይዘውታል። ያልተነካ አንድም የፖለቲካ ፓርቲና ማህበራዊም ሆነ የእምነት ተቋም የለም። በሰላማዊ መንገድ ጥያቄያችንን እናሰማለን፣ መብታችንንም እናስከብራለን ያሉ የእስልምናና የክርስትና ሀይማኖት ተከታዮች እየተቀጠቀጡ ነው። የፖለቲካ ፓርቲ አመራር አባላት በተለይም ወጣቶቹ ልዩ ኢላማ ውስጥ ገብተው ስቃይ እያዩ ነው። በዘርና በመንደር የተነጣጠሩ ጥቃቶች ከመቼውም በላይ አድገው ይገኛሉ።

በተለመደው የትግል መንገድ መገስገስ በተራ ለማለቅና ቅስም ለመሰባበር መንገድ ያበጃል። ምንም እንኳ የነጻነትን ትግል ገድሎ መቅበር ባይቻልም። ‘ታጋይ ይሞታል እንጂ ትግል አይሞትም’ የሚለው መፈክር መበረታቻ እንጂ ተራ በተራ እስርቤት መውረጃ ሊሆን አይገባውም። ታጋይ በተለይም መሪ እንኳን ሞቶ ታስሮም አሳምሮ ይጎዳል። መሪ የሌለው ይበተናል ወይም እስኪደራጅና እንደገና እስኪያንሰራራ ድረስ ኪሳራው አለውና ያንን መቀነስ መቻል አስፈላጊ ነው። የታሰሩ ጋዜጠኞች ብዛትና አፈናው በነፃው የመገናኛ ብዙሃን ላይ ተጽዕኖው ትንሽ አይደለም። የአንዱአለም መታሰር ተከታትሎም ተተኪ ሆነው የወጡ ወጣት ታጋዮች መታገት ይጎዳል። የአብርሃ ደስታ መታሰር ትግራይን ድምጽ አልባ እስከማድረግ ይደርሳል። አንደበተ ርቱዕ የሆኑት ሃብታሙ አያሌውና ዳንኤል ሺበሺ በጣም ያጎድላሉ። የዞን ዘጠኝ ‘ብሎገሮች’ መታሰር ነጻ ብዕር የያዙ ሚዛናዊና አስተዋይ ወጣቶችን ከሜዳው ውጪ ያደርጋል። ወያኔ እርሻ እንዳማረለት ገበሬ የበሰለ የበሰለውን መቀንጠስ ከቻለ የልቡን እየሰራ ሌላውን የጫጫታ ቤት ያደርገዋል። ወይንሸትን ፈንክቶና እጇን ሰባብሮ የሚያስር የውርጋጥ ስብስብ እንጂ መንግስት ሊባል አይቻለውም።

በአንድ ረዥም ምላስና በብዙ ጠመንጃ ሁለት አሥርት አመታት ታግተን ኖረናል። በደንባራ በቅሎ ቃጭል ተጨምሮ እንዲሉ ያ ረዥም ምላስ ከተቆረጠ በሁዋላ በቀረቻቸው ጠመንጃና ምላሱ በሚያደናቅፈው ጠቅላይ ሽቅብ ቁልቁል የሚሉት ወያኔዎች አሁን የለየለት ተዳፋት ላይ ናቸው። ወያኔ ከፋፍሎና ነጣጥሎ የሚመታበት የብልጥ ጊዜ አብቅቷል ምክንያቱም በጣም ጠግቧል በዚያው መጠንም ደድቧል። የጠገበ ደደብ የሚያስከትለው አደጋ ትንሽ አይሆንምና ተነጣጥሎ መመከት የሞኝ መንገድ ይሆናል። ስለዚህ ሁሉም የጥቃት ሰለባ ከሆነ ቢያንስ የሚያስማማ ነገር አለና ወደ ሕዝባዊ አመጽ የሚያመራውን መንገድ በጋራ ለማምጣት ቀጣይ እርምጃዎች ቢኖሩ እንዴት መልካም ነበር ብዬ አስባለሁ። አደባባይ ያልወጣ እየተሰራ ያለ ነገር ስለመኖሩ ባላውቅም የጋራ ጉባዔ የሚጠራበት ወይም ሳይነጋገሩ የሚግባቡበትና በሰላማዊ ትግል መርህ ውስጥ የሚካተት እርምጃ የሚወሰድበት ጊዜ አሁን ነው።

ምናልባትም ከሙስሊም ወገኖች ጋር ለማበርና ድጋፍም ለመስጠት እነሱ የወሰዱትን የእምቢተኛነት መንገድ በመደገፍ የስልክ ተጠቃሚነቱን ለአንድ ቀን ማቋረጥ የትግሉን መጠናከር ማሳያ መንገድም ይሆናል። ለበረቱት ጉልበት በመስጠት ሌላውም እንዲበረታታ ያደርጋል። የክርስትና ሀይማኖት ተከታዮችም የሚደርስባቸው በደል የለየለት ነውና በዚህ ከሙስሊም ወገኖች ጋር የጋራ ትብብር ወይም ድጋፋቸውን ቢገልጹ የሕዝባችንን አንድነት ማሳያ ይሆናል። በሌሎች ተቋማትም ላይ የተመጣጠነ እርምጃ መውሰዱ ወያኔን በሚገባ የሚያስደነግጠው ይመስለኛል። ቢያንስ ሁሉም የሚስማማበት ደግሞ ኢቲቪን አለመመልከት ጋዜጣ አለመግዛትና ራድዮ አለመስማት ሊሆን ይችላል። ያኔ እየተዘጋጀ ያለው ገለባ ፕሮፓጋንዳ መውደቂያ ያጣል። ቢራ አለመጠጣት እንኳን ትልቅ ቁንጥጫ ሊሆን ይችላል።

በተለይ አብዛኛው የንግድ አገልግሎትና ተቋም ከሕዝብ በተዘረፈ ገንዘብ ጥቂት ዘረኞች የያዙት በመሆኑ እርምጃው አርስበርስ የሚያፋጥጣችው ይሆናል። እንደ ወትሮው ሁሉ እያንዳንዱ ፓርቲ የራስ የራሱን የትግል ጥሪ እየያዘ እየመጣ እኔ እበልጥ እኔ እበልጥ ፉክክር ውስጥ እንዳይገባና ሕዝቡንም ግራ እንዳያጋባ ግን ምኞቴ ነው። ሕዝቡ ምን እናድርግ ትግሉን እንዴት እናቀጣጥለው እያለ በሚገኝበት ሁኔታ ውስጥ የፖለቲካ ፓርቲዎች የመሪነት አቅም የሚፈተሽበት ጊዜ ነውና ለሁላችንም ብርታት፣ ጥንካሬና ብልህነትን ከዚህም ጋር የሚመጣ ድልን እመኛለሁ።
biyadegelgne@hotmail.com

No comments: