Monday, July 21, 2014

የዞን 9 ጦማሪያን አባላት “ በወያኔ የስለላ ተቋም ተደርሶበት የተከሰሱበት ማስረጃ” እጃችን ውስጥ ገባ!!

July 21, 2014
የዞን 9 ጦማሪያን አባላት “ በወያኔ የስለላ ተቋም ተደርሶበት የተከሰሱበት ማስረጃ”  እጃችን ውስጥ ገባ!!
AbbayMedia:  ለጥረታቸው እያመሰገን ኢትዮጵያውያን በሙሉ ይህንን የኢንተርኔት ደኅንነት መጽሐፍ እውቀት እንዲጠቀሙበት እንመክራለን ።
ሙሉውን ዝርዝር እዚህ ላይ በመጫን ይመልከቱ፡-  https://securityinabox.org/am/howtobooklet
የኢንተርኔት ደኅንነት መጽሐፍ

 ይህ የኢንተርኔት ደኅንነት መጽሐፍ ደኅንነቱ የተጠበቀ የኢንተርኔት ግንኙነት እንዲኖረን ማወቅ የሚያስፈልጉንን መሠረታዊ ነገሮች ለማብራራት በሚያስችል መልኩ የተዘጋጀ ነው። መመሪያው በኢንተርኔት ግንኙነት ሊያጋጥሙ የሚችሉ አደጋዎችን በመለየትና በማብራራት፣ እነዚህን አደጋዎች ለመቀነስ የሚያስችል በተገቢ መረጃ ላይ የተመሠረተ ውሳኔ እንድንሰጥ ያስችለናል። ይህን ለማረጋገጥም ስምንት ከደኅንነት (ሴኵሪቲ)፣ ከመረጃ ጥበቃ (ዳታ ፕሮቴክሽን) እና ከጥብቅ ግንኙነት (ኮምዩኒኬሽን ፕራይቬሲ) ጋራ የተያያዙ ሰፋፊ ጥያቄዎችን ይመልሳል።

በእያንዳንዱ ምእራፍ መግቢያ የተነሳውን ርእሰ ጉዳይ ለማብራራት የተፈጠሩ ምናባዊ ክስተቶችና ገጸ ባህርያት ይገኛሉ። እነዚህ ገጸ ባህርያት የተወሰኑ ጉዳዮችን የሚያነሱበት እና የሚዘወተሩ ጥያቄዎችን የሚመልሱባቸው አጫጭር ምልልሶች በየምእራፉ ውስጥ ይገኛሉ። ከየምእራፉ የምንቀስማቸው ትምህርቶች ዝርዝርም በየምእራፉ ይቀርባል። በየምእራፎቹ የሚጋጣሙን በርካታ ቴክኒካዊ ቃላትና ስያሜዎች ትርጉም በመጽሐፉ መጨረሻ በማገናዘቢያ ዝርዝር ውስጥ ይገኛል። በማብራሪያው ውስጥ የሚጠቀሱ ሶፍትዌሮችን በተመለከተ “በአጠቃቀም መመሪያ” (Hands-on Guides) ውስጥ ተጨማሪ ማጣቀሻዎች እናገኛለን። በዚህ “የመርጃዎች ስብስብ” (ቱልኪት) ውስጥ የሚገኝ ምእራፍ ወይም መመሪያ ተነጥሎ ለብቻው ሊነበብ ይችላል፤ በወረቀት ለማተምም (ፕሪንት) ሆነ በኤሌክትሮኒክ መልኩ ለሌሎች ለማካፈልም የተመቸ ነው። ሆኖም “የኢንተርኔት ደኅንነት በእጃችን” (Security in-a-box) መመሪያው የሚጠቅሳቸውን በመጽሐፉ እና በሶፍትዌር መመሪያው ውስጥ ተበታትንው የሚገኙትን ሊንኮች (links) እና ማገናዘቢያዎች በሚገባ ብንከተላቸው ከመመሪያው የበለጠ ተጠቃሚ እንሆናለን። የዚህ “እንጎቻ መጽሐፍ” (Booklet) የታተመ ቅጂ ካለን “የአጠቃቀም መመሪያውን” (Hands-on Guides) በምንጠቀምበት ጊዜ ሁሉ ከአጠገባችን ቢኖር መልካም ነው። በእንጎቻ መጽሐፉ ውስጥ ስለአንድ ዘዴ የተጻፈውን ምእራፍ ጨርሰን ሳናነብና ዘዴውን በሚገባ ሳንረዳው የዲጂታል ደኅንነታችን አስተማማኝ መጠበቂያ አድርገን ልንቆጥረው አይገባም።

የሚቻል ሲሆን የእንጎቻ መጽሐፉን ምእራፎች በቅደም ተከተል ማንበብ የተመረጠ ነው። የኢንተርኔት ደኅንነትን (ሴኵሪቲ) ማስጠበቅ ሒደት ነው። አንድ ተጠቃሚ ኮምፒውተሩ ከቫይረሶችና ከማልዌር (Malware) ነጻ መሆኑን ሳያረጋግጥ የኢንትርነት ግንኙነቶቹ ምሥጢራዊነት ፍጹም የተጠበቀ እንዲሆን ለማድረግ ቢፈልግ ሙከራው አስተማማኝ ውጤት ሊያመጣ አይችልም። ሌባው አስቀድሞ እቤት ውስጥ ከገባ በኋላ በሩን ከውጭ እንደሚቆልፍ ባለቤት መሆን ማለት ነው። ይህ ማለት በዚህ መጽሐፍ ከሚነሱት ርእሰ ጉዳዮች መካከል አንዱ ከሌላው የበለጠ አስፈላጊ ነው ማለት አይደለም። ነገር ግን ወደ በኋላ የሚመጡት ምእራፎች ተገልጋዮች አስቀድመው ያውቋቸዋል ብለው ታሳቢ የሚያደርጓቸው መረጃዎችና እውቀቶች ይኖራሉ፤ ለምሳሌ አዳዲስ ሶፍትዌሮች (software) የምንጭንበት ኮምፒውተራችን ስላለበት ሁኔታ አስቀድመን እንደምናውቅ ታሳቢ ይደረጋል።

በእርግጥ እነዚህን ምእራፎች ያለቅደም ተከተል ለማንበብ እና ለመጠቀም የሚያስገድዱ በቂ ምክንያቶች ሊያጋጥሙ ይችላሉ። በአጠቃቀም መመሪያው የተጠቀሱትን መሣሪያዎች/ሶፍትዌሮች መጫን ከመጀመራችን በፊት በኮሚፒውተራችን ውስጥ የሚገኙ እጅግ አስፈላጊ ፋይሎችን ወደ መጠባበቂያ ቋት መገልበጥን (back up) መማር ያስፈልገን ይሆናል። አለዚያም በምሥጢር መያዝ ያለባቸውን ፋይሎቻችንን በፍጥነት ለመደበቅ የሚያስገድድ ድንገተኛ ሁኔታ ሊገጥመን ይችላል፤ ይህ ደግሞ የሚገኘው በምእራፍ አራት ነው። ምናልባት ደግሞ ደኅንነቱ አስተማማኝ ባልሆነ የኢንተርኔት ካፌ ኮምፒውተር ስሱ መረጃዎችን ለመመልከት እንፈልግ ይሆናል። ለምሳሌ ያህል ከዚህ ኮምፒውተር በአገራችን የተከለከለ ድረ ገጽ ከፍተን መመልከት እንፈልጋለን እንበል፤ ይህን በቀላሉ ለመማር በቀጥታ “ማንነትን መደበቅ እና የኢንተርኔት ሳንሱርን ማለፍ” ወደሚለው ምእራፍ ስምንት እንዳንሔድ የሚከለክለን ነገር የለም።

1. ኮምፒውተርን ከማልዌር እና ከሰርጎ ገቦች (hackers) እንዴት መከላከል ይቻላል?
2. መረጃዎችን ከአካላዊ ጥፋት ለመጠበቅ ምን ማድረግ እንችላለን?
3. አስተማማኝ የይለፍ (የምሥጢር) ቃል መፍጠር እና መጠቀም
4. በኮምፒውተራችን ውስጥ ያሉ ስሱ መረጃዎችን እንዴት መጠበቅ ይቻላል?
5. የጠፉ መረጃዎችን መልሶ ማግኘት የሚቻለው እንዴት ነው?
6. ስሱ መረጃዎችን በጥንቃቄ ማጥፋት የሚቻለው እንዴት ነው?
7. የኢንተርኔት ግንኙነታችንን በምሥጢር መያዝ ይቻላል? እንዴት
8. ማንነትን መደበቅ እና የኢንተርኔት ሳንሱርን/እገዳን ማለፍ
9. ደኅንነቱ የተጠበቀ የተንቀሳቃሽ (ሞባይል) ስልኮች አጠቃቀም
10. በማኅበራዊ ገጾች የራስን እና የመረጃዎችን ደኅንነት መጠበቅ
መፍቻ
ልብ ይበሉ የተከሰሱበትና “የወያኔ የመረጃ ስለላ ተቋም ማስረጃዪ ነው” ብሎ የያዘው ስለ ኢንተርኔት አጠቃቀም እውቀትን በማዳበራቸው ነው።ይህ ማንኛውም ተማሪ ወይም ሰው ሊያውቀውና ሊመራው የሚገባ የትምህርት አካል መሆኑንም የስለላ ተቋሙ ዘንግቶታል። ይሁን እንጂ ጦማሪዎቹ ለኢትዮጵያውያን የሚጠቅም ትምህርት በሚል ያዘጋጁቱን ትምህርት ሁሉም ሰው እንዲማርበት አጥብቀን እንመክራለን።

No comments: