Thursday, October 23, 2014

“አርማጌዶን” የፍጻሜያችን ፍጻሜ!

October 23,2014
(ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው)
armageddon
በዚያው ሰሞን ነው የወያኔ ባለሥልጣናት ሲያሾፉብን “ይሄንን ሁሉ ሰይጣናዊ ድርጊት የሚፈጽሙት በዓላማ እነሱ መሆናቸው ተረስቶ” ከመሀከላቸው አንዱ ምን አለ “የሕወሀት መሪዎች በዚህ ወቅት በብሔሮች መካከል ያለው የጥላቻ መንፈስና የወደፊት የሀገሪቱ ሁኔታ እጅግ አሳስቧቸዋል በጣምም እየተጨነቁበት ያሉበት ጉዳይ ነው የብሔራዊ እርቅ ጉዳይ አስፈላጊነቱ የግድ እንደሆነ ያስባሉ እንዴትና ከማን ጋራ እንደሚጨርሱት ተቸግረው ነው እንጅ….” ብሎ ቀለደብን፡፡
ከእኛም ወገን ደግሞ ጅሎቹ የዋሀኑ ተላሎቹ እውነት መስሏቸው በየፊናቸው አንዳንድ ነገሮችን እስከማለት ደረሱ፡፡ ወያኔ ግን ወያኔ ነውና ንጹሕ መስለው አሳሰበን ካሉ በኋላም እንደትናንቱ ሁሉ ዛሬም በዓላማ ይሄንን ሰይጣናዊ የዘርና የሃይማኖት ግጭት ፍጅት ለመፍጠር ሴራውንና ድርጉቱን እየፈጸመ ይገኛል ተፈጥሯዊ ባሕርይው ነውና እስካለ ጊዜ ድረስም ሲፈጽም ይቆያል፡፡
የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ በቀደም ጥቅምት 7-2-2007ዓ.ም. በነበረው ዝግጅቱ የመ.ኢ.አ.ድ ተወካይ ከሆኑት ሰውና ከሁለት ተጠቂ የአማራ ተወላጅ ቁስለኞች ጋር ባደረገው ቃለ መጠይቅ ከዚህ ዓመት ዋዜማ ከጳጉሜ 5 ጀምሮ እስከ አሁንም ድረስ በመከላከያ በፌደራልና በፖሊስ ሠራዊት አባላት ሁለቱ ብሔረሰቦች በቦታው ከሐምሳ ዓመታት በላይ አብረው ተከባብረው እንዳልኖሩ ሁሉ በአማራ ተወላጆች ላይ ከመዠንግር ተወላጆች የተቃጣ የተፈጸመ ጥቃት አስመስለው የወሰዱትና እየወሰዱት ባሉት ጭፍጨፋ ወይም የጅምላ ግድያ ወይም የዘር ማጥፋት ወንጀል እስከ አሁን ድረስ ከ540 በላይ ዜጎች ተጨፍጭፈዋል፣ ከ25 ባለይ ቤቶች በኗሪዎቹ ላይ እንደተዘጉ እሳት ተለቆባቸው እንዲቃጠሉ ተደርጓል፣ ከዚህ የተረፉት ሕፃናት እናቶች አረጋውያን ዕድሜ ልክ የለፉበት ቤት ንብረታቸውን ጥለው ተፈናቅለው እንዲሰደዱ ተደርጓል፡፡
በእርግጥ ይሄንን አሳዛኝ ዜና ሲናገር የአሜሪካ ድምፅ ራዲዮ የመጀመሪያው አይደለም ቀደም ሲልም ጀምሮ የኢሳት ቴሌቪዥን ዘግቦት ነበር፡፡ ይህ ልክና ቅጥ ያጣ ከፍተኛ የሆነ ንቀት የተሞላ አረመኔያዊ የግፍ ድርጊት ዓለማችን የዛሬ ሁለት ዐሥርት ዓመታት በሩዋንዳ በቱትሲና ለዘብተኛ የሁቱ ተወላጆች ላይ ካስተናገደችው አረመኔያዊ ግፍ በኋላ በድጋሜ ሲከሰት ይህ የመጀመሪያው ነው፡፡ በኢትዮጵያ ታሪክ ደግሞ በአንድ ዘር ተወላጆች ላይ በዘራቸው ምክንያት ብቻ ጥቃት ሲፈጸም ይህ በአማራ ተወላጆች ላይ ወያኔ ሥልጣን ከያዘ ጊዜ ጀምሮ እየወሰደ ያለው መጠነ ሰፊ ጥቃት ከዮዲት ጉዲት 842ዓ.ም-882ዓ.ም. ለ40 ዓመታት ከፈጸመችው ጥቃት በኋላ የመጀመሪያው ነው፡፡ ይህ ሰሞኑን በዚህ አረመኔ አገዛዝ የተፈጸመው የግፍ ድርጊት የአንድ ዘር አባላት በመሆናቸው ብቻ 540 ያህል ሰዎችን ከአንድ አካባቢ ብቻ ሲፈጁ የተቀሩትንም ሲያቆስሉና ሲያፈናቅሉ ትናንትናም በሱማሌና በአኝዋክ ዜጎቻችን የተፈጸመው የጦር ወንጀል ወይም የዘር ማጥፋት ለዚህች ሀገርና ሕዝብ ህልውና ምን ያህል አደገኛ እንደሆነ በሚገባ የታወቀ ቢሆንም እጅግ በሚደንቅና ግራ በሚያጋባ ሁኔታ ከዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በተለይም የሰው ልጆች መብት ያንገበግበናል ከሚሉ መንግሥታት አንድ የተባለ ነገር የለም ለምን? ለምን? እኮ ለምን?
ይህ የግፍ አገዛዝ የተማመነውን አላውቅም ሊያደርገው ካሰበው ሰይጣናዊ ድርጊት ዝግጅቱ የተነሣ ይሄንኛውን ጨምሮ ከዚህም ከቀም በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ስለፈጸማቸው የግፍ ድርጊቶች ተከታታይ ክሶች ጉዳይ ፈጽሞ የሚያሳስበው ሆኖ አልተገኘም፡፡ ከንቱ የቁራ ጩኸት አድርጎ ነው እያየው ያለው፡፡ ነገሩን እያደረገው ያለው በዓላማ ነውና ከመታረም ከመስተካከል ይልቅ በተጠናከረ መልኩ መፈጸሙን የሙጥኝ ተያይዞታል፡፡
ከዚህ ቀደም በተጠናና በተቀናበረ መልኩ በተለያዩ ቦታዎች የተፈጸሙ ተመሳሳይ የግፍ ድርጊቶቹ ሊደብቀው ሊያስተባብለው የማይችለው ሲሆንበት ይሄንን የፈጸሙ ከአሥተዳደር መዋቅሩ የወረዳ የዞንና የክልል ባለሥልጣናት እንዳሉ ያምንና ለፍርድ እንደሚቀርቡም ይገልጻል፡፡ ይሁን እንጅ አስቀድሞም ይሄንን የሚለው ለማስመሰል ወይንም ለመልስ ያህል እንጅ ሊያደርገው ባለመሆኑ እስከ ዛሬ ድረስ እነ እከሌ እነ እከሌ እንዲህ እንዲህ ዓይነት ወንጀል መፈጸማቸው በመረጋገጡ ሕጉ እንዲህ ዓይነት ቅጣት ጥሎባቸው ተቀጥተዋል ብሎ ለሕዝብ ሲገልጽና ሲያስቀጣ ታይቶ አይታወቅም፡፡ ከልምዱ እንደምንረዳው እንዲፈጽሙ ታዘው በሌላ ተመሳሳይ ወንጀል ላይ የሚገኙ አባላቱንም ወንጀሉ በሕዝብ ዕይታ ውስጥ ሲሆንና ሊታበል የማይችል ሲሆንበት ለይስሙላ እንደታሰሩ ይገለጽና ግን ወዲያውኑ ወደ ሌላ አካባቢ ተዛውረው እንዲሠሩ ያደርጋል እንጅ አገዛዙ በራሱ እዝ ስር ሆነው ወንጀል ከፈጸሙ አባላቱ ማንንም ተጠያቂ በማድረግ ታይቶ አይታወቅም፡፡ ይህም ጉዳይ ወንጀል እየተፈጸመ ያለው በሚገባ ታስቦበት በተጠናና በተቀናጀ መንገድ መሆኑን ያረጋግጣል፡፡
ይሄንን ጉዳይ የኢትዮጵያ ሕዝብ በሚገባ ያውቃል ይረዳል፡፡ ይህ መሆኑ ከታወቀ የኢትዮጵያ ሕዝብ በተለይም ከመጀመሪያው ጀምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ጥቃቱ ሲፈጸምበት የቆየውና በቀጥታ ያነጣጠረበት አማራው ምን እንደሚጠብቅ ፈጽሞ ሊገባኝ አልቻለም፡፡ በፍጹም ያልተዘራ ነው የበቀለው “የእሳት ልጅ አመድ” እንዲሉ ያለ አባቱ ነው እየኖረ ያለው፡፡ ሕዝቡ ለመታረድ ተራውን እንደሚጠብቅ የቄራ የእርድ ከብት የረባ ተቃውሞ እንኳን ሳያሳይ በዝምታ እጅና እግሩን አጣምሮ ምንም እንዳልተፈጠረ ተራውን መጠበቁ ለሚያየው ሁሉ የማይታመንና ትንግርት ነው፡፡ ኧረ ምንድን ነው የሆንከው ወገኔ? ተራህን ነው ወይ የምትጠብቀው? እነዚህ በግፍ የተገደሉ ወገኖችህ እኮ ከአማራነታቸው በስተቀር አንድም በደል አንድም ወንጀል የለባቸውም፡፡ ወንጀላቸው እኮ አማራነታቸው ብቻ ነው፡፡
ታዲያ እንዲህ ከሆነ እንዴት እኔን ይምረኛል ብለህ አሰብክ? ይህ ጭራቅ አገዛዝ እነሱን ብቻ በልቶ ይቀር ይመስልሀል? ይተወኛል ያልፈኛል ይምረኛል ብለህ ተስፋ የማይደረግ ነገር ተስፋ አድርገህ ከሆነ መበላትህ ነው ለዘር እንኳን ሳትተርፍ ማለቅህ ነው መፈጀትህ ነው፡፡ ቀን ያልፍ ይሆናል ብለህ እንጀራህን ድርሻህን የራስህን ማዕድ እየነጠቀ ሲበላብህና የበይ ተመልካች ሆነህ በችጋር እየተቆላህ እየተጠበስክ አኗኗሪ መሆንህንስ ችለኸው ኖርክ ሲያቅትህም እግርህ ወዳመራህ እየተሰደድክ የበረሀ አውሬና የባሕር ዓሣ ሲሳይ ሆነህ እያለቅህም ከችጋርህ ጋር ቆየህ እንዲህ ተዋርደህ ተሰቃይተህ ያቆየሀት ነፍስህ ያልፋል ያልከው ቀን ሳያልፍ ተደፍታ የምትቀር ከሆነ ከዚህ በኋላ ያለህ ትዕግሥት ለምንህ ይሆናል?
ተው ሳይቀድምህ ቅደመው? ተው ተበላህ? ተው አለቀልህ? ኧረ ምን ጉድ ነው? ኧረ ተው ኧረ ተው? በምኖች እጅ እንዳለህ እኮ ፈጽሞ አላወከውም! እንዳንተ አስተዋይነት እንዳንተ አርቆ አሳቢነት እንዳንተ ኃላፊነት እንደሚሰማው ዜጋነትህ እንዳንተ ትዕግሥት መስሎሀል? ፈጽሞ አላወከውም አለማወቅህ ሊያስበላህ ነው ቅንነትህ ታጋሽነትህ አሳቢነትህ ሊያስጨርስህ ነው፡፡ ተው በጊዜ ንቃ የሞት ሰው መሆንህ ካልቀረ ገለኸው ሙት የሚቀረው ልጅህ ቀን ይውጣለት በደምህ ዘርህን ታደግ ትውልድህን ነጻ አውጣ፡፡ ቀንህን ጠብቀው ማለቅህ ካልቀረ ነፍስህ በከንቱ አትለፍ ሀገርንና ሕዝብን የሚታደግ ቁምነገር ሥራባት፡፡ ገለኸው ሙት ጉርቦውን እነቀው ተው ተነሥ አለቀልህ? የቀኑ ቀን እማ የመጨረሻው ቀንማ ምን ልታደርግ ትችላለህ? ያ ቀን እኮ ካንተ ይልቅ የሚመቸው ለሱ ነው፡፡ ያኔማ ምን መላወሻ አለህ? ተረፍርፈህ ከማለቅ በስተቀር ምን አማራጭ የሚኖርህ መሰለህ?
ወያኔ በሰነዱ አስፍሮት እንዳየኸው እንደሰማኸው “አያጅባጅቦ ሳታመሀኝ ብላኝ” እንዲሉ አብሮ ለመኖር፣ ተከባብሮ ለመኖር፣ እንግዳን ለማስተናገድ ያለህን በሃይማኖታዊ አስተምህሮ የታሸ የበሰለ ባሕል ሸምጥጠው በመካድ “አማራን ለጥቃት የሚዳርገው ትምክህተኛነቱ ነው” ይሄንን ትምክህት ይዞ ከሌላው ሕዝብ ጋር ሊኖር አይችልም! ብለው ቆርጠውብሀል፡፡ አይተሀል ሰምተሀል፡፡ እውን አንተ እንደዚያ ሆነህ ነው? ወይስ ለማጥቂያ ምክንያት ሲፈለግልህ?
ትምክህት መሠረት ካለው የሚያኮራ እንጅ እንዴት ነው የሚያሳፍር የማይፈለግ እንዲጠፋ የሚፈለግ ሊሆን የሚችለው? ደናቁርት ሆይ! ይሄ ትምክህት ከየትም የመጣ ወድቆ የተገኘ ይመስላቹሀል? ይህ ትምክህት ተፈልጎ የመጣ ሳይሆን ለሽዎች ዓመታት ከነበረን የሥልጣኔ የነጻነት የማንነት እሴቶችን ለመፍጠር በተደረገ ውጣ ውረድና ታሪክ የተነሣ በራሱ ጊዜ የተፈጠረ የሥነልቡና ሀብት ነው፡፡
ደናቁርቱ ይህ ማንነት ምን ያህል እንደተደከመበት ምን ያህል መሥዋዕትነት እንደተከፈለበት እያወቁ ለታሪክ ለቅርስ ለማንነት ካላቸው ጠላትነት የተነሣ ይሄንን ቅርስህን ታሪክህን ማንነትህን ጣልና ባዶ ሁን ቀፎ ሁን አልጫ ሁን እያሉ እየተጫኑት እያስገደዱት እያዋከቡት ግራ እያጋቡት ይገኛሉ፡፡ ወያኔ “ትምክህት” የማንነት ምስክራችን መሆኑን ቅርሳችን መሆኑን የቀረልን ሀብታችን መሆኑን የወደፊት የመነቃቂያ ጉልበታችን መሆኑን የወኔ ምንጫችን መሸነጫችን መሆኑን ጠንቅቆ ስለሚያውቅና ስለሚያሳስበው ትምክህታችንን ከልቦናችን ከደማችን ላይ ነቅሎ ጥሎ ገልቱ ስልብ ጀሌው አድርጎን ሊቀር በርትቶ እያሴረ ነው፡፡ ወያኔ በአማራ ላይ ስለሚያመር እንጅ ትምክህተኛ አማራ ብቻ ነው ያለው ማን ነው? ለዚህች ሀገር ሥልጣኔና ነጻነት ድርሻ የሌለው የለምና ይበላለጥ ካልሆነ በቀር በዚህች ሀገር ታሪክና ማንነት ትምክህት የማይሰማው ብሔረሰብ ማን አለ? በግለሰብ ደረጃ ግን የዚህችን ሀገር ጥፋቷን የሚመኙ የጥፋት ልጆች አሉና ከዚህ ጠላትነታቸው የተነሣ እነሱ ማውደም ማጥፋት በመቻላቸው በዚህ ሥራቸው እብሪትና ትዕቢት ይሰማቸው ካልሆነ በስተቀር በምንም ተአምር ትምክህት ሊሰማቸው እንደማይችል ለማንም ግልጽ ነው፡፡
እኔስ እኮራለሁ ፤ ቅርሴ ነው ትምክሕቴ
በደም የወረስኩት ፤ ከእናትና አባቴ
የትንሣኤየ አቅም ፤ መነሻ ጉልበቴ
ትምክሕቴ ነው ውርስ ፤ ቅርስ የታሪክ ሀብቴ፡፡
ትልቅ እንደነበርን ፤ ትልቅ እንሆናለን
ያለው እኮ ካሳ ፤ ተናግሮ ኃይለ ቃልን
ለማገናኘት ነው ፤ ትናንትና ነገን፡፡
የሀገርን ታሪክ ፤ ታሪኬ ካላሉት
ከወዴት ይገኛል ፤ ያ ቅርስ ትምክሕት
አንተ ባንዳ ሆነህ ፤ ከነ ዘርማንዘርህ
ስታደማ የኖርክ ፤ ለሀገር ጠላት አድረህ
ታዲያ ትምክህቱ ፤ ከወዴት ይምጣልህ?
ተከናነብ እንጅ ፤ ውርደት እንደ አባትህ፡፡
ከጥንት ከመሠረት ፤ ሳይደከምበት
ከእናትና ከአባት ፤ ሳይወራረሱት
ግራ ቀኝ ቢያፈጡ ፤ ከየት ይገኛል ትምክህት?
በውጪ የምትኖሩ በስደት ያላቹህ ወገኖቻችን ሆይ! ፡-
ይሄውላቹህ እንግዲህ የእኛ መጨረሻ ይሄው ሆኗል፡፡ የቀን ጉዳይ ነው እንጅ ሳንሞት ሞተናል ነፍሳችን ሳይወጣ ሞተን ተቀብረናል መቸም ይሄንን እየሰማህ ሥራው ይሠራልህ መብሉም ይበላልህ አይመስለኝም፡፡ ከዚህ የከፋ ነገር የለህምና ሥራዬ ምኔ ሳትል ከሊቅ እስከ ደቂቅ፣ ከሃይማኖት መሪ እስከ ሕዝባዊ፣ ከምሁሩ እስከ ጨዋው ሁላቹህም የሚሰማህ የሚረዳህ የሚደርስልህ መንግሥት ባይኖርም አማራ ብቻ ሳትሆን ሌላውም የኢትዮጵያ ልጅ የሐበሻ ዘርም ቢሆን በወያኔ ያልተጎዳ ዘር የለምና ሁልህም በያለህበት ሀገር አንድላይ አደባባይ ወጥተህ ለእግዚአብሔርና ለታሪክ እሪ በል፡፡ መጨረሻችን ይሄውና እንዳለቅን እንደተፈጀን ቆጥረኸን አልቅስልን፣ ሙሾህን አውርድልን፣ እንባህን ተራጭልን፡፡ ይሄንን ባታደርግ ግን እርም እንደበላህ ቁጠረው፣ እንደሸጥከን እንደከዳኸን ቁጠረው፣ ደማችንን ደመ ከልብ እንዳደረከው ቁጠረው፡፡
ወገኔ ሆይ! መንገድ ቢሠራ ሕንፃ ቢደረደር ግድብ ቢገነባ ምን ቢያደርግ ላንተ እንዳይመስልህ፡፡ እንዲህ እንዲህ እያደረገ በምታውቀውም በማታውቀውም ጥቃቱ መጦ ጨርሶህ ለራሱ ተዝመንምኖ ሊኖርበት እንጅ፡፡ ከአያያዙ ዕይና ተረዳ ላንተ አስቦ እንዳይመስልህ ከድርጊቱ እወቅ ከአስተሳሰቡ ገምተው ከአፈጻጸሙ ንቃ፡፡ ለሕዝብ በማሰቡ ይመስልሀል እርስ በእርስህ ሊያፋጅህ የሚጥረው? የብሔረሰቦችን እኩልነት በማመኑ ይመስልሀል ጥቂትም የነበሩትን የሌላ ብሔረሰብ ተወላጆችን እየፈነገለ ሥልጣን የተባለውን ሁሉ በራሱ ዘር ብቻ እንዲያዝ ያደረገው? ላንተ ስላዘነ ይመስልሀል የሀገሪቱን ሀብት ሁሉ በፓርቲውና በግለሰቦቹ እጅ ጠቅልሎ የያዘው? ወገኔ ሆይ! ይሄ ይሄ ካላነቃህ ሌላ ምን ሊያነቃህ ይችላል?
የበረሀ አውሬ ፤ አለምዳለሁ ብሎ
ሰይጣንን መልአክ ፤ ሊያደረግ ተስፋ ጥሎ
ወገኔ አለቀ ፤ በየዕለት ተገሎ
ለሰይጣን አምልኮው ፤ መሥዋዕት ታድሎ
አፉን እንደዘጋ ፤ በአዚም ታጅሎ፡፡
ተበልተህ አትለቅ ፤ ተው ስማ ተው ስማ
በሀገሩ ሰው ሳያልቅ ፤ ሳትሆን ውድማ
ወኔህ ተቀስቅሶ ፤ ዘራፍ ብትልማ
ማን ከፊትህ ሊቆም ፤ ምኑም አይሰማ
የሚገባበትም ፤ ድራሹ አይታወቅ
እንደዚህ መሆኑ ፤ ላንተም እስከሚደንቅ፡፡
እንዲህ ከብዶ የታየህ ፤ ቋጥኝ ተመስሎ
ገለጥ ብታደርገው ፤ ባገኘኸው ቀሎ
ገለባ ቢከመር ፤ ተራራ አክሎ
ያለ የሚመስለው ፤ እስኪነሣ ነው አውሎ፡፡
ለዘር ትረፍ ካለህ ፤ በሰይፍህ ተቀስፎ
መሆኑን ታያለህ ፤ ባዶ የንብ ቀፎ፡፡
ከቀየህ መብቀሉን ፤ ወገንነቱን ዐይተህ
ስምክን ይዟልና ፤ አንተን የሆነ መስሎህ
እጅግ ተዘናጋህ ፤ ባዕድ አልመጣ! ብለህ፡፡
ከጠላትም ጠላት ፤ ሆኖ እንደከፋብህ
እንድታውቅ አድርጎ ፤ ማን የት በነገረህ?
ጉዞህ ከአውሬ ጋራ ፤ መሆኑን ካወከው
መቅደምህ ብቻ ነው ፤ ነፍስህን የሚያተርፈው፡፡
ለወያኔ ተሰልፈህ እንደዜጋና እንደሰው ለምን? እንዴት? ሳትን የገዛ ወገንህን እየጨፈጨፍክ ያለህ የመከላከያ የፌዴራልና የፖሊስ ሠራዊት አባላት ሆይ! ፡-
ይሄንን ድርጊት በገዛ ወገንህ ላይ ምንም የሠራው ወንጀል እንደሌለ እያወክ ጨክነህ ስለፈጸምክ ወያኔ አንተን ይምርሀል እንዳይመስልህ፡፡ ከእሱ ጋር በድሎት የምትኖር እንዳይመስልህ፡፡ እንድትሠራለት የፈለገውን ሠርተህ ከጨረስክ በኋላ ቀጣዩ ኢላማው ከራሱ ዘር ውጪ የሆንከው የመከላከያ የፌዴራል የፖሊስ ሠራዊት አባላት መሆንህን እወቀው፡፡ አእምሮ ካለህ ማስተዋሉ ካለህ ይሄንን ጉዳይ ከወያኔ ታሪክ ትረዳለህ፡፡
የምትተርፍ መስሎህ ፤ ማንነትህን ብትከዳ
አማራ አይደለሁ እያልክ ፤ ብትገባም ሌላ ጓዳ
እሱ እንደሆን አይተውህ ፤ ይጨርስሀል ለቃቅሞ
ሱማሌነት አላዳነ ፤ አኝዋክ ነኝ ማለት ኦሮሞ፡፡
ወያኔን በታሪኩ እንደምታውቀው ወያኔ ማለት ለተራና ነውረኛ የፖለቲካ ትርፍ ሲል ሆን ብሎ ቀጥሮ ሀውዜን ላይ የገዛ ወገኖቹህ እንዲጨፈጨፉ ያደረገ አረመኔ ነው፣ ወያኔ ማለት ትግሬ ስላልሆኑና ስለፈራቸው ብቻ በሐሰት ክስ ወንጅሎ አብረውት ታግለው የገቡትን የሌላ ብሔረሰብ አባላትን የሚገል የሚያስር የሚያባር ወራዳ የአንድ ጎጥ የወንበዴ ቡድን ነው፣ ወያኔ ማለት በምርጫ 97ዓ.ም. ላይ “ስለገደሉ ገደልኩ” ለማለት ለተቃውሞ የወጡ ሰላማዊ ሰልፈኞችን ለመምታት ከተሠማሩት ውስጥ ሰባት ወይም ዘጠኝ የሚሆኑትን የገዛ ኃይሉን ከኋላ አዘጋጅቶ ባስቀመጣቸው መትቶ ከገደለ በኋላ 199 ሰላማዊ ሠልፈኞችን የገደለ ሌላም አንተ የምታውቀውን እኛ የማናውቀውን ብዙ ዓይነት ግፍ የፈጸመና እየፈጸመ ያለ አረመኔ አገዛዝ ነው፡፡
እናም ቀንህ እስኪደርስ ነው እንጅ ለአንተም ለእያንዳንድህ ቢሆን ይመለስልሀል እንዳይመስልህ፡፡ ቀንህን ነው የምትጠብቀው ልዩነት የለንም ቶሎ ነቅተህ ካልቀደምከው በስተቀር የቀን የጊዜ ጉዳይ ነው እንጅ አንተም እሬሳ ነህ፡፡ ብትቀድመው ነው የሚሻልህ ጊዜ የለህም ቶሎ ንቃ! ሕዝብ ላይ፣ ወገንህ ላይ፣ እናትህ ላይ፣ አባትህ ላይ፣ እኅትህ ላይ፣ ወንድምህ ላይ ያነጣጠርከውን አፈሙዝ መልሰህ አንሥተህ ከራሱ ግንባር ላይ አርከፍክፍበት፡፡ ሞትህን ገድለኸው በሞትህ ላይ ፎክርበት እራስህን ነጻ አውጣ ነፍስህን ከጭራቅ አትርፋት፡፡ ሀገር ሕዝብህን ታደግ፣ የሚያኮራህን ታሪክ ሥራ ጊዜ የለህም ፍጠን የአፍታ ጊዜ ካባከንክ ያልቅልሀል መበላትህ ነው፡፡ አንተ ብቻ ትንሽ ድፈር በጣም ቀላል ነው ከቁርስ አያልፍም ፍጠን! ፍጠን! ወገን ፍጠን!
ቁረጥ ቁረጥ ስለው ፤ ገና ሲያመነታ
ድንገት ቆርጠው ጣሉት ፤ ከእንቅልፉ ለአፍታ፡፡
መቅደም እንጅ ነበር ፤ የወንድነት ግብሩ
ነገን ዛሬ ላይ ዐይቶ ፤ በቁም ሳይቀበሩ
እስኪቀደሙማ ፤ ቆመው ካንቀላፉ
ምን አለው ለሬሳ ፤ መቀበር ነው ትርፉ፡፡
የትግራይ ህዝብ ሆይ! ፡-
ወያኔ ይሄንን ሁሉ ግፍ የሚሠራው ለአንተ ጥቅም ሲል እንደሆነ ሲነግርህ ቆይቷል አንተም ታውቃለህ፡፡ ወያኔ በሚሠራው ሥራ ሁሉ ያንተ ብርቱና የማያወላዳ ድጋፍና ይሁንታ እንዳለው በአጽንኦት ይገልጣል ይሄንን ታውቃለህ፡፡ ወያኔ በቻለው መጠን ሁሉ መተለየና ፍጹም ኢፍትሐዊ በሆነ መንገድ አንተን ተጠቃሚ ለማድረግ ሲጣጣር “አይ! ይሄማ ሕገ ወጥ ነው ከሌላው ሕዝብ ጋራም ያቃቅረኛልና አይሆንም አልፈልግም” አላልክም ይልቁንም “በረሀ እያለ አደርግላቹሀለው ብሎ ቃል የገባልንን እስከዛሬ ድረስ አላደረገም ተከድተናል” የሚል ቅሬታ እንዳለህ ይነገራል፡፡ እጅግ በሚገርምና በሚያሳዝን መልኩ ይሄ ምን ማለት እንደሆነ ግን ጨርሶ አልገባህም፡፡ ይህ አንተን መከታ ያደረገ ግፈኛ አገዛዝ ያንተን ክንድ ተደግፎ ለሚሠራው ወንጀል ሁሉ ኃላፊ መሆንህን አልገባህም አልተረዳህም ወይም ይሄ መሆኑን አምነህ ተቀብለሀል ኃላፊነቱን ለመውሰድም ተዘጋጅተሀል ማለት ነው፡፡
ወያኔ እስከአሁን ያንተን ውክልና ይዞ በሠራው ግፍ ያልወደድከው ኖሮ በግልጽ “አይ! በስማችን እየተጠቀምክማ ይሄንን ልታደርግ አትችልም!” ስትል ታይተህ ተሰምተህ አታውቅም፡፡ ይልቁንም የሞቀ ድጋፍህ እየተቸረው ይገኛል፡፡ አሁንም ይሄ ማለት ምን ማለት እንደሆነ ጨርሶ አልገባህም፡፡ ወያኔ በሚያሴረው ሰይጣናዊ ሴራ ዛሬ ዓለም አንድ መንደር ሆና ዜጎች ባሕር ተሻግረው ሁሉ በባዕዳን ሀገራት ሠርተው በሚኖሩበት ዘመን የአማራ ተወላጆችን እናት አባቶቹ ለነጻነቷና ለህልውናዋ በሞቱላት በገዛ እናት ሀገሩ የተለያዩ አካባቢዎች ውጡ እያሰኘ ወልደው ከብደው ከየኖሩበት ቀየ እያፈናቀለና እየገደለ እንደቆየ ታውቃለህ፡፡ ይሄም ምን ማለት እንደሆነ ፈጽሞ አልገባህም፡፡
ወያኔ ይሄንን በማድረጉ፤ መቸም የታሪክ እውነታ ነውና ከታሪክ እውነታ ውጭ ደሞ ለአንተ ተብሎ የተለየ ነገር ሊሆንልህ አይችልምና ነገ ቀን ሲለወጥ ወያኔ ክፉኛ እንዲያቄምብህ ባደረገው የኢትዮጵያ ሕዝብ ይህ “ውጡልን” የሚለውና የሌላውም ጥቃት እጣ ባንተ ላይ ቢደርስ ልትለው የምትችለውን አንድም ነገር እያሳጣህ እንደሆነ ከቶውንም አልገባህም፡፡ የሰው ጭንቅላት የያዝክ እስከማይመስል ድረስ ተደፍነሀል፡፡ ገብቶህም ከሆነ ከወዲሁ ልትወስደው የሚገባህን እርምጃ ስትወስድ ጨርሶ ታይተህ አታውቅም፡፡ እናም ብዙ ሊገቡህ ያልቻሉ የከፋ ዋጋ የሚያስከፍሉህ ነገሮች አሉ፡፡ ገብቶህም ከሆነ የማስተካከያ የማረሚያ እርምጃዎችን አለመውሰድህ ዕዳው ያንተ መሆኑን አላወክም ወይም ኃላፊነቱን ለመውሰድ ወስነሀል ማለት ነው፡፡ ይህም ምን ማለት እንደሆነ አልገባህም እጅግ እጅግ እናዝናለን፡፡
“ነጻነቱ ስለሌለኝ እንጅ ሳይሰማኝ ቀርቶ አይደለም እኔም እኮ ችግር አለብኝ እንዴት ብየ የተቃውሞ ድምፅ አሰማለሁ?” የሚል ምክንያት ቢኖርህ ተቀባይነት ሊኖረው የማይችልበት ምክንያት ቢያንስ እንደሌላው ብሔረሰብ ሁሉ በተለያየ መንገድ ቅሬታህን ማሰማት አልቻልክም፣ አሁንም እንደሌላው ብሔረሰብ ሁሉ ከሀገር ውጪ ባሉ ልጆችህ የተቃውሞ ድምፅህን ማሰማት የምትችል ሆኖ እያለ ይሄንን ዕድል ልትጠቀምበት አልቻልክም፡፡ እዚያ ያሉ ልጆችህም እንዳንተ ሁሉ አግባብነት በሌለውና እግጅ ኃላፊነት በጎደለው መልኩ ፍጹም ጭፍን ድጋፋቸውን ለዚህ ደንቁሮ ላደነቆረህ አገዛዝ ከአህያ የተሻለ ማሰብ ለማይችል የጎጥ ቡድን የሚሰጡ ብቻ ናቸው፡፡ ይሄ ምን ማለት እንደሆነ እነሱም አልገባቸውም፡፡ እናዝናለን ምን ማድረግ ይቻላልብቻ እንዳወቅንህ እንድታውቅ፡፡ ህልውናህን ከወያኔ ህልውና ጋር ማጣበቅህ ማቆራኘትህ እንዴት ብስለት መስሎ እንደታየህ እጅግ እግጅ የሚገርምና ከአንድ ሕዝብ ሊጠበቅ የማይችል ያልተለመደም አስተሳሰብ ነው፡፡
ወያኔ የሠራልህ የጠቀመህ የበጀህ መስሎሀል ነገር ግን ሠርቶልህ ሳይሆን ሠርቶብህ ጠቅሞህ ሳይሆን አሲሮብህ እንደሚሄድና እንዲህ የተንሰፈሰፍክለትን ያህል አምርረህ የምትረግምበት ዘመን እንደሚመጣ ልትጠራጠር አይገባም፡፡ አርቆ ማሰብ ከቻልክ ይህ ሁሉ ከመሆኑ በፊት ልታደርገው የምትችለውን ነገር አድርገህ የማይቀረውንና ደስ የማይለውን ክፉ ቀንህን ለማስቀረት እንድትችል ስመክርህ ከልብ እያዘንኩልህ ነው፡፡ ልብ አድርግ ይሄንን ማድረግ የምትችለው ዛሬ እንጅ ነገ አይደለም፡፡ ነገማ ሌላ ቀን ነው፡፡
በል እንግዲህ ወገኔ ልልህ የምችለው ይሄንን ነው ካለሁ አለሁ መልሰን እንገናኛለን ከሌለሁና አውሬዎቹ ከበሉኝ ደኅና ሁን!፡፡ የአባቶቻችን አምላክ ይርዳህ፣ ድፍረቱን ኃይሉን ጽናቱን ይስጥህ፣ በእናት አባቶችህ ጫማ ያቁምህ፡፡
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ ይሁን!
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!

No comments: